የሞት መውጊያ ይወገዳል
ሞት በተፈጥሮ ያለ ነገር ነው ወይም የተለመደ ነገር ነው የሚል ጽሑፍ ብናነብ እንግዳ አይሆንብንም። በመጽሐፍ ቅዱስ መዝገብ መሠረት ግን ሁኔታው ከዚህ የተለየ ነው። ሞት በኃጢአት ምክንያት የመጣ ጠላት ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በሮሜ 5:12 ላይ “ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት፣ እንደዚሁም ሁሉ ኃጢአትን ስላደረጉ ሞት ለሰው ሁሉ ደረሰ” በማለት ይናገራል።
አምላክ የሰው ዘር እንዲሞት ዓላማው ስላልነበረ በፍቅር ተነሣስቶ ከሞት መላቀቅ የሚቻልበትን መንገድ አዘጋጅቷል። የሞትን ቅጣት ለማስወገድ ልጁ ለእኛ ሲል እንዲሞት በማድረግ ተመጣጣኝ ቤዛ አዘጋጅቷል። (ማቴዎስ 20:28፤ 1 ዮሐንስ 2:2) የሰውን ዘር በሙሉ የሚያስተዳድረውን አዲስ መንግሥት ጨምሮ ምድራዊ ገነት እንደሚያመጣ ቃል ገብቷል። ይህ መንግሥት ኃጢአትና ሞት ያስከተሏቸውን ነገሮች በሙሉ ጠራርጎ ያጠፋል። (ሉቃስ 18:30) መጽሐፍ ቅዱስ በራእይ 21:3,4 ላይ “እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ይሆናል፤ እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፣ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፣ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፣ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና” ይላል። ስለሞቱት ሰዎችስ ምን ሊባል ይቻላል?
የትንሣኤ ተስፋ አላቸው። ፍጹም ጤናማ የሆነ አካልና አእምሮ ይዘው በገነቲቷ ምድር ላይ እንደገና በሕይወት የመኖር ተስፋ አላቸው። አዎን፣ “በመቃብር ያሉቱ ሁሉ ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል፤ . . . ይወጣሉና።” (ዮሐንስ 5:28, 29) የሰውን ዘር ለመቤዠት በአምላክ የተላከው ኢየሱስ ክርስቶስ “ልጅንም አይቶ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለምን ሕይወት እንዲያገኝ የአባቴ ፈቃድ ይህ ነው፣ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ” በማለት ተጨማሪ ማረጋገጫ ይሰጠናል።—ዮሐንስ 6:40
የሚያፈቅሩት ሰው በሞት የተለያቸው ብዙ ሰዎች የተጽናኑት በዚህ የትንሣኤ ተስፋ አማካኝነት ነው። የሚያፈቅሯቸው ሰዎች “በሞት ያንቀላፉ” ብቻ መሆኑን ይገነዘባሉ፤ ስለዚህም “ተስፋ እንደሌላቸው እንደሌሎቹ ሰዎች” አያዝኑም። (1 ተሰሎንቄ 4:13፣ ዘ ኒው ኢንግሊሽ ባይብል) አምላክ አመጣዋለሁ ብሎ ቃል በገባለት አዲስ የነገሮች ሥርዓት ውስጥ እንደገና በአንድነት ተገናኝተው የሚደሰቱበትን ጊዜ ይጠባበቃሉ። ማጽናኛና ተስፋ በሚሰጠው አምላክ ይታመናሉ።—ሮሜ 15:4,13፤ 2 ቆሮንቶስ 1:3፤ 2 ተሰሎንቄ 2:16
የይሖዋ ምስክሮች የቀብር ሥርዓቶች ከሌሎቹ ሁሉ ለየት ብለው የሚታዩት በዚህ ምክንያት ነው። ምስክሮቹ የአምላክን ሞገስ ለማግኘት ሲሉ ከቃሉ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚጋጭ ማንኛውንም ልማድ ያስወግዳሉ። ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጪ በሆኑ እምነቶች ላይ የተመሠረቱ ወጎችና ልማዶች ቦታ የላቸውም። እውነተኛውን አምላክ ይሖዋን ብቻ ስለሚያመልኩ ለሞቱ ሰዎች አምልኮታዊ አክብሮት አይሰጡም። አምላክን እንደማያስደስተው ስለሚያውቁ ሀብትን ወይም የኑሮ ደረጃን የሚያንጸባርቅ የታይታ ሥርዓት አያካሂዱም። (1 ዮሐንስ 2:16) የቀብር ሥርዓታቸው ቀለል ያለና ሥርዓታማ ነው፤ ዘመድ የሞተባቸውን ሰዎች ልብም ለማረጋጋት ይረዳል። የሞተውን ሰው በማስታወስ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘውን ተስፋ የሚገልጽ ንግግር ይሰጣል። የይሖዋ ምስክሮች ያለቅሳሉ፤ ከሚገባው በላይ ግን አይደለም።
የይሖዋ ምስክሮች “የኋለኛው ጠላት . . . ሞት” በቅርቡ እንደሚወገድ ያውቃሉ። ከዚያም የሚከተሉት ትንቢታዊ ቃላት ፍጻሜያቸውን ያገኛሉ:—“ሞት ድል በመነሣት ተዋጠ ሞት ሆይ፣ መውጊያህ የት አለ? ሲኦል [ሞት አዓት] ሆይ፣ ድል መንሣትህ የት አለ?”—1 ቆሮንቶስ 15:26, 54, 55