“ተወዳጅ ሚስት ያለችው ደስተኛ ባል”
አልፎ አልፎ አንዳንድ ሰዎች፣ የይሖዋ ምሥክሮች ትዳር እንዲፈርስ ያደርጋሉ በማለት በግልጽ ይወነጅላሉ። ሆኖም ከትዳር ጓደኛሞቹ መካከል አንደኛው ብቻ የይሖዋ ምሥክር የሆነባቸው በርካታ ስኬታማ ትዳሮች ይህ አባባል ከእውነታው የራቀ መሆኑን ያሳያሉ። በአንድ የፈረንሳይ ጋዜጣ ላይ የወጣ የሚከተለው ደብዳቤ በቤተሰብ ሕይወት ውስጥ የመጽሐፍ ቅዱስን ምክር በተግባር ማዋል ደስታ የሰፈነበት ትዳር እንደሚያስገኝ ያሳያል።
“የይሖዋ ምሥክር የሆነች ተወዳጅ ሚስት ያለችው ደስተኛ ባል ሆኜ ለ28 ዓመታት ያህል ኖሬአለሁ። ከእርሷ ያልወለድኳቸውን ሁለት ልጆች ጨምሮ ለአምስቱም ልጆቼ እኩል እንክብካቤ በማድረግና የላቀ ፍቅር በማሳየት አሳድጋቸዋለች። በአሁኑ ጊዜ 45 ሠራተኞች ያሉት የአንድ ኩባንያ ሥራ አስኪያጅ ስሆን በሥራው ዓለም ስኬታማ እንድሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳደረገችልኝ ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ። ከዚህ የተነሳ በቋሚነት የሚደርሰኝ ጋዜጣ ላይ የይሖዋ ምሥክሮች ለሎቴጋሮን ክልል አስጊ እንደሆኑ የሚገልጽ ጽሑፍ ሳነብ ተጨባጭ የሆነ ምስክርነት ለመስጠት ወሰንኩ።”
በተጨማሪም ደብዳቤው እንዲህ ይላል:- “የይሖዋ ምሥክሮች ሲጋራ አያጨሱም እንዲሁም አይሰክሩም። ታዲያ ይህ አስጊ ነገር ነው? እነርሱ የሚከተሏቸውን ደንቦች ሌሎች ተግባራዊ እንዲያደርጉ የማያስገድዱ የሌሎችን ነፃነት የሚያከብሩ ክርስቲያኖች ናቸው። ሌሎችን ከማስገደድ ይልቅ በብዙ መስኮች ምሳሌ ሆነው ይገኛሉ። . . . ገንዘብ በማጭበርበር ቅሌትም ሆነ አደገኛ ዕፅ በማዘዋወር ድርጊት እጃቸውን አያስገቡም። መቁረብ አያስፈልጋቸውም፤ ግን ሥነ ምግባራዊ ንጽሕናቸውን ጠብቀው እንደሚኖሩ ላረጋግጥላችሁ እችላለሁ . . .።
“ታዲያ አንተ ራስህ ለምን የይሖዋ ምሥክር አልሆንክም? ብላችሁ እንደምትጠይቁኝ የታወቀ ነው። እኔ ያልሆንኩት ክርስቲያናዊ እምነትና ንጹሕ የሥነ ምግባር አቋም ስለሚያስፈልግ ነው። እነዚህ ደግሞ በብዙዎች ዘንድ እንዲያው በቀላሉ የሚገኙ ነገሮች አይደሉም።”