ሄምንግዌ እና ፋሽስታዊው ሰላምታ
በ1938 ዝነኛው ደራሲ ኧርነስት ሄምንግዌ ባያቸው ሁለት ፎቶግራፎች ተበሳጭቶ ነበር። አንደኛው ፎቶግራፍ (ከ1936–39) በተደረገው የስፔይን የእርስ በእርስ ጦርነት በፍራንኮ ወታደራዊ ኃይሎች በተጣሉ ቦምቦች የተገደሉት ልጆች ሬሳ በስፔይን ባርሴሎና ውስጥ በመደዳ ተዘርሮ የሚያሳይ ነው። በዚያን ጊዜ ከተገደሉት 875 ሰዎች መካከል 118ቱ ልጆች ነበሩ። ሄምንግዌ እነዚህን ሲቭሎች በቦምብ እንዲደበድቡ ትዕዛዝ የሰጠው ሰው ማን ይሆን? ብሎ አሰበ።
በኒው ዮርክ ከተማ ፓትሪክ ካርዲናል ሄይስ በስፔይን ያሉት የጀኔራል ፍራንኮ ወታደራዊ ኃይሎች ድል እንዲያደርጉ ጸሎት አድርገው እንደነበር የሚገልጽ ዜና ከኒው ዮርክ ሄራልድ ትሪቡን መሰማቱ ሄምንግዌን ይበልጥ ኅሊናውን ረበሸው። ሆኖም ደራሲውን ያሳሰበው ሁለተኛው ፎቶግራፍ የትኛው ነበር?
በሰሜናዊ ስፔይን በሳንቲያጎ ደ ኮምፖስቴላ ካቴድራል ፊት ለፊት የስፔይን የጦር መኮንኖችና ቀሳውስት ወታደሮች በሰልፍ በሚያልፉበት ጊዜ ሰላምታ ሲሰጡ የሚያሳይ ፎቶግራፍ ነው። ታዲያ ይህ ፎቶግራፍ ምን የሚያሳስብ ነገር ነበረው? ሄምንግዌ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ጀኔራል አራንዳና እና ጀኔራል ዴቪላ መሆናቸውን ለይቻቸዋለሁ . . . ይሰጡት የነበረውንም ሰላምታ አውቄዋለሁ። የጥንቱ የስፔይን መደበኛ የጦር ሠራዊት የሰላምታ አሰጣጥ ነበር። ያልተረዳሁት ነገር ቢኖር የሉጎው አቡን፣ የሳንቲያጎው ሊቀ ጳጳስ፣ የሳንቲያጎው ቄስና የማድሬዱ ጳጳስ እየሰጡት ያለውን ሰላምታ ነው። እየታየ ያለው ይህ ሰላምታ ፋሽስታዊ የሰላምታ አሰጣጥ ነውን? የናዚዎችና የኢጣሊያ ፋሽስቶች የሰላምታ አሰጣጥ ይህ ነውን?” አዎን፣ በእርግጥም እንዲህ ነበር!
በካቶሊኮች በተጣሉ ቦምቦች የተገደሉትን ልጆችና የካቶሊክ ጳጳሳት የናዚዎችንና የፋሽስቶችን ሰላምታ ሲሰጡ መመልከቱ ሄምንግዌን ግራ አጋባው። ምናልባትም የስፔይን ካቶሊክ ቀሳውስት በስፔይን የሚካሄደውን የእርስ በእርስ ጦርነት እንደ ቅዱስ ጦርነት አድርገው ቡራኬ እንደሰጡት ሳይገነዘብ አይቀርም። ሂትለር ለሁለተኛው የዓለም ጦርነት ላደረገው የጦር ልምምድ ባገለገለውና በርዕዮተ ዓለም ልዩነት ምክንያት በተነሣው በዚህ ግጭት ከ500,000 በላይ የሚሆኑ የስፔይን ተወላጆች ሕይወታቸውን አጥተዋል።
የኢየሱስ ግማሽ ወንድም የነበረው ያዕቆብ ምን ብሎ ጽፎ ነበር? “እናንተ ከዳተኞች! ዓለምን የሚወድድ የእግዚአብሔር ጠላት መሆኑን አታውቁምን? እንግዲህ ዓለምን የሚወድድ ሁሉ የእግዚአብሔር ጠላት መሆኑ ነው።” ከጥቂቶቹ በስተቀር የሕዝበ ክርስትና ቀሳውስት ብዙውን ጊዜ ከዓለም የፖለቲካና ወታደራዊ ገዥዎች ጋር ራሳቸውን አስማምተዋል። — ያዕቆብ 4:4 የ1980 ትርጉም
[በገጽ 31 ላይ የሚገኝ ምንጭ]
A.G.E. Fotostock