ወንጌላውያን የሚሆኑት እነማን ናቸው?
ከዛሬ 40 ዓመታት በፊት በተደረገ በአንድ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ስብሰባ ላይ አባላቶቹ “የወንጌላዊነትን መንፈስ እንዲያቀጣጥሉ” እንዲሁም መንጎቻቸው “ለወንጌላዊነት ሥራ እንዲነሣሱ” ያስተምሯቸው ዘንድ በጥብቅ ተመክረው ነበር። ከአምስት ዓመታት በኋላ የካቶሊክ ቄስ የሆኑት ጆን ኤ ኦብሬን “እጅን አጣጥፎ መቀመጥ ሳይሆን” “እነርሱ ዘንድ በመሄድ” አዳዲስ ደቀ መዛሙርት ማፍራቱ አስፈላጊ እንደሆነ ጽፈዋል። በጥር 1994 ደግሞ ሊቀ ጳጳስ ጆን ፖል ዳግማዊ “ዛሬ በወንጌል የምናፍርበት ሳይሆን ሰገነት ላይ ወጥተን የምንሰብክበት ጊዜ ነው” ሲሉ ተናግረው ነበር።
እነዚህ ለወንጌላዊነት ሥራ በየወቅቱ የቀረቡ ጥሪዎች ጆሮ ዳባ ልበስ የተባሉ ይመስላል። ኢላዋራ ሜርኩሪ በተባለው የአውስትራሊያ ጋዜጣ ላይ የወጣ አንድ ጽሑፍ እንዲህ ሲል አትቷል፦ “በደቡብ ጠረፍ አካባቢ የሚገኙት ስመ ጥር ካቶሊኮች እምነታቸውን በተመለከተ የይሖዋ ምሥክሮች የሚያደርጉትን ነገር ለማድረግ አይፈልጉም።” “ባጭር አነጋገር ወንጌላዊነት በካቶሊክ አእምሮ ውስጥ የለም” ሲሉ አንድ ሰው ተናግረዋል። አንድ ሌላ ሰው ደግሞ እንዲህ ሲሉ አሳባቸውን ገልጸዋል፦ “ቤተ ክርስቲያኒቷ እምነቷን ማስፋፋቷ ጥሩ ቢሆንም በር እያንኳኩ መሆን የለበትም። ምናልባት በትምህርት ቤቶች ሃይማኖታዊ ትምህርት በመስጠት አለዚያም ደግሞ ደብዳቤ በመላክ ቢደረግ የተሻለ ይሆናል።” በአካባቢው የሚገኝ የአንድ ካቴድራል አስተዳዳሪ እንኳ ሳይቀሩ ሊቀ ጳጳሱ ምን ማለታቸው እንደሆነ በትክክል ማብራራት አልቻሉም። እንዲህ ብለዋል፦ “ሰዎች ወንጌሉን በሕይወታቸው ውስጥ እንዲሠሩበት እናበረታታለን። ይህ እንግዲህ ከበር ወደ በር መሄድ ማለት ከሆነ ሌላ ነገር ነው።” ይህን ዜና የዘገበው ጽሑፍ ርዕስ “ካቶሊኮች ጳጳሱ ያቀረቡትን የስብከት ጥሪ አልተቀበሉትም” በማለት ነጥቡን ጠቅለል አድርጎ ገልጾታል።
ሕዝበ ክርስትና የወንጌላዊነትን ሥራ መሥራት ይሳናት እንጂ ከአምስት ሚልዮን የሚበልጡት የይሖዋ ምሥክሮች “ሂዱና . . . አሕዛብን ሁሉ . . . ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” የሚለውን የኢየሱስን ትእዛዝ በመፈጸም ላይ ናቸው። (ማቴዎስ 28:19, 20፤ ከሥራ 5:42 ጋር አወዳድር።) በአሁኑ ጊዜ ከቤት ወደ ቤት የሚያደርጉት ስብከት ከ230 በሚበልጡ አገሮች ውስጥ በመከናወን ላይ ነው። የያዙት መልእክት መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ወደፊቱ ጊዜ የሚናገረውን ድንቅ ተስፋ ያዘለ አስተማማኝ መልእክት ነው። በሚቀጥለው ጊዜ ወደ ቤትህ ሲመጡ ለምን አታነጋግራቸውም?