ስለ ትዳር ታስባለህን?
በዓለም ዙሪያ እየተከሰተ ያለውን የትዳር መፍረስ ከአንድ የምድር መናወጥ ጋር ብናወዳድር በነውጡ ይበልጥ እየተመታች ያለችው አገር ዩናይትድ ስቴትስ ሆና እናገኛታለን። በቅርብ ዓመታት በዚህች አገር ከአንድ ሚልዮን የሚበልጥ ትዳር በፍቺ አክትሟል። ይህም በአማካይ በየደቂቃው ሁለት ትዳሮች ይፈርሳሉ ማለት ነው። ይሁን እንጂ በትዳር ውስጥ ችግር የሚከሰትባት አገር ዩናይትድ ስቴትስ ብቻ እንዳልሆነች ታውቅ ይሆናል።
አንድ ጥናት እንዳመለከተው ከ1970 ወዲህ በካናዳ፣ በእንግሊዝና በዌልስ፣ በፈረንሳይ፣ በግሪክ እና በኔዘርላንድስ የፍቺ ቁጥር ከእጥፍ በላይ ጨምሯል።
አብዛኞቹ ወንዶችና ሴቶች የሚጋቡት ስለሚዋደዱና የቀረውን የሕይወት ዘመናቸውን አብረው ለማሳለፍ ስለሚፈልጉ ነው ብለን እንድናምን የሚያደርጉን በርካታ ምክንያቶች አሉ። የሚያሳዝነው ግን ሲያልሙት የነበረው አስደሳች ትዳር እንዲያው ሕልም ብቻ ሆኖ መቅረቱ ነው። ብዙዎቹ ከሕልም ዓለማቸው ሲባንኑ ተቻኩለው ወደ ትዳር ዓለም እንደገቡ ወይም አቻ የሚሆናቸውን ሰው እንዳላገቡ ሲናገሩ ይሰማል።
በርካታ ትዳሮች የሚፈርሱት ለምንድን ነው? ስለ መጠናናት የሚናገር መጽሐፍ የጻፉ አንዲት ሴት “ዋነኛው ምክንያት የዝግጅት ጉድለት ነው” ሲሉ ተናግረዋል። አክለውም “በትዳር ውስጥ በሚፈጠር ችግር ፍዳቸውን እያዩ ያሉ የትዳር ጓደኛሞችን በማነጋግርበት ጊዜ ሁለት ዓይነት ስሜት ማለትም ሐዘንና ንዴት ይመጣብኛል። እርስ በርሳቸው አርኪ የሆነ ግንኙነት እንደሚኖራቸው አድርገው ያሰቡት ሕልም እውን ሳይሆንላቸው መቅረቱ በጣም ያሳዝነኛል። የትዳርን ውስብስብነት ምንም የማያውቁ ደንቆሮ መሆናቸውን ስመለከት ደግሞ በጣም እናደዳለሁ።”
ብዙዎች ትዳር የሚመሠርቱት ትዳርን የተሳካ ማድረግ ስለሚቻልበት መንገድ በጣም ውስን እውቀት ይዘው ወይም ምንም እውቀት ሳይኖራቸው ነው። ሆኖም ይህ ሁኔታ ሊያስገርመን አይገባም። አንድ አስተማሪ እንዲህ ሲሉ የታዘቡትን ተናግረዋል:- “ኮሌጅ ገብተው ስለ አይጥና እንሽላሊት ባሕርይ የሚያጠኑ ነገር ግን ባልና ሚስት ስለሚባሉት ሰዎች ባሕርይ ምንም የማያውቁት ወጣቶቻችን ስንቶቹ ናቸው?”
ወደፊት ትዳር ለመመሥረት በዕቅድ ላይ ያለህም ሆንክ ያገባህ ስለ ትዳር ታስባለህን? የምታስብ ከሆነ እውነተኛ የሕይወት ትስስር በፊልሞች፣ በቴሌቪዥን ፕሮግራሞችና ስለ ፍቅር በሚያወሩ ልብ ወለድ መጻሕፍት ከሚቀርበው ፈጽሞ የተለየ እንደሆነ መገንዘብ ይኖርብሃል። ቢሆንም ግን ከልብ የሚዋደዱ ሁለት የጎለመሱ ሰዎች የሚመሠርቱት ትዳር ከአምላክ የተገኘ በረከት እንደሆነ ተደርጎ ሊቆጠር ይችላል። (ምሳሌ 18:22፤ 19:14) ታዲያ ትዳር የሚጠይቃቸውን ነገሮች ለማሟላት ዝግጁ መሆንህን ማረጋገጥ የምትችለው እንዴት ነው? የትዳር ጓደኛ በምትመርጥበት ጊዜ ምን ነገሮችን ግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርብሃል? ወይም ያገባህ ከሆንክ ደግሞ በትዳርህ ይበልጥ ዘላቂ ደስታ ማግኘት የምትችለው እንዴት ነው?