በእምነታቸው ምሰሏቸው
1. ታኅሣሥ 21 ከሚጀምር ሳምንት አንስቶ በጉባኤ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ላይ ምን እናጠናለን?
1 ታኅሣሥ 21, 2015 በሚጀምረው ሳምንት በእምነታቸው ምሰሏቸው የተባለውን መጽሐፍ በጉባኤ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ላይ ማጥናት እንጀምራለን። ይህ መጽሐፍ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሱ 14 ታማኝ ወንዶችና ሴቶችን ታሪክ ያብራራል። ይህ መጽሐፍ እነዚህን ታማኝ ሰዎች በዓይነ ሕሊናችን እንድንስላቸው በሚያደርግ መንገድ የተዘጋጀ ሲሆን እነዚህ ሰዎች ይሖዋን ሲያገለግሉ የተለያዩ ችግሮች ያጋጠሟቸው፣ በእርግጥ በሕይወት የነበሩ ሰዎች መሆናቸውን እንድንገነዘብ ይረዳናል። በተጨማሪም መጽሐፉ ከእነዚህ ዘገባዎች የምናገኘውን ተግባራዊ ሊሆን የሚችል ትምህርት ይጠቁመናል።—ዕብ. 6:12
2. በእምነታቸው ምሰሏቸው የተባለው መጽሐፍ ምን ገጽታዎች አሉት?
2 የመጽሐፉ ገጽታዎች፦ መጽሐፉ እያንዳንዱ ባለታሪክ መቼና የት እንደኖረ የሚጠቁም የጊዜ ሰሌዳና ካርታ አለው። በተጨማሪም እያንዳንዱ ምዕራፍ “ሊታሰብባቸው የሚገቡ ነጥቦች” የሚል ገጽታ ያለው ሲሆን ይህ ገጽታ በታሪኩ ላይ እንድናሰላስልና የተማርነውን ተግባራዊ እንድናደርግ ይረዳናል። ከዚህም በተጨማሪ መጽሐፉ በጥንቃቄ ምርምር የተደረገባቸውና ዝርዝር መረጃ የያዙ ማራኪና ውብ ሥዕሎችን አካቷል፤ ይህም ታሪኩን በዓይነ ሕሊናችን እንድንስለው ይረዳናል።
3. ከዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ጥቅም ለማግኘት ምን ማድረግ እንችላለን?
3 ጥቅም ማግኘት የምትችሉት እንዴት ነው? ከበላይ አካሉ የተላከው መልእክት የሚከተለውን ማበረታቻ ይዟል፦ “ክንውኖቹን በዓይነ ሕሊናችሁ ለመመልከት ጣሩ፤ ሕያው ሆነው ይታዩአችሁ። በመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባው ላይ የተጠቀሱት ባለ ታሪኮች የተሰማቸው ስሜት ይሰማችሁ፣ እነሱ ያዩትን ነገር እናንተም ለማየት ጣሩ። በሕይወታቸው ውስጥ አንድ ነገር ሲያጋጥማቸው ምን ምላሽ እንደሰጡ ስታነቡ እናንተ ብትሆኑ ምን ታደርጉ እንደነበር ለማሰብ ሞክሩ።” እርግጥ ነው፣ ታሪኩን በዓይነ ሕሊናችን እንስላለን ሲባል የራሳችንን መላ ምት በመጠቀም የሌለ ታሪክ እንፈጥራለን ማለት ሳይሆን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያለው ታሪክ ሕያው እንዲሆንልን እናደርጋለን እንዲሁም ራሳችንን በባለታሪኮቹ ቦታ አስቀምጠን ለማሰብ እንሞክራለን ማለት ነው። እንዲህ ማድረግ ጊዜ ሰጥቶ ማሰላሰል ይጠይቃል። (ነህ. 8:8) ጥናቱ የሚጀምረው ከአንድ ምዕራፍ መካከል ከሆነ የሚመራው ወንድም ከ30 እስከ 60 ሴኮንድ በሚያህል ጊዜ ውስጥ ያለፈውን ትምህርት በመከለስ ይጀምራል። የጥናት ፕሮግራሙ “ሊታሰብባቸው የሚገቡ ነጥቦች” የሚለውን ገጽታ የማያካትት በሚሆንበት ጊዜ ጥናቱን የሚመራው ወንድም መደምደሚያ ላይ አንድ ወይም ሁለት ጥያቄዎችን ተጠቅሞ ትምህርቱን ሊከልስ ይችላል።
4. በእምነታቸው ምሰሏቸው የተባለውን መጽሐፍ ማጥናታችን አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?
4 በዚህ ዓለም ውስጥ እምነታችንን ሊሸረሽሩ ወይም ሊያዳክሙ የሚችሉ የተለያዩ ነገሮች ያጋጥሙናል። ይህ መጽሐፍም ሆነ “በእምነታቸው ምሰሏቸው” በሚል ዓምድ ሥር በመጠበቂያ ግንብ ላይ በተከታታይ የሚወጡት ርዕሶች እምነታችንን ማጠናከር እንድንችል ይሖዋ ያዘጋጀልን ስጦታዎች ናቸው። (ያዕ. 1:17) ይህን መጽሐፍ በጉባኤ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ላይ በሚጠናበት ጊዜ አዘውትረን በስብሰባው ላይ በመገኘትና በተቻለ መጠን የተሟላ ተሳትፎ በማድረግ ጥቅም ለማግኘት እንጣር።