የጥያቄ ሣጥን (1)
◼ ጉባኤውን በገንዘብ ለመደጎም ሲባል አንዳንድ የገቢ ማሰባሰቢያ ዝግጅቶች ማድረግ ተገቢ ነው?
የእራት ግብዣ በማድረግ፣ አንዳንድ ዕቃዎችን ለጨረታ በማቅረብ፣ ፌስቲቫሎችን በማዘጋጀት ወይም በሌሎች የገቢ ማሰባሰቢያ ዘዴዎች አማካኝነት እርዳታ መሰብሰብ በብዙ ሃይማኖታዊ ድርጅቶች ውስጥ የተለመደ ነው። ምናልባት አንዳንዶች ይህን የሚያደርጉት ለበጎ ዓላማ እንደሆነ ቢሰማቸውም ድርጊቱ ከልመና ተለይቶ የሚታይ አይደለም። የይሖዋ ምሥክሮች የገንዘብ እርዳታ ማግኘት የሚፈልጉት በዚህ መንገድ አይደለም።
በነሐሴ 1879 የወጣው የመጠበቂያ ግንብ መጽሔት ሁለተኛ እትም አብያተ ክርስቲያናት ገንዘብ ለማሰባሰብ የሚጠቀሙበትን ዘዴ የማንኮርጅበትን ምክንያት ሲናገር እንዲህ ብሏል:- “‘የጽዮን መጠበቂያ ግንብ’ ደጋፊ ይሖዋ ራሱ እንደሆነ እናምናለን። ይህ በመሆኑም ከሰዎች ድጋፍ ለማግኘት በፍጹም አይለምንም ወይም አይማጠንም። ‘የተራሮች ወርቅና ብር ሁሉ የእኔ ነው’ የሚለው አምላክ የሚያስፈልገንን ገንዘብ ማስገኘት ካቃተው ያን ጊዜ መጽሔቱን ማተም ማቆም እንደሚኖርብን እናውቃለን።”
ዛሬም ቢሆን “እያንዳንዱ ሰው በቅሬታ ወይም በግዴታ ሳይሆን፣ በልቡ ያሰበውን ያህል ይስጥ፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር በደስታ የሚሰጠውን ሰው ይወዳል” የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓት መከተላችንን እንቀጥላለን። (2 ቆሮ. 9:7) ሰዎች በፈቃደኝነት ተነሳስተው ገንዘብ መለገስ እንዲችሉ የመዋጮ ሣጥኖች በመንግሥት አዳራሾች ውስጥ ይቀመጣሉ። (2 ነገ. 12:9) የመዋጮ ዝግጅት ልመና አይደለም፤ ሰጪውም ቢሆን በምላሹ አንድ ነገር አገኛለሁ በሚል ስሜት ሊያደርገው አይገባም።
የጥያቄ ሣጥን (2)
◼ ከአገልግሎታችን ጋር በተያያዘ ከተቃራኒ ጾታ ጋር በምንሆንበት ጊዜ ምን ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልገናል?
ወንድሞቻችንና እህቶቻችን በአኗኗራቸው ከፍተኛ የሥነ ምግባር ደረጃን በጥብቅ ይከተላሉ ብለን የምንጠብቅበት በቂ ምክንያት አለን። ሆኖም የምንኖረው ርኩስና በሥነ ምግባር ልቅ በሆነ ዓለም ውስጥ ነው። ጥሩ ዓላማ ያለን ቢሆንም እንኳ ነቀፋ የሚያመጣ ነገር ከማድረግ ወይም ተገቢ ባልሆነ ድርጊት ከመካፈል እንድንርቅ ዘወትር ጠንቃቆች መሆን አለብን። ይህም አገልግሎት በምንወጣበት ጊዜ ጥንቃቄ ማድረግንም ይጨምራል።
በመስክ አገልግሎት ላይ ለእውነት ልባዊ ፍላጎት ያላቸው የሚመስሉ ተቃራኒ ጾታ ያላቸው ሰዎች ዘወትር እናገኛለን። ብቻችንን ከቤት ወደ ቤት ስናገለግል በሩን ከከፈተልን ተቃራኒ ጾታ ካለው ሰው በቀር በቤት ውስጥ ሌላ ማንም ሰው ከሌለ ብዙውን ጊዜ ወደ ውስጥ ዘልቀን ከመግባት ይልቅ በር ላይ ሆነን ምሥክርነቱን ብንሰጥ የተሻለ ይሆናል። ያነጋገርነው ሰው ፍላጎት ካሳየ ሌላ አስፋፊ ይዘን ወይም ቤት ውስጥ ሌላ ሰው በሚኖርበት ጊዜ ተመላልሶ መጠየቅ ለማድረግ እንችላለን። ይህም የማይሆን ከሆነ ተመሳሳይ ጾታ ያለው ሌላ አስፋፊ ተመላልሶ መጠየቅ ቢያደርግለት የጥበብ እርምጃ ይሆናል። ተቃራኒ ጾታ ያለውን ሰው መጽሐፍ ቅዱስ ማስጠናትንም በተመለከተ ተመሳሳይ እርምጃ መውሰድ ይኖርብናል።—ማቴ. 10:16
አብሮን የሚያገለግል ሰው በምንመርጥበትም ጊዜ ጠንቃቆች መሆን ያስፈልገናል። አልፎ አልፎ ተቃራኒ ጾታ ካላቸው አስፋፊዎች ጋር አብሮ ማገልገል የሚቻል ቢሆንም እንዲህ የምናደርገው የቡድን ምሥክርነት በሚሰጥበት ጊዜ ቢሆን ይመረጣል። በመሠረቱ በአገልግሎት ላይም ቢሆን የትዳር ጓደኛችን ካልሆነ ሰው ጋር ለብቻችን ረዘም ያለ ጊዜ ማሳለፉ ጥበብ አይደለም። ስለዚህ የአገልግሎት ቡድኑን የሚመራው ወንድም በአሥራዎቹ ዕድሜ ላይ የሚገኙ ወጣቶችን ጨምሮ አስፋፊዎችን ለአገልግሎት በሚመድብበት ጊዜ ጥሩ የማመዛዘን ችሎታ መጠቀም ይኖርበታል።
ዘወትር ጥሩ የማመዛዘን ችሎታ በመጠቀም ለራሳችንም ሆነ ለሌሎች ‘ዕንቅፋት ላለመሆን’ እንጠነቀቃለን።—2 ቆሮ. 6:3
ከግንቦት 1997 የመንግሥት አገልግሎታችን ላይ የተወሰደ