የጥያቄ ሣጥን
◼ አንድ ተናጋሪ አድማጮቹ ጥቅስ እንዲያወጡ በሚጋብዝበት ጊዜ ጥቅሱን አውጥቶ መከታተል ጠቃሚ የሆነው ለምንድን ነው?
አድማጮች አውጥተው እንዲከታተሉ የሚጋበዙትን ጥቅስ ብዛት የሚወስነው የንግግሩ ርዕሰ ጉዳይ እንዲሁም ንግግሩ የተወሰነ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ቁጥር በቁጥር የሚያብራራ መሆን አለመሆኑ ነው።
ጥቅስ የሚነበብበት አንደኛው ምክንያት እየተነገረ ያለው ነገር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኝ ስለመሆኑ ማረጋገጫ ለመስጠት እንደሆነ ልብ ማለት ያስፈልጋል። (ሥራ 17:11) ሌላው ዓላማ የአድማጮች እምነት ይገነባ ዘንድ ለትምህርቱ ቅዱስ ጽሑፋዊ ማስረጃዎችን ማቅረብ ነው። አንድ ቁልፍ ጥቅስ በሚነበብበት ጊዜ በቀጥታ መጽሐፍ ቅዱስ ምን እንደሚል መከታተል ትምህርቱ እንዳይረሳ ያደርጋል። ጥቅሶች ሲነበቡ አውጥቶ ከመከታተል በተጨማሪ ማስታወሻ መያዝና ሐሳቦቹ በቅደም ተከተል ሲቀመጡ በትኩረት መከታተል ጥቅም አለው።
ማኅበሩ የሚያዘጋጀው የንግግር አስተዋጽዖ አንድን ርዕሰ ጉዳይ የሚያዳብሩ ብዙ ጥቅሶች ሊኖሩት ቢችሉም ተናጋሪው ንግግሩን በሚዘጋጅበት ጊዜ እንዲረዱት ታስበው የሚቀርቡ ናቸው። ንግግር ስለሚሰጥበት ርዕሰ ጉዳይ የተሟላ ግንዛቤ እንዲኖረው ወይም ተናጋሪው ከበስተ ጀርባ ያሉት ቅዱስ ጽሑፋዊ መሠረታዊ ሥርዓቶች ቁልጭ ብለው እንዲታዩትና ርዕሱ እንዴት እንደተብራራ እንዲያስተውል ይረዱታል። ንግግሩን ለማብራራት የትኞቹን ጥቅሶች እንደሚጠቀም የሚወስነው ተናጋሪው ሲሆን የመረጣቸውን ጥቅሶች ሲያነብና ሲያብራራ አውጥተው እንዲከታተሉት አድማጮቹን ይጋብዛል። ተጨማሪ መረጃ ለመስጠት ሲባል የገቡትን ጥቅሶች በቃሉ መናገር ወይም በራሱ አባባል መግለጽ ይችላል። ሆኖም በዚህ ጊዜ አድማጮች የግድ አውጥተው መከታተል አለባቸው ማለት አይሆንም።
ተናጋሪው የመረጣቸውን ጥቅሶች በኮምፒዩተር አትሞ ወይም በእጅ ጽፎ ከወረቀት ላይ ከማንበብ ይልቅ በቀጥታ ከመጽሐፍ ቅዱስ ማንበብ ይኖርበታል። አድማጮች ጥቅስ አውጥተው እንዲከታተሉት በሚጋብዝበት ጊዜ ጥቅሱ የሚገኝበትን መጽሐፍ፣ ምዕራፍና ቁጥር (ቁጥሮች) በግልጽ መናገር አለበት። ጥቅሱ የሚነበብበትን ዓላማ ግልጽ ለማድረግ የሚረዳ ጥያቄ በማንሳት ወይም አጠር ያለ ሐሳብ በመስጠት አድማጮች ጥቅሱን ለማውጣት ጊዜ እንዲያገኙ ማድረግ ይችላል። ጥቅሱን ደግሞ መናገሩ አድማጮች ቦታውን ቶሎ እንዲያገኙ ይረዳቸዋል። ይሁን እንጂ አድማጮች የሚይዙት የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ሊለያይ ስለሚችል ገጹን መናገር አስፈላጊ አይደለም። ጥቅስ እንድናወጣ ስንጋበዝ አውጥተን መከታተላችን በንግግሩ አማካኝነት የሚብራራው የአምላክ ቃል ካለው ኃይል እንድንጠቀም ይረዳናል።—ዕብ. 4:12