የጥያቄ ሣጥን
◼ በኢንተርኔት አማካኝነት ከማናውቀው ሰው ጋር ግንኙነት መመሥረት ምን አደጋዎች አሉት?
ሰዎች በኢንተርኔት አማካኝነት እንዲተዋወቁና እርስ በርስ መልእክት እንዲለዋወጡ ለማድረግ ታስበው የሚዘጋጁ በርካታ ድረ ገጾች አሉ። ከእነዚህ ድረ ገጾች መካከል ብዙዎቹ፣ የግለሰቦችን ፎቶግራፎች ጨምሮ ስለ እነሱ የሚናገሩ ሌሎች የግል መረጃዎችን ለማስቀመጥ የሚያስችሉ ናቸው። የግለሰቡን ድረ ገጽ የሚመለከቱ ሰዎች ከእሱ ጋር ግንኙነት መጀመር ይችላሉ። እንዲህ ዓይነቶቹ ድረ ገጾች በወጣቶች ዘንድ በጣም የተለመዱ ሲሆኑ የይሖዋ ምሥክር የሆኑ አንዳንድ ወጣቶችም የይሖዋ ምሥክር እንደሆኑ ከሚናገሩ ሰዎች ጋር ግንኙነት ለመመሥረት በእነዚህ ድረ ገጾች ተጠቅመዋል።
በኢንተርኔት የተዋወቅነው ሰው ማንነቱን፣ መንፈሳዊነቱንና ውስጣዊ ግፊቶቹን በተመለከተ ትክክል ያልሆኑ ሐሳቦችን መናገር ላይከብደው ይችላል። (መዝ. 26:4 NW) የይሖዋ ምሥክር እንደሆነ የሚናገረው ግለሰብ ምናልባትም የማያምን ወይም ደግሞ የተወገደ አልፎ ተርፎም የለየለት ከሃዲ ሊሆን ይችላል። (ገላ. 2:4) ሕፃናትን የሚያስነውሩ በርካታ ግለሰቦች ሰለባዎቻቸውን የሚያጠምዱት እነዚህን ድረ ገጾች ተጠቅመው እንደሆነ ይነገራል።
መልእክት የምንለዋወጣቸው ሰዎች በጉባኤ ውስጥ ጥሩ አቋም እንዳላቸው እርግጠኞች ብንሆንም እንኳ በዚህ መልክ የምናደርገው የሐሳብ ልውውጥ በቀላሉ አቅጣጫውን ሊስት ይችላል። ይህ የሚሆነው ሰዎች በአካል ከማያውቁት ሰው ጋር እንደ ልብ ማውራት ስለሚቀናቸው ነው። በተጨማሪም እነዚህ ሰዎች በኢንተርኔት የሚያደርጉት የመልእክት ልውውጥ ሌላ ሰው ጆሮ እንደማይደርስና ምንም ነገር ቢጽፉ ወላጆቻቸውም ሆኑ ሽማግሌዎች እንደማያውቁባቸው ይሰማቸዋል። የሚያሳዝነው ግን ክርስቲያን ወላጆች ያሏቸው በርካታ ወጣቶች በዚህ ወጥመድ የተያዙ ሲሆን አሳፋሪ ንግግር መናገርም ጀምረዋል። (ኤፌ. 5:3, 4፤ ቈላ. 3:8) ሌሎች ደግሞ በግል ድረ ገጻቸው ውስጥ የጾታ ፍላጎትን የሚያነሳሱ ፎቶግራፎቻቸውን አስገብተዋል፣ ስሜትን የሚቀሰቅሱ ቅጽል ስሞችን ተጠቅመዋል አሊያም የጾታ ግንኙነትን በግልጽ የሚያሳዩ የሙዚቃ ቪዲዮዎችን አካትተዋል።
ከላይ በተጠቀሰው ሁኔታ የተነሳ ወላጆች የልጆቻቸውን የኮምፒውተር አጠቃቀም መቆጣጠር ይኖርባቸዋል። (ምሳሌ 29:15) አንድ የማናውቀውን ሰው ወደ ቤታችን መጋበዝ አሊያም ልጆቻችንን ከእሱ ጋር ትተን መሄድ አደገኛ ሊሆን ይችላል። በተመሳሳይም የይሖዋ ምሥክሮች እንደሆኑ ቢናገሩም እንኳ በኢንተርኔት አማካኝነት ከማናውቃቸው ሰዎች ጋር ጓደኝነት መመሥረት ለእኛም ሆነ ለልጆቻችን አደገኛ ነው።—ምሳሌ 22:3