-
ማቴዎስ 22:15-22አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ
-
-
15 ከዚያም ፈሪሳውያን ሄደው በንግግሩ ሊያጠምዱት ሴራ ጠነሰሱ።+ 16 ስለዚህ ደቀ መዝሙሮቻቸውን ከሄሮድስ ሥርወ መንግሥት ደጋፊዎች+ ጋር ወደ እሱ በመላክ እንዲህ አሉት፦ “መምህር፣ አንተ እውነተኛ እንደሆንክና የአምላክን መንገድ በትክክል እንደምታስተምር እንዲሁም ለመወደድ ብለህ ምንም ነገር እንደማታደርግ፣ የሰውንም ውጫዊ ማንነት አይተህ እንደማትፈርድ እናውቃለን። 17 እስቲ ንገረን፣ ምን ይመስልሃል? ለመሆኑ ለቄሳር ግብር መክፈል ይገባል ወይስ አይገባም?”* 18 ኢየሱስ ግን ክፋታቸውን አውቆ እንዲህ አላቸው፦ “እናንተ ግብዞች፣ ለምን ትፈትኑኛላችሁ? 19 እስቲ ለግብር የሚከፈለውን ሳንቲም አሳዩኝ።” እነሱም አንድ ዲናር* አመጡለት። 20 እሱም “ይህ ምስልና የተቀረጸው ጽሑፍ የማን ነው?” አላቸው። 21 እነሱም “የቄሳር” አሉ። እሱም “እንግዲያው የቄሳር የሆነውን ለቄሳር፣ የአምላክ የሆነውን ደግሞ ለአምላክ ስጡ” አላቸው።+ 22 ይህን ሲሰሙ ተደነቁ፤ ከዚያም ትተውት ሄዱ።
-
-
ሉቃስ 20:20-26አዲስ ዓለም ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ
-
-
20 በቅርብ ሲከታተሉት ከቆዩ በኋላ በንግግሩ እንዲያጠምዱት ጻድቅ መስለው የሚቀርቡ ሰዎችን በድብቅ ቀጥረው ላኩ፤+ ይህን ያደረጉት ለመንግሥትና ለአገረ ገዢው* አሳልፈው ለመስጠት ነው። 21 የተላኩትም ሰዎች እንዲህ ሲሉ ጠየቁት፦ “መምህር፣ አንተ ትክክለኛውን ነገር እንደምትናገርና እንደምታስተምር እንዲሁም እንደማታዳላ፣ ከዚህ ይልቅ የአምላክን መንገድ በእውነት እንደምታስተምር እናውቃለን፦ 22 ለመሆኑ ለቄሳር ግብር መክፈል ይገባናል ወይስ አይገባንም?”* 23 እሱ ግን ተንኮላቸው ገብቶት እንዲህ አላቸው፦ 24 “እስቲ አንድ ዲናር* አሳዩኝ። በላዩ ላይ ያለው ምስልና የተቀረጸው ጽሑፍ የማን ነው?” እነሱም “የቄሳር” አሉ። 25 እሱም “እንግዲያው የቄሳር የሆነውን ለቄሳር፣+ የአምላክ የሆነውን ደግሞ ለአምላክ+ ስጡ” አላቸው። 26 እነሱም በሕዝቡ ፊት በንግግሩ ሊያጠምዱት አልቻሉም፤ ከዚህ ይልቅ በመልሱ በመገረም ዝም አሉ።
-