“ነቅታችሁ ጠብቁ”
1 ኢየሱስ በማቴዎስ 26:38–41 [አዓት ] ላይ የተመዘገቡትን ቃላት ሲናገር ሰው ሆኖ ከኖረባቸው ጊዜያት ሁሉ ይበልጥ አሳሳቢ የሆነው ጊዜ እየተቃረበ ነበር። በመላው የሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ከሁሉ የበለጠ ዋጋ ያለው ጊዜ መሆኑ የሚታይበት ወቅት ነበር። የመላው የሰው ዘር ደህንነት በዚያ ወቅት በሚፈጸመው ነገር ላይ የተመካ ነበር። የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት ‘ነቅተው መጠበቅ’ አስፈልጓቸው ነበር።
2 ዛሬ ኢየሱስ አዳኝና ፍርድ አስፈጻሚ በመሆን ጣምራ ሚና ለመጫወት የሚመጣበት ጊዜ በጣም በቀረበበት ወቅት ላይ እንገኛለን። ንቁ ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን የጊዜውን አጣዳፊነት ስለምንገነዘብ እጃችንን አጣጥፈን መዳናችንን አንጠባበቅም። በማንኛውም ጊዜ ዝግጁ መሆን እንዳለብን እናውቃለን። ለይሖዋ በምናቀርበው አገልግሎት ዘወትር ‘ጠንክረን መሥራትና የምንችለውን ሁሉ ለማድረግ መጣር’ ያስፈልገናል። (1 ጢሞ. 4:10 አዓት) በግለሰብ ደረጃስ ስለ እያንዳንዳችን ምን ለማለት ይቻላል? ነቅተን በመጠበቅ ላይ እንገኛለንን?
3 ራሳችንን መመርመር፦ “ለራሳችሁ ተጠንቀቁ” በማለት ኢየሱስ ተጨማሪ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል። (ሉቃስ 21:34, 35) ምንጊዜም ‘በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል ነቀፋና ነውር የሌለብን’ ሆነን በመመላለስ ለራሳችን መጠንቀቅ አለብን። (ፊልጵ. 2:14, 15) ኢየሱስን በመምሰልና በአምላክ ቃል ውስጥ ካሉት መሠረታዊ ሥርዓቶች ጋር ተስማምተን በመመላለስ በየዕለቱ ከአንድ ክርስቲያን የሚጠበቀውን ነገር እያደረግን እንኖራለንን? ‘በክፉው የተያዘው’ ዓለም የሚያንጸባርቀውን ክርስቲያናዊ ያልሆነ ጠባይ ማስወገድ አለብን። (1 ዮሐ. 5:19፤ ሮሜ 13:11–14) በቅዱሳን ጽሑፎች አማካኝነት ራሳችንን ስንመረምር በእርግጥ ኢየሱስ እንዳዘዘው ንቁዎች ነንን?
4 ሽማግሌዎች መንጋውን በምን መንገድ እንደያዙት ስሌት እንደሚያቀርቡ በመገንዘብ በጉባኤ ውስጥ ያሏቸውን ሥራዎች በትጋት ለማከናውን ንቁዎች መሆን አለባቸው። (ዕብ. 13:17) የቤተሰብ ራሶች ቤተሰባቸውን በይሖዋ መንገዶች በመምራት ረገድ ልዩ ግዴታ አለባቸው። (ዘፍ. 18:19፤ ኢያሱ 24:15፤ ከ1 ጢሞ. 3:4, 5 ጋር አወዳድር።) በተጨማሪም እርስ በርሳችን እንድንዋደድ የተሰጠንን ቅዱስ ጽሑፋዊ ትእዛዝ ሁላችንም በተግባር ማዋላችን ምን ያህል አስፈላጊ ነው! ይህ የእውነተኛ ክርስትና ምልክት ነው።— ዮሐ. 13:35
5 ሌሎችን ለማስጠንቀቅ ንቁ ሁኑ፦ ነቅቶ መጠባበቅ ማለት ለራሳችን መጠንቀቅ ማለት ብቻ አይደለም። ሌሎችን ደቀ መዛሙርት የማድረግ ተልዕኮ አለን። (ማቴ. 28:19, 20) ለሰዎች ያለን ፍቅር በዚህ ዓለም ፊት ከተደቀነው ጥፋት መትረፍ ይችሉ ዘንድ እንድናስጠነቅቃቸው ሊገፋፋን ይገባል። ይህ ሁሉም ክርስቲያኖች ያለባቸው ኃላፊነት ነው። የአምልኮታችን ወሳኝ ክፍል ነው። (ሮሜ 10:9, 10፤ 1 ቆሮ. 9:16) በዚህ ሕይወት አድን ሥራ ስንካፈል ብዙውን ጊዜ ግዴለሽነት ወይም ቀጥተኛ ተቃውሞ ያጋጥመናል። አብዛኞቹ ሰዎች ማስጠንቀቂያችንን ጆሮ ዳባ ልበስ ቢሉትም እንኳ በሥራችን የመቀጠል ግዴታ አለብን። (ሕዝ. 33:8, 9) ለአምላክና ለሰዎች ያለን ልባዊ ፍቅር በሥራችን ጸንተን ወደፊት እንድንገፋ ያስችለናል።
6 ራሳችንን ዘና የምናደርግበት ጊዜ አይደለም። የዕለት ተዕለት የኑሮ ጭንቀቶች ሐሳባችንን እንዲከፋፍሉት መፍቀድም ሆነ ወጥመድ ሊሆንብን በሚችለው ይህ ሥርዓት በሚያስገኘው ደስታ እጅግ መዋጥ የለብንም። (ሉቃስ 21:34, 35) ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ አጣዳፊ በሆነ ዘመን ላይ እንገኛለን። ጊዜው ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ክፉ ሥርዓት ላይ የቅጣት እርምጃ ወደሚወስድበት ወቅት እየገሰገሰ ነው። ንቁና ዝግጁ ሆነው የሚጠባበቁ ብቻ በሕይወት ይተርፋሉ። የኢየሱስን መመሪያዎች ከታዘዝንና “ከዚህ ሁሉ ለማምለጥ” ከቻልን ምንኛ እንደሰት ይሆን!— ሉቃስ 21:36