‘የአንበሳ ልብ’ ሊኖርህ ይችላል
መጽሐፍ ቅዱስ አልፎ አልፎ አንበሳን የድፍረትና የልበ ሙሉነት ምሳሌ አድርጎ ይጠቀምበታል። ጀግና ወይም ደፋር የሆኑ ሰዎች ‘የአንበሳ ልብ’ እንዳላቸው ተደርገው ተገልጸዋል፤ በተጨማሪም ጻድቃን “እንደ አንበሳ ያለ ፍርሃት ይኖራሉ” ሊባል ይቻላል። (2 ሳሙኤል 17:10፤ ምሳሌ 28:1) አንበሳ በተለይ ከሌሎች እንስሳት ጋር በሚጣላበት ጊዜ ‘በእንስሳት መካከል ብርቱ’ ነው የሚለው ስሙ የሚገባው እንደሆነ ያስመሰክራል።—ምሳሌ 30:30 የ1980 ትርጉም
ይሖዋ አምላክ ሕዝቡን ለመጠበቅ ያደረገውን ውሳኔ ከአንበሳ ድፍረት ጋር አመሳስሎታል። ኢሳይያስ 31:4, 5 እንዲህ ይላል፦ “አንበሳ ወይም የአንበሳ ደቦል በንጥቂያው ላይ ሲያገሣ፣ ብዙ እረኞች ቢከማቹበት ከቃላቸው እንደማይፈራ ከድምፃቸውም እንደማይዋረድ፣ እንዲሁ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር በጽዮን ተራራና በኮረብታዋ ላይ ይዋጋ ዘንድ ይወርዳል። . . . ኢየሩሳሌምን ይጋርዳታል ይከልላታል፣ ይታደጋታል፣ አልፎም ያድናታል።” በዚህ መሠረት ይሖዋ በተለይ አገልጋዮቹ መከራ ሲደርስባቸው እንክብካቤ እንደሚያደርግላቸው አረጋግጦላቸዋል።
መጽሐፍ ቅዱስ ታላቁን የሰው ዘር ጠላት ማለትም ሰይጣን ዲያብሎስን በጣም ተርቦ ከሚያገሳ አንበሳ ጋር ያነጻጽረዋል። እንዳንዋጥ ከፈለግን ‘የማስተዋል ስሜታችንን እንድንጠብቅና ንቁዎች እንድንሆን’ ቅዱሳን ጽሑፎች ይመክሩናል። (1 ጴጥሮስ 5:8 አዓት) እንዲህ ለማድረግ የሚያስችለን አንዱ መንገድ ገዳይ የሆነው መንፈሳዊ ድብታ እንዳይዘን መጠንቀቅ ነው። ይህን በተመለከተ ኢየሱስ “ልባችሁ በመጠጥ ብዛትና በስካር ስለ ትዳርም በማሰብ እንዳይከብድ፣ . . . ለራሳችሁ ተጠንቀቁ” ብሏል። (ሉቃስ 21:34-36) አዎን፣ በእነዚህ ‘የመጨረሻ ቀናት’ በመንፈሳዊ ንቁ መሆን ‘የአንበሳ ልብ’ ይኸውም ‘በይሖዋ ላይ ጽኑ እምነት ያለው’ ልብ ይሰጠናል።—2 ጢሞቴዎስ 3:1፤ መዝሙር 112:7, 8