“ከቤት ወደ ቤት”
“በየዕለቱ በመቅደስና ከቤት ወደ ቤት ስለ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደሆነ ማስተማርንና መስበክን አይተዉም ነበር።” (ሥራ 5:42 አዓት) የይሖዋ ምሥክሮች ከበር ወደ በር ለሚያደርጉት የስብከት ሥራቸው ማስረጃ ለማቅረብ ይህን ከላይ የተጠቀሰውን ጥቅስና ሥራ 20:20ን አዘውትረው ይጠቅሳሉ። ይሁን እንጂ በጀርመን አገር አንዳንድ የይሖዋ ምሥክሮችን የሚተቹ ሰዎች የግሪክኛውን ቃል በትክክል አልተረጎሙትም በማለት የአዲሲቱን ዓለም ትርጉም አተረጓጎም ነቅፈዋል።
ይሁን እንጂ እንዲህ አይነቱ ነቀፌታ ትክክል ነውን? ፈጽሞ ትክክል አይደለም። መጀመሪያ ነገር ሌሎች ስድስት የጀርመንኛ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞችም እነዚህን ቁጥሮች በተመሳሳይ መንገድ ተርጉመዋቸዋል። ከእነሱም መካከል ዙርሸር ቢበል፣ በሩፐርት እስቶር የተዘጋጀው “አዲስ ኪዳን”፣ በኤን አድለር የታረመው የፍራንዝ ዚገና የጃኮብ ሻፈር ትርጉሞች ይገኙበታል። ብዙ የእንግሊዝኛ ትርጉሞችም ከዚህ አተረጓጎም ጋር ይስማማሉ።
ጀርመናዊው ምሁር ሐንስ ብሩንስ ሥራ 5:42ን “ከቤት ወደ ቤት” ብለው መተርጎማቸው ትክክል መሆኑን ሲያስረዱ “በጥንቱ ግሪክኛ አነጋገር መሠረት ከቤት ወደ ቤት ይሄዱ የነበሩ ይመስላል” ብለዋል። አዎን በዚህ ጥቅስ ላይ “ካት ኦይኰን” የሚለው የመጀመሪያው አባባል “በቤት” የሚል የመስተዋድድነት ትርጉም ያለው ሳይሆን “በየቤቱ” የሚል የአከፋፋይነት ትርጉም ያለው አባባል ነው። (“ካት ኦይኩስ” የሚለው በሥራ 20:20 ላይ የሚገኝ ሐረግ በብዙ ቁጥር የተነገረ ሲሆን “በየቤቱ” የሚል ትርጉም አለው።) እንደ ሃይንዝ ሹርማን የመሳሰሉት ሌሎች ምሁራንም ይህ አተረጓጎም ትክክል መሆኑን ገልጸዋል። የአዲስ ኪዳን ማብራሪያ መዝገበ ቃላት አታሚዎች የሆኑት ሆርስት ባልዝና ጌርሀርድ እሽናይደር ይህ አገላለጽ “ከአንድ ቤት ወደ ሌላ ቤት” በማለት ሊተረጐም እንደሚችል ይናገራሉ። በርካታ የእንግሊዝኛ ማመሳከሪያ ጽሑፎችም ይህንን ጥቅስ በተመሳሳይ መንገድ ያብራሩታል።
እንግዲያውስ አዲሲቱ ዓለም ትርጉም አሁንም እንደገና የተቺዎችን ጥቃት ለመቋቋም ችሎአል። ከዚህም ይበልጥ ከቤት ወደቤት የሚደረገው አገልግሎት ጠንካራ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ድጋፍ እንዳለው ግልጽ ነው። (ከማቴዎስ 10:11-14፤ 24:14 ጋር አወዳድር) በዚህ ረገድ የይሖዋ ምሥክሮች የመጀመሪያው መቶ ዘመን አቻዎቻቸውን ለመምሰል ታድለዋል።