የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • be ጥናት 29 ገጽ 181-ገጽ 185 አን. 2
  • የድምፅ ጥራት

በዚህ ክፍል ውስጥ ምንም ቪዲዮ አይገኝም።

ይቅርታ፣ ቪዲዮውን ማጫወት አልተቻለም።

  • የድምፅ ጥራት
  • በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
  • ተመሳሳይ ሐሳብ ያለው ርዕስ
  • ድምፅን ማሻሻልና የድምፅ ማጉያ አጠቃቀም
    ቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት መመሪያ መጽሐፍ
  • ቃላትን አጥርቶ መናገር
    በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
  • ‘ለእንግዳ ድምፅ’ ጆሯችሁን እንዳትሰጡ ተጠንቀቁ
    የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ—2004
  • ጡንቻዎች ምርጥ የንድፍ ሥራ ውጤቶች
    ንቁ!—1999
ለተጨማሪ መረጃ
በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
be ጥናት 29 ገጽ 181-ገጽ 185 አን. 2

ጥናት 29

የድምፅ ጥራት

ምን ማድረግ ይኖርብሃል?

ሌላ ሰው በመኮረጅ ሳይሆን አተነፋፈስህን በመቆጣጠርና የተወጠሩ ጡንቻዎችን ዘና በማድረግ የድምፅህን ጥራት አሻሽል።

አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

አንድ ተናጋሪ ጥሩ ድምፅ ካለው ሰዎች ዘና ሊሉና ደስ ብሏቸው ሊያዳምጡ ይችላሉ። ድምፁ ጥራት ከሌለው ግን ንግግሩን ሊያስተጓጉልበት እንዲሁም ተናጋሪውን ራሱንም ሆነ አድማጮቹን ተስፋ ሊያስቆርጥ ይችላል።

ሰዎችን የሚማርካቸው የሚነገረው መልእክት ብቻ ሳይሆን የሚነገርበትም መንገድ ነው። አንድ ሰው ሲያነጋግርህ ደስ ብሎህ የምትሰማው የድምፁ ቃና አሳቢነት የጎደለውና የቁጣ ከሚሆን ይልቅ ፍቅር፣ ርኅራኄና ደግነት የተንጸባረቀበት ቢሆን አይደለምን?

የድምፃችን ጥራት ከድምፅ አወጣጥ ሂደት ጋር ብቻ የተያያዘ ጉዳይ አይደለም። የግለሰቡም ባሕርይ በዚህ ረገድ የራሱ ድርሻ ሊኖረው ይችላል። አንድ ሰው ስለ መጽሐፍ ቅዱስ እውነት ያለው እውቀት እያደገ ሲሄድና ያንንም በሕይወቱ ሲሠራበት በአነጋገሩ የሚያደርገው ለውጥ በግልጽ ይታያል። የድምፁ ቃና እንደ ፍቅር፣ ደስታና ደግነት ያሉትን አምላክ የሚደሰትባቸው ባሕርያት የሚያንጸባርቅ ይሆናል። (ገላ. 5:​22, 23) ለሌሎች ያለውን ልባዊ አሳቢነት ከድምፁ ቃና ማስተዋል ይቻላል። የማጉረምረምንና የማማረርን ዝንባሌ አስወግዶ በምትኩ የአመስጋኝነትን ባሕርይ ሲያዳብር ይህ ለውጥ ከአፉ በሚወጣው ቃልና በድምፁ ቃና ግልጽ ሆኖ ይታያል። (ሰቆ. 3:​39-42፤ 1 ጢሞ. 1:​12፤ ይሁዳ 16) አንድ ሰው እየተናገረ ያለውን ቋንቋ ባትረዳው እንኳ አነጋገሩ የቁጣ፣ የእብሪትና የትችት ይሁን ወይም ደግሞ የትሕትና፣ የደግነትና የፍቅር ከድምፁ ቃና በቀላሉ መረዳት ትችላለህ።

አንዳንድ ጊዜ አንድ ሰው ድምፁ ጥሩ የማይሆነው በሕመም ምክንያት ማንቁርቱ ሲጎዳ ወይም ደግሞ አብሮት በሚወለድ እንከን ምክንያት ሊሆን ይችላል። እንዲህ ያሉት ችግሮች ከባድ ከመሆናቸው የተነሣ በዚህ ሥርዓት ሙሉ በሙሉ መፍትሔ አያገኙ ይሆናል። ይሁን እንጂ ብዙውን ጊዜ የአንደበት ክፍሎችን በሚገባ መጠቀም የሚቻለው እንዴት እንደሆነ መማር ድምፅን ለማሻሻል ይረዳል።

በመጀመሪያ ደረጃ የድምፅ ሁኔታ ከሰው ሰው እንደሚለያይ መገንዘብ ያስፈልጋል። ግብህ የሌሎችን ሰዎች ድምፅ መኮረጅ መሆን የለበትም። ከዚህ ይልቅ የራሱ ልዩ ባሕርይ ያለውን ድምፅህን በተሻለ መንገድ መጠቀምን ተማር። ይህን ለማድረግ ሊረዳህ የሚችለው ምንድን ነው? ሁለት ዓበይት ነገሮች አሉ።

አተነፋፈስህን መቆጣጠር። ድምፅህን በተሻለ መንገድ ለመጠቀም በቂ አየር መሳብና አተነፋፈስህን በተገቢው መንገድ መቆጣጠር ያስፈልግሃል። አለዚያ ግን ድምፅህ ሊደክምና ንግግርህ ሊቆራረጥ ይችላል።

ሰፋ ያለው የሳንባህ አካል የሚገኘው በደረትህ የላይኛው ክፍል አይደለም። ይህ አካባቢ ትልቅ መስሎ የሚታየው በትከሻ አጥንቶች ምክንያት ነው። ከዚህ ይልቅ ሳንባችን ሰፋ የሚለው ከወደታች ከድልሺ አካባቢ ነው። ድልሺ የሚባለው ጡንቻ ከታችኞቹ የጎድን አጥንቶች ጋር የተያያዘና ደረትንና የሆድ ዕቃን የሚከፍል ነው።

አየር ወደ ውስጥ በማስገባት የሞላኸው የሳንባህን የላይኛውን ክፍል ብቻ ከሆነ ብዙም ሳይቆይ ትንፋሽ ያጥርሃል። ድምፅህ ኃይል አይኖረውም፤ አንተም ቶሎ ትደክማለህ። ጥሩ አተነፋፈስ እንዲኖርህ ትከሻዎችህን ወደኋላ ለጠጥ አድርገህ ቀጥ ብለህ መቀመጥ ወይም መቆም ያስፈልግሃል። ከመናገርህ በፊት አየር ወደ ውስጥ በምትስብበት ጊዜ የሚለጠጠው የደረትህ የላይኛው ክፍል ብቻ መሆን የለበትም። በቅድሚያ የታችኛውን የሳንባህን ክፍል አየር መሙላት ይኖርብሃል። የታችኛው የሳንባህ ክፍል አየር ሲሞላ የጎድን አጥንቶችህ ወደ ጎንና ወደ ጎን ይለጠጣሉ። በዚህ ጊዜ ድልሺ ሆድ ዕቃህን ቀስ ብሎ ወደታች ሲጫነው ቀበቶህ አካባቢ ግፊቱ ይሰማሃል። ይሁንና ሳንባህ ያለው ሆድ ዕቃህ መካከል ሳይሆን ሳንባ አቃፊህ ውስጥ ነው። ይህን ሂደት ራስህ ማየት እንድትችል ሳንባ አቃፊህን ከግራና ከቀኝ በእጆችህ በመያዝ አየር በደንብ ወደ ውስጥ አስገባ። አተነፋፈስህ ትክክለኛ ከሆነ ሆድህ ወደ ውስጥ ተሰልቦ ደረትህ አይነፋም። ከዚህ ይልቅ የጎድን አጥንቶችህ ወደ ውጭ ወጣ ይላሉ።

ቀጥሎ ደግሞ እንዴት አየር እንደምታስወጣ ተለማመድ። ያስገባኸውን አየር ቀስ በቀስ ልታስወጣ ይገባል እንጂ በአንድ ጊዜ በማስወጣት ማባከን የለብህም። ጉሮሮህን በማስጨነቅ አየሩ እንዳይወጣ ለመቆጣጠር አትሞክር። ይህ ደግሞ ድምፅህ እንዲሻክር ወይም እንዲሰልል ያደርጋል። የሆድ ጡንቻዎችና በጎድን አጥንቶች መካከል ያሉት ጡንቻዎች አየር እንዲወጣ የሚያደርጉ ሲሆኑ ድልሺ ግን አየሩ የሚወጣበትን ፍጥነት ይቆጣጠራል።

በገጽ 183 ላይ የሚገኙ ሥዕሎች

አንድ ሯጭ ትንፋሹን መቆጣጠር እንደሚለማመድ ሁሉ አንድ ተናጋሪም አተነፋፈሱን በመለማመድ ትንፋሹን መቆጣጠርን ሊማር ይችላል። ቀጥ ብለህና ትከሻዎችህን ወደኋላ ለጠጥ አድርገህ በመቆም የሳንባህን የታችኛውን ክፍል አየር ሙላ። ከዚያም ቀስ በቀስ ትንፋሽህን እየለቀቅህ ረጋ ብለህ በዚያው አንድ ትንፋሽ የቻልከውን ያህል ቁጠር። ከዚያም በተመሳሳይ መንገድ እየተነፈስህ ድምፅህን ከፍ አድርገህ ማንበብን ተለማመድ።

የተወጠሩ ጡንቻዎችን ማዝናናት። የድምፅን ጥራት ለማሻሻል ሌላው በጣም አስፈላጊ የሆነ ነገር ዘና ማለት ነው! በምትናገርበት ጊዜ ዘና ማለት በድምፅህ አወጣጥ ላይ ምን ያህል ለውጥ እንደሚያመጣ ስታይ ትገረማለህ። ጭንቀት ጡንቻዎች እንዲወጠሩ ስለሚያደርግ አእምሮህም ሆነ ሰውነትህ ዘና ማለት ይኖርበታል።

ስለ አድማጮችህ ተገቢውን አመለካከት መያዝ ጭንቀትህን ይቀንስልሃል። በአገልግሎት የምታገኛቸውን ሰዎች በተመለከተ ምናልባት አንተ መጽሐፍ ቅዱስን ያጠናኸው ለጥቂት ወራት ብቻም እንኳ ቢሆን ስለ ይሖዋ ዓላማ ልትነግራቸው የምትችለው ጠቃሚ መልእክት እንደያዝህ አስታውስ። ደግሞም እነርሱ ተገነዘቡትም አልተገነዘቡት ልታነጋግራቸው የሄድከው እርዳታ ስለሚያስፈልጋቸው መሆኑን አትርሳ። በመንግሥት አዳራሽ ንግግር የምትሰጥም ከሆነ በዚያ የሚገኙት አብዛኛዎቹ አድማጮችህ የይሖዋ አገልጋዮች ናቸው። አንተ ሲሳካልህ ማየት የሚመኙ ወዳጆችህ ናቸው። እንዲህ ዓይነት አፍቃሪ አድማጮች የትም ልታገኝ አትችልም።

የጉሮሮ ጡንቻዎችህን ሥራዬ ብለህ ዘና ለማድረግ መጣር ይኖርብሃል። ሐብለ ድምፅህ አየር በውስጡ በሚያልፍበት ጊዜ እንደሚርገበገብ አስታውስ። የክራር ወይም የመሰንቆ ክር ሲወጠር ወይም ሲላላ ድምፁ እንደሚለወጥ ሁሉ የጉሮሮ ጡንቻዎችም ሲጨነቁ ወይም ዘና ሲሉ የድምፃችን ቃና ይለዋወጣል። ሐብለ ድምፁ ዘና ሲል ድምፅ ወፈር ያለ ይሆናል። የጉሮሮ ጡንቻዎችን ማዝናናት አየር በሰርን በኩል እንደልብ እንዲወጣ ስለሚያደርግ ጥሩ ድምፅ ለማውጣት ይረዳል።

መላ ሰውነትህ ማለትም ጉልበትህ፣ እጅህ፣ ትከሻህና አንገትህ ዘና እንዲል አድርግ። ይህም ሰውነት ድምፅ ጥርት ብሎ እንዲሰማ የሚረዳ የማስተጋባት ባሕርይ እንዲኖረው ያደርጋል። ሰውነታችን በደንብ ድምፅ የማስተጋባት ባሕርይ የሚኖረው ዘና ሲል ስለሆነ ውጥረት ካለበት ይህን ተግባሩን ሊያከናውን አይችልም። ማንቁርት ውስጥ የተፈጠረው ድምፅ የሚያስተጋባው በሰርን ዋሻ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በደረታችን የአጥንት ክፍሎች፣ በጥርስ፣ በላንቃና በሳይነስ አማካኝነት ጭምር ነው። እነዚህ ሁሉ ድምፁ በጥሩ ሁኔታ እንዲስተጋባ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ። በክራሩ የድምፅ ሣጥን ላይ አንድ ነገር ብትጭንበት ድምፁ ይታፈናል። ድምፅ በደንብ እንዲያስተጋባ ካስፈለገ እንዳይነዝር የሚያግድ ነገር መኖር የለበትም። ጡንቻዎቻችን በመወጠራቸው ምክንያት የሰውነታችን አጥንቶችም መንዘር ካልቻሉ ድምፃችን ይታፈናል። ድምፅህ በደንብ የሚያስተጋባ ከሆነ ግን ድምፅህን መለዋወጥም ሆነ የተለያዩ ስሜቶችን ማንጸባረቅ ትችላለህ። አድማጮችህ ብዙ ቁጥር ያላቸው ቢሆኑም እንኳ በጣም መጨነቅ ሳያስፈልግህ በቂ ድምፅ ማውጣት ትችላለህ።

የንግግር ድምፅ አፈጣጠር

ድምፅ እንዲፈጠር ዋነኛ ምክንያት የሚሆነው ከሳንባ የሚወጣው አየር ነው። ሳንባ በአየር ቱቦዎች አማካኝነት አየር በጉሮሯችን መካከል ወደሚገኘው ማንቁርት እንዲደርስ እንደ ወናፍ ሆኖ ያገለግላል። ማንቁርት ውስጥ በሁለቱም ተቃራኒ አቅጣጫ ሐብለ ድምፅ የሚባሉ ትናንሽ ጡንቻዎች ይገኛሉ። ድምፅ እንዲፈጠር ትልቁን ሚና የሚጫወቱት እነዚህ ጡንቻዎች ናቸው። እነዚህ ጡንቻዎች አየር በማንቁርት ውስጥ የሚያልፍበትን ክፍተት በመክፈትና በመዝጋት አየር እንዲገባና እንዲወጣ ከማድረጋቸውም ሌላ አላስፈላጊ ነገሮች ወደ ሳንባችን እንዳይገቡ ይከላከላሉ። በምንተነፍስበት ጊዜ አየር በሐብለ ድምፆች መካከል ሲያልፍ ምንም ድምፅ አይፈጠርም። ይሁን እንጂ አንድ ሰው መናገር ሲፈልግ ሐብለ ድምፆቹ ስለሚወጠሩ ከሳንባ የሚወጣው አየር ገፍቷቸው ሲያልፍ ይርገበገባሉ። ድምፅ የሚፈጠረው በዚህ መንገድ ነው።

ሐብለ ድምፆቹ በጣም በተወጠሩ መጠን የሚርገበገቡበት ፍጥነት ስለሚጨምር ድምፁ ይቀጥናል። በሌላ በኩል ግን ሐብለ ድምፆቹ ዘና ሲሉ ድምፁ ወፈር ያለ ይሆናል። ከማንቁርት የወጣው የድምፅ ሞገድ ጫፍ ላይ ወደሚገኘው የጉሮሮ ክፍል ይገባል። ከዚያም በአፍና በሰርን ዋሻ በኩል አልፎ ይወጣል። ከዚያ በኋላ ላንቃ፣ ትናጋ፣ ምላስ፣ ጥርስ፣ ከንፈር እንዲሁም መንገጭላ አንድ ላይ ተቀናጅተው ከታች የመጣውን የድምፅ ሞገድ በመሰባበር ትርጉም ያለው የንግግር ድምፅ ሆኖ እንዲወጣ ያደርጋሉ።

የሰው ልጅ ድምፅ ማንኛውም ሰው ሠራሽ መሣሪያ የሚያወጣው ድምፅ ሊተካከለው የማይችል ድንቅ ስጦታ ነው። ከጠበቀ ፍቅር አንስቶ እስከ መረረ ጥላቻ ድረስ የተለያዩ ስሜቶችን መግለጽ ይችላል። ድምፃችንን ካለማመድነውና በደንብ ከገራነው ብዙ ዓይነት ቃናዎችን ሊያወጣ ይችላል። በዚህ መንገድ ለዘፈን የሚመች ውብ ድምፅ ብቻ ሳይሆን ልብ የሚነካ ንግግር ለመስጠትም የሚረዳ ጥሩ ድምፅ ይሆናል።

አንዳንድ የድምፅ ችግሮችን ማሻሻል

ደካማ ድምፅ። ለስለስ ያለ ድምፅ ሁሉ ደካማ ነው ማለት ላይሆን ይችላል። ደስ የሚል ቅላጼ ያለው ከሆነ ሰዎች በደስታ ሊሰሙት ይችላሉ። ያም ሆኖ ግን ይበልጥ እንዲሰማ የድምፁ መጠን በቂ ሊሆን ይገባል።

ድምፅህ በደንብ እንዲሰማ በሰውነትህ ውስጥ እንዲያስተጋባ ማድረግ ይኖርብሃል። ይህም በዚህ ምዕራፍ ውስጥ በተገለጸው መሠረት ሰውነትህን ማዝናናትን ይጠይቅብሃል። ሆን ብለህ ሰውነትህን ዘና ለማድረግ መሞከር እንዲሁም ከንፈርህን በጣም ሳትጫን ትንሽ ብቻ ገጠም በማድረግ እምምም . . . የሚል ድምፅ እያሰማህ መለማመድ ሊረዳህ ይችላል። እንዲህ ዓይነት ድምፅ ስታወጣ ጭንቅላትህና ደረትህ አካባቢ ንዝረት ይሰማሃል።

አንዳንድ ጊዜ አንድ ሰው ድምፁ የሚደክመው ወይም የሚሻክረው ጤንነቱ ሲታወክ ወይም በቂ እንቅልፍ ሳያገኝ ሲቀር ነው። ጤንነቱና እንቅልፉ ከተስተካከለ የድምፁ ችግርም እንደሚስተካከል የታወቀ ነው።

የሰለለ ድምፅ። ሐብለ ድምፅ ላይ ውጥረት ሲፈጠር የሚወጣው ድምፅ የሰለለ ይሆናል። ተናጋሪው ድምፁን የሚያወጣው ተጨንቆ ከሆነ አድማጮችም ይጨንቃቸዋል። በሐብለ ድምፅ ላይ የሚፈጠረውን ውጥረት ለመቀነስ የጉሮሮ ጡንቻዎችን በማዝናናት የሰለለውን ድምፅ ማስተካከል ይቻላል። ዕለት ተዕለት ከሰዎች ጋር ስትነጋገር ሥራዬ ብለህ ልምምድ አድርግ። አየር በደንብ ወደ ውስጥ ማስገባትም ይረዳሃል።

የሚነፋነፍ ድምፅ። አንዳንድ ጊዜ እንዲህ ዓይነት ድምፅ የሚፈጠረው አፍንጫ ሲታፈን ቢሆንም ሁልጊዜ ምክንያቱ ይህ ነው ማለት አይደለም። የጉሮሮና የአፍ ጡንቻዎች ሲወጠሩ አየር በሰርን በኩል እንደልብ እንዳያልፍ እንቅፋት ሊሆን ይችላል። ይህም ድምፁ እንዲነፋነፍ ያደርጋል። ይህን ችግር ለማስወገድ ዘና ማለት ያስፈልጋል።

ጎርናና ድምፅ። ጎርናና ድምፅ ሰዎች ዘና ብለው እንዲያነጋግሩን ከመጋበዝ ይልቅ እንዲፈሩን ሊያደርግ ይችላል።

የባሕርይ ለውጥ ለማምጣት የማያቋርጥ ጥረት ማድረግ ያስፈልግ ይሆናል። (ቆላ. 3:​8, 12) ይህንን አድርገህ ከሆነ ደግሞ የድምፅ አወጣጥን ማስተካከል ሊረዳህ ይችላል። ጉሮሮህንና መንገጭላህን ዘና ለማድረግ ሞክር። ይህም ድምፅህ ለመስማት ደስ የሚል እንዲሆን ከማድረጉም ሌላ አፍህን በደንብ ሳትከፍት በመቅረትህ ምክንያት ድምፅህ እንዳይታፈን ይረዳሃል።

ማሻሻል የሚቻልበት መንገድ

  • ክርስቲያናዊ ባሕርያትን አዳብር።

  • የሳንባህ የታችኛው ክፍል በአየር እንዲሞላ በማድረግ በአግባቡ መተንፈስ ተለማመድ።

  • በምትናገርበት ጊዜ የጉሮሮህ፣ የአንገትህ፣ የትከሻህና የሰውነትህ ጡንቻዎች ዘና እንዲሉ አድርግ።

መልመጃ፦ (1) ለአንድ ሳምንት ያህል በየቀኑ ለጥቂት ደቂቃዎች የሳንባህን የታችኛውን ክፍል በአየር መሙላት በሚያስችል መንገድ መተንፈስን ተለማመድ። (2) ለአንድ ሳምንት ቢያንስ በየቀኑ አንድ ጊዜ፣ ስትናገር ሥራዬ ብለህ የጉሮሮ ጡንቻዎችህን ዘና ለማድረግ ሞክር።

    አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
    ውጣ
    ግባ
    • አማርኛ
    • አጋራ
    • የግል ምርጫዎች
    • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
    • የአጠቃቀም ውል
    • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
    • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
    • JW.ORG
    • ግባ
    አጋራ