ከሙት ባሕር ጥቅሎች የመጨረሻው መውጣት
ባለፈው መስከረም ለአሥርተ ዓመታት የቆየው አንድ ምሁራዊ ኬላ ተሰበረ። አዲስ ክርክር ሊነሣ ቢችልም የሙት ባሕር ጥቅሎችን በሚያጠኑ ተማሪዎች መካከል የነበረው የከረረ ክርክር ያበቃ መስሏል።
የሙት ባሕር ጥቅሎች በሙት ባሕር አቅራቢያ በሚገኙ ዋሻዎች የተገኙት በ1947 እና በተከታዮቹ ዓመታት ነበር። እነዚህ ጥቅሎች የዕብራይስጥ ቅዱሳን ጽሑፎችን መሠረታዊ ትክክለኛነት ለማረጋገጥና ኢየሱስ በምድር በነበረበት ጊዜ በፓለስቲና ምድር የነበረውን ሃይማኖታዊ ሁኔታ ለመረዳት የሚያስችል እውቀት ለማስገኘት ከፍተኛ ጥቅም ሰጥተዋል። (ኢሳይያስ 40:8) አንዳንዶቹ የብራና ጽሑፎች ብዙ ሳይዘገዩ የታተሙ ሲሆን በ1991 ላይ 400 የሚያክሉ የብራና ጽሑፎች ሳይታተሙ በመቆየታቸው አብዛኞቹ ምሁራን ገና ሊያገኟቸው አልቻሉም ነበር። አብዛኞቹ ምሁራን “በአሁኑ የማሳተም ፍጥነት የሙት ባሕር ጥቅሎች የያዟቸው እውቀት ለዓለም በሙሉ ከመዳረሱ በፊት ሁላችንም ሞተን እንደምናልቅ ስናስብ ተስፋ ቆርጠናል” ብለው እንደተናገሩት እንደ ፕሮፌሰር ቤን ዛየን ዋክሆልደር ተሰምቷቸው ነበር።
ባለፈው መስከረም ወር ግን ይህ ሁኔታ ተለውጧል። መጀመሪያ ፕሮፌሰር ዋክሆልደርና የሳቸው ተባባሪ የሆኑት ማርቲን አቤግ በጥንቃቄ የተጠበቁት ጽሑፎች በብልሀት ለመቅዳት በኮምፒተር የተጠቀሙ መሆናቸውን አስታወቁ። ከዚያም በዩናይትድ ስቴትስ ካሊፎርኒያ በሳን ማሪኖ የሚገኝ የሃንቲንግቶን ቤተ መጻሕፍት የቀድሞዎቹን የብራና ጽሑፎች ፎቶግራፍ እንዳነሣ ጥሩ ስም ያላቸው ምሁራን በነፃ እንዲያገኟቸው የሚያደርግ መሆኑን አስታወቀ። በጥሩ ሁኔታ እንዲጠበቁና እንዳይጠፉ ሲባል ጥቅሎቹ በበርካታ የፎቶግራፍ ቅጂዎች ተዘጋጅተዋል። የፎቶግራፎቹ ስብስቦች በልዩ ልዩ ቦታዎች እንዲቀመጡ ተደርጓል። ከእነዚህም አንዱ የሀንቲንግቶን ቤተ መጻሕፍት ነበር።
አንድ ምሁር ይህን የሁኔታዎች መለወጥ “የበርሊኑን ግንብ ከማፍረስ ጋር የሚተካከል ምሁራዊ ሥራ” በማለት ጠርተውታል። የቀድሞዎቹ የጥቅሉ አሳታሚዎች በኮምፒተር የተቀዳውን ጽሑፍ ሕትመትና የፎቶግራፎቹን መውጣት “ስርቆት” ብለው ጠርተዋል። ስለ ድርጊቱ ከትክክለኛ ስነ ምግባር ውጭ መሆን ብዙ ዓመታት የሚቆይ ክርክር ሳይጧጧፍ አይቀርም። ቢሆንም ብዙ ተጨማሪ ምሁራን መላውን የሙት ባሕር ጥቅል የማየት አጋጣሚ ያገኛሉ።
[በገጽ 32 ላይ የሚገኝ ሥዕል]
ከሙት ባሕር ጥቅሎች አንዱ የሆነው የዕንባቆም ማብራሪያ ቅጂ