የተቀበረ ሀብት ለማግኘት መጣር
በ1848 በአሜሪካ ካሊፎርኒያ ውስጥ ሰተር በተባለው የእንጨት መሰንጠቂያ ፋብሪካ አጠገብ ወርቅ ተገኘ። በ1849 በሺዎች የሚቆጠሩ በአንድ ጊዜ ሀብታም ለመሆን ተስፋ በማድረግ ከያሉበት ወደ አካባቢው ጐረፉ። በዩናይትድ ስቴትስ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛውን ቦታ የያዘ የወርቅ ሽሚያ ተጀመረ። በአቅራቢያው የምትገኘው የሳን ፍራንሲስኮ ወደብ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ከትንሽ መንደር ተነሥታ 25,000 ነዋሪዎች የሚገኙባት ከተማ ሆነች። በቅጽበት ሀብታም የመሆኑ ተስፋ ኃይለኛ የመሳብ ችሎታ ሆነባቸው።
የጥንቷ የእስራኤል ንጉሥ ሰሎሞን ሰዎች የተቀበረን ገንዘብ እንዴት አጥብቀው እንደሚፈልጉ አውቋል ይህንንም እንዲህ በማለት በጻፈ ጊዜ ጠቅሶታል:- “ረቂቅ እውቀትን ብትጠራት፣ ለማስተዋልም ድምፅህን ብታነሣ፣ እርስዋንም እንደ ብር ብትፈላልጋት፣ እርስዋንም እንደ ተቀበረ ገንዘብ ብትሻት የዚያን ጊዜ ይሖዋን መፍራት ታውቃለህ፣ የአምላክንም እውቀት ታገኛለህ።” — ምሳሌ 2:3–5
በወርቅና በብር ብዙ ልትሠራ ትችላለህ፤ በእውቀትና በማስተዋል ግን ይበልጥ ልትሠራ ትችላለህ። እውቀትና ማስተዋል ትክክለኛ ውሳኔ እንድታደርግ፣ ችግሮችን መፍታት እንድትችል፣ በጋብቻ የተሳካልህ እንድትሆንና ደስታ እንድታገኝ ይረዱሃል። (ምሳሌ 2:11, 12) በተመሳሳይም እውነተኛ እውቀትና ጥበብ ፈጣሪህን እንድታውቀው፣ ዓላማውን እንድትረዳና እንድትታዘዘው እንዲሁም ደስ እንድታሰኘው ይረዳሃል። ወርቅ ከእነዚህ አንዱንም አያስገኝልህም።
የሚከተሉት የመጽሐፍ ቅዱስ ቃላት ትክክል ናቸው:- “የጥበብ ጥላ እንደ ገንዘብ ጥላ ናትና፤ የእውቀትም ብልጫዋ ጥበብ ገንዘብ ላደረጋት ሕይወትን እንድትሰጥ ነው።” (መክብብ 7:12) ብዙዎች ቅጽበታዊ ሀብት ለማግኘት ያልማሉ፤ ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስን ከፍቶ እውነተኛ ሀብት የሆኑትን ማስተዋልን፣ እውቀትንና ጥበብን ማግኘት እንዴት ይበልጥ ብልህነት ነው።