የጥያቄ ሣጥን
◼ ስብሰባዎቻችን የሚያንጹ እንዲሆኑ በበኩላችን ምን ማድረግ እንችላለን?
የጉባኤ ስብሰባዎችን የሚመሩና አብዛኞቹን ክፍሎች የሚያቀርቡት ሽማግሌዎችና የጉባኤ አገልጋዮች ስለሆኑ ስብሰባዎቹ ውጤታማ እንዲሆኑ ማድረግ የእነሱ ብቻ ኃላፊነት እንደሆነ አንዳንዶች ሊሰማቸው ይችላል። እውነታው ግን ሁላችንም ስብሰባዎች ጠቃሚ እንዲሆኑ የበኩላችንን አስተዋጽኦ ማድረግ እንችላለን። ስብሰባዎች የሚያንጹ እንዲሆኑ በሚከተሉት አሥር መንገዶች የበኩላችንን ድጋፍ ልንሰጥ እንችላለን:-
አስቀድሞ በመዘጋጀት። በደንብ ከተዘጋጀን ስብሰባዎች አስደሳች ይሆኑልናል። ሁላችንም ይህንን ስናደርግ ስብሰባዎች የሚያነቃቁና የበለጠ የሚያንጹ ይሆናሉ። አዘውትሮ በመሰብሰብ። ከፍተኛ የተሰብሳቢ ቁጥር መኖሩ በስብሰባው ለተገኘነው ሁሉ የሚያንጽና በስብሰባ ስለ መገኘት ያለን አድናቆት ከፍ እንዲል ያደርጋል። በሰዓቱ በመድረስ። ፕሮግራሙ ከመጀመሩ በፊት ከደረስን በመክፈቻ መዝሙር እና ጸሎት ላይ ስለምንካፈል ከስብሰባው ሙሉ በሙሉ እንጠቀማለን። የሚያስፈልጉትን ጽሑፎች ሁሉ ይዞ በመምጣት። መጽሐፍ ቅዱሳችንንና በስብሰባው ጊዜ የምንጠቀምባቸውን ጽሑፎች ይዘን በመምጣት እየተሰጠ ያለውን ትምህርት ለመከታተልና በደንብ ለመረዳት እንችላለን። ሐሳብ የሚከፋፍሉ ነገሮችን ባለማድረግ። ፊት ከተቀመጥን ይበልጥ በጥሞና ማዳመጥ እንችላለን። ማንሾካሾክና አሁንም አሁንም ወደ መጸዳጃ ቤት መመላለስ የእኛንም ሆነ የሌሎችን ሐሳብ ይሰርቃል። ተሳትፎ በማድረግ አብዛኞቻችን እጃችንን አውጥተን ሐሳብ በምንሰጥበት ጊዜ እምነታችንን ስለምንገልጽ ብዙዎቹ ይበረታታሉ እንዲሁም ይታነጻሉ። አጠር ያለ ሐሳብ በመስጠት። አጠር ያለ ሐሳብ መስጠታችን ሌሎችም እንዲሳተፉ እድል ይሰጣል። የምንሰጠው አጠር ያለ ሐሳብ ከሚጠናው ርዕስ መውጣት የለበትም። የተሰጠንን ክፍል ተዘጋጅተን በመምጣትና በማቅረብ። በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ክፍል ሲኖረን ወይም በአገልግሎት ስብሰባ ላይ እንደ ሠርቶ ማሳያ የመሰለ ክፍል ሲሰጠን በደንብ እንዘጋጅ፣ አስቀድመን እንለማመድ እንዲሁም ተገኝተን ለማቅረብ እንጣር። ክፍል ያቀረቡትን በማመስገን። ጥረታቸው ምን ያህል የሚደነቅ እንደሆነ እንንገራቸው። እንዲህ ማድረጋችን ያንጻቸዋል እንዲሁም ለወደፊቱ የበለጠ እንዲሠሩ ያበረታታቸዋል። እርስ በርስ በመተናነጽ። ከስብሰባዎች በኋላና በፊት ደግነት የተሞላበት ሰላምታና የሚያንጽ ንግግር ስብሰባዎች ላይ በመካፈል የምናገኘውን ደስታና ጥቅም እንዲጨምር ያደርጋሉ።