እውነተኛ ወዳጆች ያስፈልጉናል
ጄኒ እና ሱ ሞቅ ያለ ጭውውት ይዘዋል። በሚነጋገሩበት ጊዜ ፈገግ ይላሉ እንዲሁም ዓይኖቻቸው በርተዋል። ሁኔታቸው ሁሉ እርስ በርስ ለመደማመጥ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው ያሳያል። ምንም እንኳ የተለያየ አስተዳደግ ቢኖራቸውም በጋራ ብዙ ተመሳሳይ ዝንባሌዎች ያሏቸው ከመሆኑም በተጨማሪ እርስ በርስ በጣም ይከባበራሉ።
በሌላ ቦታ የሚኖሩት ኤሪክና ዴኒስ በአንድ ፕሮጄክት ውስጥ አብረው እየሠሩ ሲሆን ከዚህ በፊት ለብዙ ዓመታት በተለያዩ ፕሮጄክቶች ውስጥ አብረው ሠርተዋል። ያለ ችግር የሚግባቡ ሲሆን ሳቅ ይቀናቸዋል። ቁም ነገር ካነሱ የልባቸውን ይጨዋወታሉ። እርስ በርስ ይከባበራሉ። ኤሪክ እና ዴኒስ እንደ ጄኒ እና ሱ እውነተኛ ጓደኛሞች ናቸው።
እነዚህ አገላለጾች ልብህን ሊነኩትና ስለ ጓደኞችህ እንድታስብ ሊያደርጉህ ይችላሉ። ወይም ደግሞ እንዲህ ያሉ ጓደኞች ለመፈለግ ሊያነሳሱህ ይችላሉ። አንተም ብትሆን እንደዚህ ዓይነት ጓደኞች ማግኘት ትችላለህ!
እውነተኛ ጓደኞች የሚያስፈልጉን ለምንድን ነው?
ጥሩ ጓደኝነት ለአእምሮአዊም ሆነ ለአካላዊ ደህንነታችን አስፈላጊ ነው። ብቸኝነት ቢሰማን የሆነ ችግር አለብን ማለት አይደለም። አንዳንድ ተመራማሪዎች የብቸኝነት ስሜት ጓደኛ እንደሚያስፈልገን የሚጠቁም ረሃብ ነው ይላሉ። ያም ሆነ ይህ ምግብ ረሃብን እንደሚያስታግሥ ወይም ጨርሶ እንደሚያጠፋ ሁሉ ጥሩ ጓደኝነትም የሚሰማንን የብቸኝነት ስሜት ሊቀንስ ወይም ሊያጠፋልን ይችላል። ከዚህም በላይ ደግሞ ለእኛ ከፍ ያለ ግምት የሚሰጡ ጥሩ ጓደኞችን ማግኘት ይቻላል።
ሰዎች የተፈጠሩት ጓደኛ እንደሚያስፈልጋቸው ተደርገው ነው። (ዘፍጥረት 2:18) መጽሐፍ ቅዱስ እውነተኛ ጓደኛ ወይም ባልንጀራ “ለመከራ ይወለዳል” ይላል። (ምሳሌ 17:17 አዓት) ስለዚህ ልባዊ ጓደኛሞች አስፈላጊ በሚሆንበት ጊዜ አንዱ የሌላውን እርዳታ መጠየቅ መቻል አለባቸው። ሆኖም ጓደኝነት ማለት በችግር ጊዜ መረዳዳት አለዚያም አብሮ መሥራት ወይም መጫወት ማለት ብቻ አይደለም። ጥሩ ጓደኛሞች ምርጥ ባሕርያትን ለማዳበር እርስ በርስ ይረዳዳሉ። ምሳሌ 27:17 “ብረት ብረትን ይስለዋል፣ ሰውም ባልንጀራውን ይስላል” ይላል። አንድ ብረት እንደ እርሱ ከብረት የተሠራውን ቢላዋ ለመሳል እንደሚያገለግል ሁሉ አንድ ሰው የጓደኛውን የማሰብ ችሎታና መንፈሳዊነት ሊስል ይችላል። ያሰብነው ነገር ባለመሳካቱ ሐዘን በገባን ጊዜ ጓደኛችን ችግራችንን ሲረዳልንና ቅዱስ ጽሑፋዊ ማበረታቻ ሲሰጠን ከጭንቀታችን እንድንላቀቅ በከፍተኛ ሁኔታ ሊረዳን ይችላል።
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጓደኝነት ከፍቅር፣ በደንብ ከመቀራረብ፣ ከምሥጢርና አብሮ ከመሆን ጋር ተያይዞ ተጠቅሷል። በአካባቢያችን ከሚኖሩ ሰዎች፣ ከሥራ ባልደረቦቻችንና እነዚህን ከመሳሰሉ ሌሎች ሰዎች ጋር ጓደኛ መሆን ይቻላል። በተጨማሪም አንዳንዶች ከዘመዶቻቸው መካከል የተወሰኑትን የቅርብ ጓደኞቻቸው አድርገዋቸዋል። ቢሆንም ብዙ ሰዎች እውነተኛ ጓደኛ ማግኘትና በጓደኝነት መቀጠል አስቸጋሪ ሆኖባቸዋል። ይህ የሆነው ለምንድን ነው? እውነተኛና ዘላቂ ወዳጅነት መመሥረት ትችላለህን?