አረጋውያን—ለጉባኤው ውድ ሀብት ናችሁ
“መለስ ብዬ ሳስበው፣ ወጣት ሳለሁ ባከናወንኳቸው ነገሮች እደነቃለሁ። አሁን ግን በዕድሜዬ ምክንያት ብዙ ነገር ማድረግ አልችልም።”—ኮኒ፣ 83 ዓመት
ምናልባት እናንተም ዕድሜያችሁ በመግፋቱ ብዙ ነገር ማድረግ አትችሉ ይሆናል። ይሖዋን ለበርካታ ዓመታት በታማኝነት ብታገለግሉም አሁን ባሉባችሁ የአቅም ገደቦች የተነሳ አፍራሽ ስሜቶች ሊያድሩባችሁ ይችላሉ። ለምሳሌ በአሁኑ ወቅት የምታከናውኑትን ነገር በፊት ታከናውኑ ከነበረው ነገር ጋር ታወዳድሩ ይሆናል። ታዲያ እንዲህ ዓይነቱን አስተሳሰብ ማሸነፍ የምትችሉት እንዴት ነው?
ይሖዋ ከእናንተ የሚጠብቀው ምንድን ነው?
‘ይሖዋ ከእኔ የሚጠብቀው ምንድን ነው?’ ብላችሁ ራሳችሁን ጠይቁ። በዘዳግም 6:5 ላይ የሚገኘው ሐሳብ ሊያጽናናችሁ ይችላል፤ ጥቅሱ “አንተም አምላክህን ይሖዋን በሙሉ ልብህ፣ በሙሉ ነፍስህና በሙሉ ኃይልህ ውደድ” ይላል።
በዚህ ጥቅስ መሠረት ይሖዋ የሚጠብቅባችሁ በሙሉ ልባችሁ፣ በሙሉ ነፍሳችሁና በሙሉ ኃይላችሁ እንድታገለግሉት ነው። ይህን መገንዘባችሁ ራሳችሁን ከሌሎች ጋር ከማወዳደር እንድትቆጠቡ እንዲሁም አሁን የምታከናውኑትን ነገር ከቀድሞው ጋር እንዳታወዳድሩ ይረዳችኋል።
ወጣት ሳላችሁ በወቅቱ ከነበራችሁበት ሁኔታ አንጻር ለይሖዋ ምርጣችሁን ሰጥታችሁት እንደሚሆን የታወቀ ነው። አሁን ደግሞ ሁኔታችሁ ቢቀየርም ካላችሁበት ሁኔታ አንጻር አቅማችሁ የፈቀደውን እያደረጋችሁ እንደሆነ ጥርጥር የለውም። በዚህ መንገድ ካሰባችሁት፣ በፊት ታቀርቡ የነበረው አገልግሎት ከአሁኑ ጋር ተመሳሳይ ነው ሊባል ይችላል። ያኔም ለይሖዋ ምርጣችሁን ትሰጡ ነበር፤ አሁንም ለይሖዋ ምርጣችሁን እየሰጣችሁ ነው።
በወጣትነታችሁ ለይሖዋ ምርጣችሁን ትሰጡ ነበር፤ አሁንም ዕድሜያችሁ ቢገፋም ምርጣችሁን እየሰጣችሁ ነው
ተሞክሯችሁ ሌሎችን በእጅጉ ይጠቅማል
ሌላም ነጥብ ደግሞ እናንሳ፦ በዕድሜ መግፋታችሁ ባሳጣችሁ ነገር ላይ ሳይሆን በከፈተላችሁ አጋጣሚ ላይ ለማተኮር ጥረት አድርጉ። በእርግጥም፣ ወጣት ሳላችሁ ማድረግ የማትችሏቸውን አንዳንድ ነገሮች አሁን ማድረግ ትችላላችሁ። ለምሳሌ ምን ማድረግ ትችላላችሁ?
ተሞክሯችሁን ለሌሎች አካፍሉ። የሚከተሉትን ጥቅሶች ልብ በሉ፦
ንጉሥ ዳዊት እንዲህ ብሏል፦ “በአንድ ወቅት ወጣት ነበርኩ፤ አሁን ግን አርጅቻለሁ፤ ይሁንና ጻድቅ ሰው ሲጣል፣ ልጆቹም ምግብ ሲለምኑ አላየሁም።”—መዝ. 37:25
ኢያሱ ደግሞ እንዲህ ብሏል፦ “እንግዲህ እኔ መሞቻዬ ተቃርቧል፤ አምላካችሁ ይሖዋ ከገባላችሁ መልካም ቃል ሁሉ አንዲቷም እንኳ ሳትፈጸም እንዳልቀረች በሙሉ ልባችሁና በሙሉ ነፍሳችሁ ታውቃላችሁ። ሁሉም ተፈጽሞላችኋል። ከመካከላቸው ሳይፈጸም የቀረ አንድም ቃል የለም።”—ኢያሱ 23:14
እናንተም ተመሳሳይ ሐሳብ ተናግራችሁ ታውቁ ይሆናል። ዳዊትና ኢያሱ እነዚህን ሐሳቦች የተናገሩት ከግል ተሞክሯቸው ተነስተው ነው። እነዚህ ታማኝ የይሖዋ አገልጋዮች ለበርካታ አሥርተ ዓመታት ያዩትንና የሰሙትን ነገር መሠረት አድርገው ስለተናገሩ ንግግራቸው ይበልጥ ክብደት ሊኖረው ችሏል።
እናንተም ይሖዋን ለበርካታ ዓመታት አገልግላችሁ ከሆነ ይሖዋን ማገልገል የሚያስገኘውን በረከት ከተሞክሯችሁ በመነሳት መናገር ትችላላችሁ። ይሖዋ ሕዝቡን ለየት ባለ መንገድ ሲባርክ ያያችሁበት ጊዜ ትዝ ይላችኋል? ይህን ተሞክሮ ለሌሎች ንገሯቸው። እንዲህ ያለው ተሞክሮ የሌሎችን መንፈስ ሊያድስ ይችላል፤ እናንተም ይህን በሕይወታችሁ አይታችሁ መሆን አለበት። በይሖዋ አገልግሎት ያገኛችኋቸውን ተሞክሮዎች ለሌሎች ስታካፍሉ ለእነሱ የብርታት ምንጭ ትሆናላችሁ።—ሮም 1:11, 12
ሌሎችን ማበረታታት የምትችሉበት ሌላው መንገድ አቅማችሁ በፈቀደ መጠን በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ በአካል በመገኘት ነው። እንዲህ ማድረጋችሁ ለእናንተም ሆነ ለእምነት አጋሮቻችሁ ጥቅም ያስገኛል። ቀደም ሲል የተጠቀሱት እህት ኮኒ እንዲህ ብለዋል፦ “በስብሰባዎች ላይ በአካል መገኘቴ ተስፋ እንዳልቆርጥ ይረዳኛል። በስብሰባ ላይ የሚገኙት ወንድሞቼና እህቶቼ እንዲህ ያለ ፍቅር እያሳዩኝ እንዴት ተስፋ ልቆርጥ እችላለሁ? እኔም ትናንሽ ስጦታዎችን ለሌሎች በመስጠት አድናቆቴን ለመግለጽ እሞክራለሁ። ከወንድሞቼና ከእህቶቼ ጋር በመንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች መካፈሌን እቀጥላለሁ።”
ይሖዋ በታማኝነት የምታቀርቡትን አገልግሎት ከፍ አድርጎ ይመለከታል
ቅዱሳን መጻሕፍት፣ የአቅም ገደብ ቢኖርባቸውም ይሖዋ ይወዳቸው ስለነበሩ ብዙ ሰዎች ይናገራሉ። ኢየሱስ በተወለደበት ዘመን የኖረውን አረጋዊውን ስምዖንን እንደ ምሳሌ እናንሳ። ስምዖን ወደ ቤተ መቅደሱ ሲሄድ በቤተ መቅደሱ ውስጥ የተለያዩ ሥራዎችን የሚያከናውኑ ወጣቶችን ተመልክቶ መሆን አለበት። እሱ ግን ዕድሜው ስለገፋ ይሖዋ የሚያከናውነውን ነገር ከቁብ እንደማይቆጥረው ተሰምቶት ሊሆን ይችላል። ሆኖም የይሖዋ አመለካከት ከዚህ የተለየ ነው። ስምዖን በይሖዋ ዓይን “ጻድቅና ለአምላክ ያደረ ሰው” ነበር፤ እንዲሁም ይሖዋ ለስምዖን ሕፃኑን ኢየሱስን የማየት መብት በመስጠት ባርኮታል። እንዲያውም ይሖዋ ስለ መሲሑ ትንቢት እንዲናገር ተጠቅሞበታል። (ሉቃስ 2:25-35) በግልጽ ለማየት እንደሚቻለው ይሖዋ ትኩረት ያደረገው በስምዖን አካላዊ ጥንካሬ ላይ አይደለም፤ ከዚህ ይልቅ ጠንካራ እምነት እንዳለውና ‘መንፈስ ቅዱስ በእሱ ላይ እንደነበር’ ተመልክቷል።
ይሖዋ ለስምዖን ሕፃኑን ኢየሱስን የማየትና ስለ መሲሑ ትንቢት የመናገር መብት በመስጠት ባርኮታል
እናንተም ያለባችሁ የአቅም ገደብ ምንም ይሁን ምን ይሖዋ ለእሱ በታማኝነት የምታቀርቡትን አገልግሎት ከፍ አድርጎ እንደሚመለከት መተማመን ትችላላችሁ። በእሱ ዘንድ አንድ መሥዋዕት “ይበልጥ ተቀባይነት የሚኖረው አንድ ሰው ባለው መጠን ሲሰጥ እንጂ በሌለው መጠን ሲሰጥ አይደለም።”—2 ቆሮ. 8:12
ይህን በአእምሯችሁ በመያዝ፣ ማድረግ በምትችሉት ነገር ላይ አተኩሩ። ለምሳሌ ለአጭር ሰዓትም ቢሆን በየትኞቹ የአገልግሎት ዘርፎች መካፈል ትችላላችሁ? ስልክ በመደወል ወይም አጭር ደብዳቤ በመጻፍ ሌሎችን ማበረታታት ትችሉ ይሆን? እንዲህ ያሉ ትናንሽ የሚመስሉ የፍቅር መግለጫዎች በእምነት አጋሮቻችሁ ላይ ትልቅ ተጽዕኖ ሊፈጥሩ ይችላሉ፤ በተለይ ደግሞ ይህን ያደረጉት ለረጅም ጊዜ ይሖዋን ያገለገሉ ክርስቲያኖች መሆናቸው በሌሎች ላይ ትልቅ ለውጥ ያመጣል።
አንዳንዶች በእርጅና ምክንያት እንቅስቃሴያቸው የተገደበ ነው። “ሕይወቷን አድኖላታል” በሚለው ሣጥን ውስጥ የሚገኘውን ከምሥራቅ አፍሪካ የተገኘ ተሞክሮ ልብ በሉ።
ለረጅም ዘመናት ያሳያችሁት እምነትና ታማኝነት ለሌሎች ብርታት እንደሚሆን አስታውሱ። ጽናት በማሳየት ረገድ ሕያው ምሳሌ ናችሁ። “አምላክ ቅዱሳንን በማገልገልም ሆነ ወደፊትም ማገልገላችሁን በመቀጠል የምታከናውኑትን ሥራ እንዲሁም ለስሙ ያሳያችሁትን ፍቅር በመርሳት ፍትሕ [እንደማያዛባ]” እርግጠኛ ሁኑ።—ዕብ. 6:10
በቻላችሁት መጠን ሌሎችን እርዱ
ጥናቶች እንደሚያሳዩት፣ ሌሎችን በመርዳት የተጠመዱ አረጋውያን የተሻለ ጤንነትና የአእምሮ ንቃት አላቸው፤ ረጅም ዕድሜም ይኖራሉ።
እርግጥ ነው፣ መልካም ማድረግ በእርጅና ምክንያት የሚመጡ ተፈታታኝ ሁኔታዎችን በሙሉ አያስቀርም። ይህን ማድረግ የሚችለው የአምላክ መንግሥት ብቻ ነው፤ የአምላክ መንግሥት የእርጅናና የሞት ዋነኛ መንስኤ የሆነውን ኃጢአትን ያስወግዳል።—ሮም 5:12
እስከዚያው ግን፣ ሌሎች ይሖዋን እንዲያውቁ መርዳትን ጨምሮ ለእሱ የምታቀርቡት አገልግሎት ተስፋችሁ ብሩህ እንዲሆን ይረዳችኋል፤ ምናልባትም ጤንነታችሁን ሊያሻሽለው ይችላል። ውድ አረጋውያን፣ ይሖዋ በእሱ አገልግሎት የምታከናውኑትን ሥራ ከፍ አድርጎ እንደሚመለከተው አትጠራጠሩ። ጉባኤውም የእምነት ምሳሌነታችሁን እንደ ውድ ሀብት ይቆጥረዋል።