የሌሎችን እርዳታ ጠይቁ
1 በመንፈስ አነሳሽነት የተጻፈው ‘አስጨናቂ’ የሚለው ቃል ያለንበትን የመጨረሻ ዘመን በትክክል ይገልጻል። (2 ጢሞ. 3:1) ስለሆነም ከአቅማችሁ በላይ እንደሆነ የሚሰማችሁ ፈታኝ መንፈሳዊ ችግር ሲያጋጥማችሁ ምን ማድረግ ትችላላችሁ?
2 በመንፈሳዊ የጎለመሱ የጉባኤ አባላትን ለማማከር ፈቃደኛ ናችሁ? አንዳንዶች እፍረት ስለሚሰማቸው፣ ሌሎችን ማስቸገር ስለማይፈልጉ ወይም በእርግጥ ሊረዳቸው የሚችል ሰው ማግኘታቸውን ስለሚጠራጠሩ እርዳታ ለመጠየቅ ያመነቱ ይሆናል። በተቻለ መጠን የራሳችንን ኃላፊነት ራሳችን ለመወጣት መጣር እንዳለብን የታወቀ ነው፤ ይሁን እንጂ መንፈሳዊ ደህንነታችንን የሚነኩ ጉዳዮችን በተመለከተ የሌሎችን እርዳታ ለመጠየቅ ምንጊዜም ነፃነት ሊሰማን ይገባል።—ገላ. 6:2, 5
3 መጀመሪያ ልታደርግ የምትችለው ነገር:- የጉባኤ የመጽሐፍ ጥናት መሪህን ቀርበህ መስክ አገልግሎት አብረኸው ማገልገል ትችል እንደሆነ ለመጠየቅ ትፈልግ ይሆናል። አብራችሁ ስታገለግሉ በመንፈሳዊ ለማደግ ያለህን ፍላጎት ለመንገር አጋጣሚ ታገኛለህ። የጉባኤ አገልጋይ ከሆነ መንፈሳዊ እርዳታ እንደሚያስፈልግህ ንገረውና ሽማግሌዎች እንዲረዱህ ይጠይቅልሃል። ወይም አንተው ራስህ ከሽማግሌዎች መካከል ወደ አንዱ ቀርበህ ስለሚያሳስቡህ ነገሮች ልታነጋግረው ትችላለህ።
4 ምን ዓይነት እርዳታ ያስፈልግሃል? በሆነ ምክንያት ቅንዓትህ ቀዝቅዞአል? ልጆችህ ከጉባኤ ጋር ያላቸውን ቅርርብ እንዳያቋርጡ ጥረት በማድረግ ላይ ያለህ ነጠላ ወላጅ ነህን? እርዳታ የሚያስፈልግህ በዕድሜ የገፋህ ሰው ነህን? ወይስ አንድ ችግር ተስፋ እንድትቆርጥ እያደረገህ ነው? ያለንበት የመጨረሻው ዘመን የሚያስከትልብንን ችግሮች መቋቋም ቀላል ላይሆን ይችላል፤ ጨርሶ መወጣት የማይቻል ግን አይደለም። አስፈላጊውን እርዳታ ማግኘት ትችላላችሁ።
5 ሽማግሌዎች የሚያበረክቱት እርዳታ:- ሽማግሌዎች ከልብ ያስቡልናል። ስለሚያሳስባችሁ ነገሮች ስትነግሯቸው ያዳምጣሉ። ሌሎች አስፋፊዎችም ተመሳሳይ ችግር የሚያጋጥማቸው ከሆነ ሽማግሌዎች እረኝነት በሚያደርጉበትም ሆነ ለጉባኤ ትምህርት በሚሰጡበት ጊዜ ይህን ግምት ውስጥ ያስገባሉ። “ለመንጋው ምሳሌ” እንደመሆናቸው መጠን በደስታ ከጎናችሁ ሆነው ለመሥራት ምንጊዜም ዝግጁ ናቸው። (1 ጴጥ. 5:3) እነዚህ ተሞክሮ ያላቸው ወንድሞች የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች በምክንያት ሲያስረዱ ማዳመጥ የምታቀርቡትን አገልግሎት ሊያሻሽልላችሁ እንዲሁም በግል ሕይወታችሁ እገዛ ሊሰጣችሁ ይችላል።—2 ጢሞ. 3:16, 17
6 ኢየሱስ ብዙ “ወንዶችን ስጦታ” አድርጎ ሰጥቶናል። (ኤፌ. 4:8 የአዲሲቱ ዓለም ትርጉም የግርጌ ማስታወሻ) ይህም ሽማግሌዎች ሊረዱን ዝግጁ ናቸው ማለት ነው። እናንተን ለመርዳት ዝግጁ ናቸው። ሽማግሌዎች ‘የእናንተ ናቸው።’ (1 ቆሮ. 3:21-23) ከምታመነቱ ደፍራችሁ ተናገሩ። እርዳታ ካስፈለጋችሁ ጠይቁ።