በስተ ግራ፦ አንዲት ኮልፖርተር በኮሪያ ስትሰብክ፣ 1931፤ በስተ ቀኝ፦ በዛሬው ጊዜ በኮሪያ በምልክት ቋንቋ ሲሰበክ
ክፍል 2
የመንግሥቱ ስብከት ሥራ—ምሥራቹን በዓለም ዙሪያ ማሰራጨት
በእረፍት ቀንህ በጠዋት አገልግሎት ለመውጣት እየተዘጋጀህ ነው። ትንሽ ድካም ስለተሰማህ ልውጣ ወይስ ልቅር ብለህ ታመነታለህ። የጠዋቱን ጊዜ አረፍ ብለህ ማሳለፍ አምሮሃል! ሆኖም ወደ ይሖዋ ከጸለይክ በኋላ አገልግሎት ለመውጣት ትወስናለህ። ከዚያም ከአንዲት ታማኝ አረጋዊት እህት ጋር አገልግሎት ወጣህ፤ የእኚህን እህት ጽናትና ደግነት ስትመለከት ልብህ ተነካ። ከቤት ወደ ቤት እየሄዳችሁ የእውነትን መልእክት ለሰዎች ስታካፍሉ፣ እንደ አንተው ዓይነት ሥልጠና ያገኙ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ወንድሞችህና እህቶችህም አንተ የያዝካቸው ዓይነት ጽሑፎችን በመጠቀም ይህንኑ መልእክት ለሰዎች እንደሚሰብኩ ወደ አእምሮህ ይመጣል። አገልግሎትህን ጨርሰህ ወደ ቤትህ ስትመለስ ኃይልህ እንደታደሰ ይሰማሃል። ቤት ከመቅረት ይልቅ አገልግሎት ለመውጣት በመወሰንህ በጣም ትደሰታለህ!
በአሁኑ ጊዜ የአምላክ መንግሥት የሚያከናውነው ዋነኛ ተግባር ክርስቲያኖች ምሥራቹን እንዲሰብኩ ማድረግ ነው። ኢየሱስ የስብከቱ ሥራ በመጨረሻው ቀን በስፋት እንደሚከናወን አስቀድሞ ተናግሯል። (ማቴ. 24:14) ይህ ትንቢት ፍጻሜውን እያገኘ ያለው እንዴት ነው? በዚህ ክፍል ውስጥ፣ ከክርስቲያናዊው አገልግሎት ጋር በተያያዘ ትልቅ ሚና እየተጫወቱ ስላሉት ሰዎች እንዲሁም ስለሚጠቀሙባቸው ግሩም ዘዴዎችና መሣሪያዎች እንመረምራለን፤ ክርስቲያኖች የሚያከናውኑት ይህ አገልግሎት በዓለም ዙሪያ ያሉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የአምላክ መንግሥት እውን እንዲሆንላቸው አድርጓል።