የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • በቴክኖሎጂ መገናኘት!
    ንቁ!—2012 | የካቲት
    • በቴክኖሎጂ መገናኘት!

      ● እስቲ የሚከተለውን ሁኔታ በዓይነ ሕሊናህ ለመሳል ሞክር። ሳም ከአዳዲስ ቴክኖሎጂ ጋር እኩል ስለማይሄድ ሰዎች ኋላቀር እንደሆነ በመግለጽ ይቀልዱበት ነበር። ሳም ከቤተሰቡና ከወዳጆቹ ጋር ለመገናኘት በሚያስችለው ዘመን አመጣሽ ቴክኖሎጂ ለመጠቀም ለበርካታ ዓመታት ፈቃደኛ አልነበረም። በአሥራዎቹ ዕድሜ ላይ የሚገኙትን የሳም ልጆች ጨምሮ ሁሉም ሰው በአዲሱ ቴክኖሎጂ መጠቀም ይፈልጋል። ሳም 16 ዓመት ለሆናት ልጁ “ሰዎች በአካል ተገናኝተው ይጫወቱ የነበረበት ዘመን ይናፍቀኛል” ይላት ነበር።

      ከጊዜ በኋላ ግን ሳም አቋሙን መልሶ ማጤን ጀመረ። አንዳንድ ሰዎችን ሳያያቸውም ሆነ ሳያናግራቸው ዓመታት አልፈዋል። በሥራ ከመወጠራቸው የተነሳ ከእሱ ጋር የተራራቁ የቤተሰቡ አባላት ትዝ አሉት። ሳም ‘ከእነዚህ ሁሉ ሰዎች ጋር ያለኝ ግንኙነት ጨርሶ እንዳይቋረጥ በአዲሱ ቴክኖሎጂ መጠቀም ሳይኖርብኝ አይቀርም’ ብሎ አሰበ። ሰዎች እንደ ኋላቀር የሚያዩት ሳም በመጨረሻ ስልክ ለማስገባት ወሰነ። ይህ የሆነው በዩናይትድ ስቴትስ በሚገኝ ገጠራማ አካባቢ ሲሆን ጊዜው የ20ኛው መቶ ዘመን አጋማሽ ነበር።

      እስቲ ይህን ሁኔታ በአእምሯችን ይዘን ወደ 2012 እንምጣ። የሳም የልጅ ልጅ የሆነው ናታን፣ ወደ ሌላ አገር ከሄዱት ሮቤርቶ እና አንጀላ የተባሉ የቅርብ ጓደኞቹ ጋር በስልክ እያወራ ነው። ናታን ስልኩን ከዘጋ በኋላ ጓደኞቹ ከሄዱ አሥር ዓመት እንዳለፈ ሲያስታውስ ‘አቤት፣ ጊዜው እንዴት ይነጉዳል!’ ብሎ አሰበ።

      ቀደም ባሉት ዓመታት ናታን፣ ሩቅ ወደ ሆነ አካባቢ ከተዛወሩ የቤተሰቡ አባላትና ጓደኞቹ ጋር አልፎ አልፎ በስልክ መገናኘት መቻሉ በራሱ ያስደስተው ነበር። አሁን አሁን ግን በአሥራዎቹ ዕድሜ ላይ የሚገኙትን የናታንን ልጆች ጨምሮ ሁሉም ሰው ከሌሎች ጋር ለመገናኘት ማኅበራዊ ድረ ገጾችን ይጠቀማል።

      ናታን ግን ከአዳዲስ ቴክኖሎጂ ጋር እኩል ስለማይሄድ ሰዎች ኋላቀር እንደሆነ አድርገው ይመለከቱታል። እሱ ደግሞ “ከሰዎች ጋር በስልክ በማውራት ድምፃቸውን መስማት እችል የነበረበት ዘመን ይናፍቀኛል” ይላል። ጊዜ እያለፈ ሲሄድ ግን አቋሙን እንደገና ማጤን ጀምሯል። ናታን ‘ከሰዎች ጋር ያለኝ ግንኙነት እንዳይቋረጥ በአዲሱ ቴክኖሎጂ መጠቀም ሳይኖርብኝ አይቀርም’ የሚል ስሜት አለው።

      አንተስ እንደ ናታን ተሰምቶህ ያውቃል? ሰዎች በተፈጥሯቸው ከሌሎች ጋር የሐሳብ ልውውጥ ማድረግ ያስደስታቸዋል። (ዘፍጥረት 2:18፤ ምሳሌ 17:17) በዛሬው ጊዜ ደግሞ ብዙዎች ይህን ለማድረግ በማኅበራዊ ድረ ገጾች እየተጠቀሙ ነው፤ ታዲያ አንተስ ስለዚህ ቴክኖሎጂ ማወቅ የሚኖርብህ ነገር ምንድን ነው?

  • ተወዳጅ የሆኑት ለምንድን ነው?
    ንቁ!—2012 | የካቲት
    • ተወዳጅ የሆኑት ለምንድን ነው?

      ከታች ከተዘረዘሩት መካከል ባለፈው ወር በየትኞቹ የመገናኛ ዘዴዎች ተጠቅመሃል?

      በአካል ተገናኝቶ መነጋገር

      ደብዳቤ መጻፍ ወይም ካርድ መላክ

      ስልክ

      ኢ-ሜይል

      የሞባይል የጽሑፍ መልዕክት

      በቪዲዮ እየተያዩ ቻት ማድረግ

      ቻት

      ማኅበራዊ ድረ ገጾች

      የአሁኑን ዘመን ያህል በርካታ የመገናኛ ዘዴዎች ኖረው አያውቁም፤ እያንዳንዱ ዘዴ ደግሞ የራሱ የሆነ ጠንካራና ደካማ ጎን አለው። እስቲ አንዳንድ ምሳሌዎችን እንመልከት።

      በአካል ተገናኝቶ መነጋገር

      ጠንካራ ጎን፦ በግለሰቡ ፊት ላይ የሚነበበውን ስሜት፣ የድምፁን ቃና እንዲሁም አካላዊ መግለጫዎቹን ለማስተዋል ያስችላል።

      ደካማ ጎን፦ ሁለቱም ግለሰቦች በአካል መገናኘት ይጠበቅባቸዋል።

      ደብዳቤ መጻፍ ወይም ካርድ መላክ

      ጠንካራ ጎን፦ ፍቅርንና አሳቢነትን ለመግለጽ ያስችላል።

      ደካማ ጎን፦ መልእክቱ እስኪጻፍ ብቻ ሳይሆን ግለሰቡ እጅ እስኪደርስ ድረስ ጊዜ ይወስዳል።

      ኢ-ሜይል

      ጠንካራ ጎን፦ በፍጥነት የሚጻፍ ከመሆኑም ሌላ ተቀባዩ ጋ ቶሎ ይደርሳል።

      ደካማ ጎን፦ ብዙውን ጊዜ የጸሐፊውን ስሜት ጥሩ አድርጎ አይገልጽም፤ ወይም ደግሞ ተቀባዩ መልእክቱን በተሳሳተ መንገድ ሊረዳው ይችላል።

      ሌላው አማራጭ ደግሞ ማኅበራዊ ድረ ገጽ ነው፤ አንዳንዶች ከሰዎች ጋር ለመገናኘት ከሁሉ የተሻለው ዘዴ ይህ እንደሆነ ይሰማቸዋል። በአሁኑ ጊዜ በመቶዎች የሚቆጠሩ ማኅበራዊ ድረ ገጾች ይገኛሉ፤ ከእነዚህ መካከል በጣም ተወዳጅ የሆነው ፌስቡክ ሲሆን ከ800 ሚሊዮን የሚበልጡ አባላት አሉት! ታይም መጽሔት እንደተናገረው “ፌስቡክ አገር ቢሆን ኖሮ ከቻይናና ከሕንድ ቀጥሎ በሕዝብ ብዛት ሦስተኛ ይሆን ነበር።” ይሁንና ማኅበራዊ ድረ ገጾች ምንድን ናቸው? ይህን ያህል ተወዳጅ የሆኑትስ ለምንድን ነው?

      ማኅበራዊ ድረ ገጽ፣ ከምትፈልጋቸው ሰዎች ጋር የመረጃ ልውውጥ ማድረግ የምትችልበት ድረ ገጽ ነው። የ21 ዓመቷ ጂን “ከሰዎች ጋር ለመገናኘት የሚያስችል ግሩም ዘዴ ነው” ብላለች። “ማኅበራዊ ድረ ገጾች፣ በጉዞ ወይም በተለያዩ ዝግጅቶች ላይ የተነሳችኋቸውን ፎቶግራፎች በቀላሉ ለሌሎች ለማሳየትም ያስችላሉ።”

      ከሰዎች ጋር ለመገናኘት ደብዳቤ መጻፍ አይሻልም? አንዳንዶች ‘ደብዳቤ መጻፍማ ጊዜ ይወስዳል’ ይላሉ፤ በተጨማሪም ፎቶግራፎችን አሳጥቦ መላክ ብዙ ወጪ ይጠይቃል። ስልክ መደወልስ? ይህም ቢሆን ብዙ ጊዜ ይወስዳል፤ ደግሞም በስልክ በአንድ ጊዜ ማነጋገር የምትችለው አንድ ሰው ብቻ ከመሆኑም ሌላ አንተ በፈለግኸው ጊዜ ሰዎቹ ቤት ላይኖሩ ወይም ከአንተ ጋር ለማውራት ላይመቻቸው ይችላል። ኢ-ሜይል መላክስ? የ20 ዓመቷ ዳንዬል “አሁን አሁን ሰዎች ለኢ-ሜይል መልስ መስጠት አቁመዋል፤ መልስ ቢሰጡ እንኳ ሳምንታት ቆይተው ነው” ስትል ቅሬታዋን ገልጻለች፤ አክላም እንዲህ ብላለች፦ “ማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ ግን ስለማደርጋቸው ነገሮች የሚገልጽ ሐሳብ አሰፍራለሁ፤ ጓደኞቼም ስለ ውሏቸው ይጽፋሉ። ልክ ድረ ገጻችንን ስንከፍት አንዳችን ስለሌላው ማወቅ እንችላለን። ቀላል ዘዴ ነው!”

      ይህ ሲባል ግን በማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ የሚሰፍረው ነገር ሁሉ ዝም ብሎ ፍሬ ከርስኪ ነው ማለት አይደለም። ለምሳሌ ያህል፣ መጋቢት 11 ቀን 2011 በጃፓን የተወሰኑ አካባቢዎችን ያወደመውን የመሬት መናወጥና ሱናሚ የመሳሰሉ አደጋዎች ሲከሰቱ ብዙዎች የወዳጅ ዘመዶቻቸውን ደኅንነት ለማወቅ በማኅበራዊ ድረ ገጾች ይጠቀማሉ።

      በዩናይትድ ስቴትስ የሚኖረው ቤንጃሚን ያጋጠመውን ሁኔታ እንደ ምሳሌ እንውሰድ። እንዲህ ብሏል፦ “ጃፓን በሱናሚ በተመታች ጊዜ የስልክ መስመሮች ተቋርጠው ነበር። አንድ የማውቀው ሰው፣ በቶኪዮ ለምትኖር አንዲት ወዳጃችን ኢ-ሜይል ቢልክላትም መልስ እንዳላገኘ ነገረኝ። በዚህ ጊዜ በሞባይል ስልኬ አማካኝነት ኢንተርኔት ከፍቼ ወደ ድረ ገጿ ገባሁ። ወዳጃችን ደህና እንደሆነችና ወደፊት ዝርዝር ጉዳዮችን እንደምትጽፍ የሚገልጽ አጭር ሐሳብ ድረ ገጿ ላይ አስቀምጣ ነበር።”

      ቤንጃሚን ቀጥሎ እንዲህ ብሏል፦ “ይህችን ሴት ለሚያውቋትና ማኅበራዊ ድረ ገጽ ለማይጠቀሙ ጓደኞቻችን ግን በግለሰብ ደረጃ ኢ-ሜይል መላክ ነበረብኝ። የእያንዳንዳቸውን አድራሻ ማግኘትና ለእነሱ መጻፍ ጊዜ ወስዶብኛል። ብዙዎቹ መልስ የሰጡኝ ከቀናት በኋላ ነበር። እንዲያውም አንድ ሰው መልስ የሰጠኝ ከሁለት ሳምንት ገደማ በኋላ ነበር! እነዚያ ሰዎች ከተለያየ ሰው በጣም ብዙ መልእክት ስለሚደርሳቸው ለሁሉም መልስ መስጠት ከብዷቸው ነበር። በማኅበራዊ ድረ ገጽ ቢጠቀሙ ኖሮ ግን ብዙ ጊዜ መቆጠብ ይቻል ነበር። በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ ሁሉም ሰው ምን እየተከናወነ እንዳለ ማወቅ ይችል ነበር!”

      በእርግጥም ማኅበራዊ ድረ ገጾች ጥቅም እንዳላቸው ማንም ሊክድ አይችልም። ይሁንና የሚያስከትሉት አደጋስ ይኖር ይሆን? ከሆነ አደጋው ምንድን ነው? አንተስ ራስህን መጠበቅ የምትችለው እንዴት ነው?

      [በገጽ 5 ላይ የሚገኝ ሣጥን/​ሥዕል]

      የሚሠራው እንዴት ነው?

      1. የምትፈልገውን ሐሳብ በየጊዜው ድረ ገጽህ ላይ ታስቀምጣለህ።

      2. በጓደኛ ዝርዝርህ ውስጥ የሚገኙ ሁሉ የራሳቸውን ድረ ገጽ ሲከፍቱ አንተ ያሰፈርከውን ሐሳብ መመልከት ይችላሉ፤ አንተም የራስህን ድረ ገጽ ስትከፍት የእነሱን ሐሳብ መመልከት ትችላለህ።

  • ልታነሳቸው የሚገቡ አራት ጥያቄዎች
    ንቁ!—2012 | የካቲት
    • ልታነሳቸው የሚገቡ አራት ጥያቄዎች

      እንደማንኛውም የኢንተርኔት አገልግሎት ሁሉ ማኅበራዊ ድረ ገጽም የራሱ የሆነ አደጋ አለው።a ይህን በአእምሮህ በመያዝ ቀጥሎ የቀረቡትን ጥያቄዎች እንድታስብባቸው እንጋብዝሃለን።

      1 ማኅበራዊ ድረ ገጾች የግል ሕይወቴን የሚነኩት እንዴት ነው?

      “ከቃላት ብዛት ኀጢአት አይታጣም፤ አንደበቱን የሚገታ ግን ጠቢብ ነው።”​—ምሳሌ 10:19

      ልታውቀው የሚገባ ነገር፦ ጥንቃቄ ካላደረግህ ስለ ራስህ የምታሰፍረው መረጃ፣ ፎቶግራፎችህ፣ በጓደኛ ዝርዝርህ ውስጥ ያሉ ሰዎች እንዲመለከቱት ድረ ገጽህ ላይ በየጊዜው የምታሰፍረው አጭር ሐሳብ እንዲሁም ሌሎች ላሰፈሩት ሐሳብ የምትሰጠው ምላሽ ስለ አንተ በጣም ብዙ መረጃ ሊያስተላልፍ ይችላል። ለምሳሌ ያህል፣ አንድ ሰው ከእነዚህ መረጃዎች በመነሳት የመኖሪያ አድራሻህን፣ ቤት መሆንህን ወይም አለመሆንህን፣ የምትሠራበትን ቦታ ወይም ትምህርት ቤትህን ማወቅ ይችላል። በድረ ገጽህ ላይ አድራሻህ የሚገኝ ከሆነና “ነገ ሽርሽር እንሄዳለን!” እንደሚለው ያሉ አጭር ሐሳቦችን ካሰፈርክ ቤትህን ለመዝረፍ የሚረዳ በቂ መረጃ ለሌቦች ሰጠህ ማለት ነው።

      የኢ-ሜይል አድራሻህን፣ የተወለድክበትን ቀን ወይም የስልክ ቁጥርህን የመሳሰሉ ዝርዝር መረጃዎችን ድረ ገጽህ ላይ ማስፈርህም ለጥቃት ሊያጋልጥህ ይችላል፤ ወይም ሌሎች በአንተ ስም ተጠቅመው የማጭበርበር ድርጊቶች ሊፈጽሙ ይችላሉ። ይሁንና ብዙ ሰዎች እንዲህ ያለ አደጋ ሊከተል እንደሚችል ሳያስቡ ዝርዝር መረጃዎችን በድረ ገጾቻቸው ላይ ያሰፍራሉ።

      ሰዎች ድረ ገጻቸው ላይ አንድ መረጃ ማስፈራቸው መረጃውን አደባባይ ላይ ከመለጠፍ ተለይቶ እንደማይታይ አያስተውሉም። ድረ ገጻቸው ላይ ያሰፈሩትን ሐሳብ “ጓደኞቻቸው ብቻ” እንዲያዩት ቢያደርጉም እንኳ ጓደኛ የተባሉት ሰዎች በዚህ መረጃ የፈለጉትን ሊያደርጉ ይችላሉ። እንደ እውነቱ ከሆነ በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ የተቀመጠ ማንኛውም መረጃ አደባባይ ላይ እንደተሰቀለ ወይም በቀላሉ አደባባይ ሊወጣ እንደሚችል ተደርጎ መታየት አለበት።

      ማድረግ የምትችለው ነገር፦ በምትጠቀምበት ድረ ገጽ ላይ የግል መረጃዎችህን ሁሉም ሰው እንዳያየው ማድረግ የምትችልበትን መንገድ (ፕራይቬሲ ሴቲንግ) በደንብ ለማወቅና በሚገባ ለመጠቀም ጥረት አድርግ። በየጊዜው የምታሰፍራቸውን ሐሳቦች ወይም ፎቶግራፎችህን የምታውቃቸውና የምትተማመንባቸው ሰዎች ብቻ እንዲያዩ አድርግ።

      እንደዚህም አድርገህ ቢሆን ድረ ገጽህ ላይ ያስቀመጥከው መረጃ አንተ ካሰብከው ውጪ ለብዙ ሰዎች ሊዳረስ እንደሚችል አትዘንጋ። በድረ ገጽህ ላይ ያሰፈርከውን ሐሳብ በየጊዜው በመመርመር አታላዮች አንተን ለማግኘት ወይም በአንተ ስም ተጠቅመው ለማጭበርበር ሊጠቀሙበት የሚችሉ መረጃ አለመኖሩን አረጋግጥ። በጓደኛ ዝርዝርህ ውስጥ ላሉ ሰዎችም እንኳ የራስህንም ሆነ የሌሎችን ሚስጥር ከመናገር ተቆጠብ። (ምሳሌ 11:13) እንዲህ ያለውን መረጃ ለማስተላለፍ በሌላ የመገናኛ ዘዴ መጠቀም ትችላለህ። ካምረን የተባለች አንዲት ወጣት “በስልክ መጠቀም ስሜትን ይበልጥ ለመግለጽ የሚያስችል ከመሆኑም ሌላ ሚስጥርህን ለመጠበቅ ይረዳል” ብላለች።

      ዋናው ነጥብ፦ ኪም የተባለች ሴት የተናገረችው ሐሳብ ነጥቡን ጠቅለል አድርጎ ይገልጸዋል፦ “በማኅበራዊ ድረ ገጾች ስትጠቀም ጥንቃቄ የምታደርግ ከሆነ ሰዎች ስለ ግል ሕይወትህ አያውቁም። ማኅበራዊ ድረ ገጽ ለአደጋ የሚያጋልጥህ ጥንቃቄ ሳታደርግ ከቀረህ ነው።”

      2 ማኅበራዊ ድረ ገጾች ጊዜዬን ይሻሙብኝ ይሆን?

      “ይበልጥ አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች ለይታችሁ [እወቁ]።”​—ፊልጵስዩስ 1:10

      ልታውቀው የሚገባ ነገር፦ በማኅበራዊ ድረ ገጾች መጠቀም ጊዜህን ሊሻማብህና ይበልጥ አስፈላጊ ለሆኑ ነገሮች ትኩረት እንዳትሰጥ ሊያደርግህ ይችላል። ኬ የተባለች አንዲት ሴት “በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ ከበርካታ ሰዎች ጋር የምትገናኝ ከሆነ ብዙ ጊዜ የምታጠፋ ከመሆኑም ሌላ ሱስ ሊሆንብህ ይችላል” ብላለች። በዚህ ወጥመድ ተይዘው የነበሩ አንዳንድ ሰዎች የሰጧቸውን ሐሳቦች እንመልከት፦

      “ማኅበራዊ ድረ ገጾችን መጠቀምህን ማቆም ብትፈልግ እንኳ እንዲህ ማድረግ ከባድ ነው። ሱስ ይሆንብሃል ማለት ይቻላል።”​—ኢሊዝ

      “በጓደኞችህ ድረ ገጽ ላይ ያሉትን ሐሳቦች መመልከቱ እንዳለ ሆኖ ልታደርጋቸው የምትችላቸው ሌሎች ብዙ ነገሮች አሉ፤ ለምሳሌ ጨዋታዎችን፣ አእምሮን የሚያሠሩ ጥያቄዎችን እንዲሁም የዘፋኞችንና የአድናቂዎቻቸውን ድረ ገጾች ታገኛለህ።”​—ብሌን

      “ከባድ ሱስ ይሆንብሃል፤ በጣም ተመስጠህ ረጅም ሰዓት ማጥፋትህን የምትገነዘበው እናትህ መጥታ ዕቃዎቹን ለምን እንዳላጠብክ ስትጠይቅህ ነው።”​—አናሊስ

      “በድረ ገጼ ላይ ለጻፍኳቸው ነገሮች ማን መልስ እንደሰጠ ለማወቅ ስለምጓጓ በተቻለ ፍጥነት ከትምህርት ቤት እመለሳለሁ። ከዚያም ለእነዚያ ሁሉ ሰዎች መልስ እሰጣለሁ፤ እንዲሁም በድረ ገጻቸው ላይ ያስቀመጧቸውን አዳዲስ ፎቶግራፎች እመለከታለሁ። ኢንተርኔት በምጠቀምበት ጊዜ ጠባዬ ሁሉ ይለዋወጣል፤ ሲያቋርጡኝ ብስጭትጭት እላለሁ። ከማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ የማይጠፉ አንዳንድ የማውቃቸው ሰዎች አሉ፤ ሌላው ቀርቶ ሰው ቤት ተጋብዘው ሲሄዱ ወይም ሌሊት ላይ እንኳ እነዚህን ድረ ገጾች ይከፍታሉ!”​—ሜገን

      ማድረግ የምትችለው ነገር፦ ጊዜ ልታባክነው የማይገባ ሀብት ነው። ታዲያ ለገንዘብ እንደምታደርገው ሁሉ በጊዜ አጠቃቀምህ ረገድም ለምን ባጀት አታወጣም? በመጀመሪያ፣ ማኅበራዊ ድረ ገጾችን በመጠቀም ምን ያህል ጊዜ ብታሳልፍ ተገቢ እንደሚሆን ጻፍ። ከዚያም ለአንድ ወር ያህል ጊዜህን እንዴት እንደተጠቀምክበት በመመልከት ውሳኔህን ምን ያህል እንዳከበርክ ገምግም። አስፈላጊ ከሆነ ማስተካከያ አድርግ።

      ወላጅ ከሆንክና በጉርምስና ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆችህ በማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ ረጅም ጊዜ የሚያጠፉ ከሆነ ይህን የሚያደርጉበትን ምክንያት ለማስተዋል ሞክር። ለምሳሌ ያህል፣ ናንሲ ዊላርድ ሳይበር ሴፍ ኪድስ፣ ሳይበር ሳቪ ቲንስ በተባለው መጽሐፋቸው ላይ እንደተናገሩት ልጆች ማኅበራዊ ድረ ገጾችን በመጠቀም ረጅም ጊዜ ማጥፋታቸው ጭንቀትና ውጥረት እንዳለባቸው እንዲሁም ለራሳቸው ያላቸው ግምት ዝቅተኛ እንደሆነ የሚጠቁም ሊሆን ይችላል። እኚህ ሴት “በአሥራዎቹ ዕድሜ ያሉ ብዙ ወጣቶች ሌሎች ስለ እነሱ ያላቸው አመለካከት በጣም ያሳስባቸዋል” በማለት ጽፈዋል። “ወጣቶች በእኩዮቻቸው ዘንድ ምን ያህል ተቀባይነት እንዳላቸው የሚለኩት ከጓደኞቻቸው ጋር በኢንተርኔት አማካኝነት በሚያደርጉት የሐሳብ ልውውጥ መጠን ከሆነ ይህ ሱስ ሊሆንባቸው ይችላል።”

      ማኅበራዊ ድረ ገጾችም ሆኑ ማንኛውም ዓይነት ድረ ገጽ ከቤተሰብህ አባላት ጋር ሊኖርህ በሚገባው ግንኙነት ላይ ተጽዕኖ እንዲያሳድሩ ፈጽሞ አትፍቀድ። ዶን ታፕስኮት፣ ግሮውን አፕ ዲጂታል በተባለው መጽሐፋቸው ላይ እንዲህ ብለዋል፦ “የሚገርመው ነገር ኢንተርኔት በአካል የተራራቁ የቤተሰብ አባላትን የሚያቀራርብ ቢሆንም በአንድ ጣሪያ ሥር ያሉትን ግን ሊያራርቃቸው ይችላል።”

      ዋናው ነጥብ፦ ኤመሊ የተባለች አንዲት ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “ማኅበራዊ ድረ ገጽ ከሰዎች ጋር ለመገናኘት የሚያስችል ጥሩ ዘዴ ይመስለኛል። ይሁንና እንደማንኛውም ነገር ሁሉ ማኅበራዊ ድረ ገጾችን በመጠቀም የምታሳልፈውን ጊዜም ገደብ ልታበጅለት ይገባል።”

      3 ማኅበራዊ ድረ ገጾች በሌሎች ዘንድ ባለኝ ስም ላይ ምን ተጽዕኖ ያሳድራሉ?

      “መልካም ስም ከብዙ ብልጽግና ይመረጣል፤ መከበርም ከብርና ከወርቅ ይበልጣል።”​—ምሳሌ 22:1

      ልታውቀው የሚገባ ነገር፦ በማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ የምታሰፍረው ሐሳብ ሰዎች ስለ አንተ በሚኖራቸው አመለካከት ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድር ሲሆን ይህን ማስተካከልም አስቸጋሪ ሊሆን ይችላል። (ምሳሌ 20:11፤ ማቴዎስ 7:17) ብዙዎች እንዲህ ያለውን አደጋ ያስተዋሉት አይመስልም። ራኬል የተባለች አንዲት ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “ሰዎች በማኅበራዊ ድረ ገጾች በሚጠቀሙበት ጊዜ የማመዛዘን ችሎታቸውን የሚያጡ ይመስላል። ሌላ ጊዜ ቢሆን የማይሉትን ነገር በድረ ገጻቸው ላይ ያሰፍራሉ። አንዳንዶች ተገቢ ያልሆነ አንድ ሐሳብ ማስፈራቸው ብቻ ስማቸውን ሊያጎድፍ እንደሚችል አይገነዘቡም።”

      በማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ በምታሰፍረው ነገር ምክንያት ስምህ መጉደፉ በወደፊት ሕይወትህም ላይ መጥፎ ተጽዕኖ ሊያሳድር ይችላል። ግሮውን አፕ ዲጂታል የተባለው መጽሐፍ እንዲህ ይላል፦ “ማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ነገር ምክንያት ከሥራ የተባረሩ ወይም ሌላ ሥራ መቀጠር ያልቻሉ በርካታ ሰዎች እንዳሉ የሚገልጹ ታሪኮችን መስማት የተለመደ ነው።”

      ማድረግ የምትችለው ነገር፦ ድረ ገጽህን ከፍተህ እዚያ ላይ የሰፈረውን ሐሳብ በሌሎች ዓይን ለማየት ሞክር። ራስህን እንዲህ እያልክ ጠይቅ፦ ‘በሌሎች ዘንድ መታወቅ የምፈልገው በዚህ መንገድ ነው? አንድ ሰው በድረ ገጼ ላይ ያስቀመጥኳቸውን ፎቶግራፎች ከተመለከተ በኋላ ስለ እኔ ምን ዓይነት አመለካከት ይኖረዋል? ሌሎችን ማሽኮርመም እንደምወድ፣ ለፆታ ብልግና የሚጋብዝ አለባበስ እንዳለኝ እንዲሁም ያለ ጭፈራ ሌላ ሥራ እንደሌለኝ ይሰማዋል? ከሆነ ሥራ ባመለክትና ቀጣሪዬ ድረ ገጼን ቢመለከት ስለ እኔ እንዲህ ዓይነት ግምት እንዲኖረው እፈልጋለሁ? እነዚህ ፎቶግራፎች የምመራበትን የሥነ ምግባር አቋም በትክክል ይገልጻሉ?’

      ወጣት ከሆንክ ደግሞ ራስህን እንዲህ ብለህ ጠይቅ፦ ‘ወላጆቼ፣ አስተማሪዎቼ ወይም ሌሎች የማከብራቸው ሰዎች ድረ ገጼን ቢመለከቱትስ? እዚያ ላይ የሚያዩትና የሚያነቡት ነገር ያሳፍረኛል?’

      ዋናው ነጥብ፦ በሌሎች ዘንድ የሚኖርህን ስም በተመለከተ ሐዋርያው ጳውሎስ “አንድ ሰው ምንም ዘራ ምን ያንኑ መልሶ ያጭዳል” በማለት የጻፈውን ሐሳብ አስታውስ።​—ገላትያ 6:7

      4 ማኅበራዊ ድረ ገጾች በጓደኛ ምርጫዬ ላይ ምን ተጽዕኖ ያሳድራሉ?

      “ከጠቢብ ጋር የሚሄድ ጠቢብ ይሆናል፤ የተላሎች ባልንጀራ ግን ጕዳት ያገኘዋል።”​—ምሳሌ 13:20

      ልታውቀው የሚገባ ነገር፦ ጓደኞችህ በአስተሳሰብህና በድርጊትህ ላይ ተጽዕኖ ማሳደራቸው አይቀርም። (1 ቆሮንቶስ 15:33) በመሆኑም በማኅበራዊ ድረ ገጾች ላይ ጓደኛ የምታደርጋቸውን ሰዎች በተመለከተ መራጭ መሆንህ የተገባ ነው። አንዳንዶች እምብዛም ወይም ጨርሶ ከማያውቋቸው ሰዎች የሚላኩላቸውን በመቶዎች የሚቆጠሩ የጓደኝነት ግብዣዎች ይቀበላሉ። ሌሎች ደግሞ በጓደኛ ዝርዝራቸው ላይ ካሉት ሰዎች መካከል ጥሩ ጓደኞች ያልሆኑ እንዳሉ ከጊዜ በኋላ ተገንዝበዋል። እስቲ አንዳንዶቹ ምን እንዳሉ እንመልከት፦

      “አንድ ሰው እገሌ ከገሌ ሳይል ሁሉም ሰው የላከለትን የጓደኝነት ግብዣ የሚቀበል ከሆነ ውሎ አድሮ ችግር ውስጥ መግባቱ አይቀርም።”​—አናሊስ

      “ብዙ የማውቃቸው ሰዎች፣ በጓደኛ ዝርዝራቸው ውስጥ ሊያስገቧቸው የማይፈልጓቸውን ሰዎች እንኳ ጓደኛ አድርገው ይቀበላሉ፤ ይህን የሚያደርጉት የግለሰቡን ስሜት መጉዳት ስለማይፈልጉ እንደሆነ ይናገራሉ።”​—ሊአን

      “በማኅበራዊ ድረ ገጾች አማካኝነት ጓደኝነት መመሥረት በአካል ከምናገኛቸው ሰዎች ጋር ወዳጅነት ከመመሥረት ተለይቶ የሚታይ አይደለም። በጓደኛ ምርጫህ ረገድ ጠንቃቃ መሆን አለብህ።”​—አሌክሲስ

      ማድረግ የምትችለው ነገር፦ ጓደኞችህን የምትመርጥበት መሥፈርት አውጣ። ለምሳሌ ያህል፣ አንዳንዶች በጓደኛ ምርጫቸው ረገድ ገደብ አበጅተዋል፦

      “ጓደኛ አድርጌ የምቀበለው እንዲያው በሩቅ የማውቃቸውን ሰዎች ሳይሆን ማንነታቸውን በደንብ የማውቃቸውን ሰዎች ብቻ ነው።”​—ጂን

      “በጓደኛ ዝርዝሬ ውስጥ የማስገባው ለረጅም ጊዜ የማውቃቸውን ሰዎች ብቻ ነው። የማላውቃቸውን ሰዎች ፈጽሞ ጓደኛ አድርጌ አልቀበላቸውም።”​—ሞኒክ

      “ጓደኛ አድርጌ የምቀበለው በደንብ የማውቃቸውንና ከእኔ ጋር ተመሳሳይ የሆነ የሥነ ምግባር አቋም ያላቸውን ሰዎች ብቻ ነው።”​—ሬ

      “የማላውቀው ሰው ጓደኛው እንድሆን ቢጋብዘኝ ግብዣውን አልቀበልም። አቋሜ ይህ ነው። በጓደኛ ዝርዝሬ ውስጥ ያሉት ሰዎች በሙሉ በደንብ የማውቃቸውና በገሃዱ ዓለም ጓደኞቼ የሆኑ ግለሰቦች ናቸው።”​—መሪ

      “ጓደኛዬ አድርጌ የተቀበልኩት ሰው ተገቢ ያልሆኑ ፎቶግራፎችን ወይም ሐሳቦችን በድረ ገጹ ላይ ቢያስቀምጥ ይህን ሰው ከጓደኛ ዝርዝሬ ላይ ለመሰረዝ ዓይኔን አላሽም። ሌሎች ያስቀመጡትን ነገር መመልከቱ በራሱ ከመጥፎ ጓደኞች ጋር ከመቀራረብ ተለይቶ አይታይም።”​—ኪም

      “ማኅበራዊ ድረ ገጽ በነበረኝ ጊዜ መረጃዎቼን እንዲያዩ የምፈቅደው በጣም ለተወሰኑ ሰዎች ብቻ ነበር። የጓደኞቼ ጓደኞች የሆኑ ሰዎች የጻፍኳቸውን ሐሳቦችም ሆነ ፎቶግራፎቼን እንዲያዩ አልፈቅድም፤ ይህን ማድረግ የሚችሉት ጓደኞቼ ብቻ ነበሩ። እንዲህ የማደርገው የጓደኞቼ ጓደኞች ለእኔ ጥሩ ወዳጆች መሆናቸውን እርግጠኛ ስላልሆንኩ ነው። ማንነታቸውንም ሆነ ምን ዓይነት ስም እንዳላቸው አላውቅም።”​—ሄዘር

      ዋናው ነጥብ፦ ዶክተር ግዌን ሹርገን ኦኪፍ፣ ሳይበርሴፍ በተባለው መጽሐፋቸው ላይ “ከሁሉ የተሻለው መርሕ ከምታውቃቸውና በገሃዱ ዓለም ጓደኛህ ከሆኑ ሰዎች ውጪ ማንንም በጓደኛ ዝርዝርህ ውስጥ አለማስገባት ነው” ብለዋል።b

      [የግርጌ ማስታወሻዎች]

      a ንቁ! የትኛውንም ዓይነት ማኅበራዊ ድረ ገጽ ለይቶ በመጥቀስ አይደግፍም አሊያም አያወግዝም። ክርስቲያኖች የኢንተርኔት አጠቃቀማቸው ከመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ጋር እንደማይቃረን ማረጋገጥ አለባቸው።​—1 ጢሞቴዎስ 1:5, 19

      b ስለ ማኅበራዊ ድረ ገጾች ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት የንቁ! መጽሔትን የሐምሌ 2011 እትም ከገጽ 24-27 እና የነሐሴ 2011 እትም ከገጽ 10-13 ተመልከት።

      [በገጽ 8 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

      ዘግተህ ውጣ!

      የምትጠቀምበትን ድረ ገጽ በአግባቡ ዘግተህ የማትወጣ ከሆነ ሌሎች በአንተ ድረ ገጽ ላይ የፈለጉትን ነገር ማስፈር ይችላሉ። ሮበርት ዊልሰን የተባሉት የሕግ ባለሞያ እንደተናገሩት ድረ ገጽህን ሳትዘጋ መውጣት “የገንዘብ ቦርሳህን ወይም ሞባይል ስልክህን በሕዝብ መዝናኛ ቦታ ትቶ የመሄድ ያህል ነው። ማንኛውም ሰው ድረ ገጽህ ላይ ሐሳቡን ማስፈር ይችላል።” እኚህ ሰው ሐሳባቸውን ሲያጠቃልሉ “ዘግተህ መውጣትህን አትርሳ” የሚል ምክር ሰጥተዋል።

      [በገጽ 8 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

      ራስህን ለችግር እያጋለጥክ ይሆን?

      ኮንሲዩመር ሪፖርትስ ያካሄደው ጥናት እንዳሳየው በማኅበራዊ ድረ ገጽ የሚጠቀሙ በርካታ ሰዎች “ለዝርፊያና ለጥቃት እንዲሁም በስማቸው ለሚፈጸም የማጭበርበር ድርጊት ሊያጋልጣቸው የሚችል ነገር ያደርጋሉ። አሥራ አምስት በመቶ የሚሆኑት አድራሻቸውን ወይም የጉዞ እቅዳቸውን፣ 34 በመቶ የሚሆኑት የትውልድ ቀናቸውን እንዲሁም ልጆች ካሏቸው ሰዎች መካከል 21 በመቶ የሚሆኑት የልጆቻቸውን ስምና ፎቶግራፍ በድረ ገጻቸው ላይ አስፍረዋል።”

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ