ክፍል 1
አምላክ ስለ እኛ በእርግጥ ያስባልን?
1, 2. ሰዎች ስለ አምላክ የሚጠይቁት ጥያቄ ምንድን ነው? ለምንስ?
በሕይወትዎ ውስጥ በአንድ ወቅት ላይ ‘በእርግጥ የሚያስብልን አምላክ ካለ ይህን ያህል ብዙ መከራ እንዲመጣብን የፈቀደው ለምንድን ነው?’ ብለው ጠይቀው ይሆናል። ሁላችንም መከራ በራሳችን ላይ ደርሶ አይተናል፤ ወይም መከራ የደረሰበት ሰው እናውቃለን።
2 በታሪክ ዘመናት በሙሉ ሰዎች በጦርነት፣ በጭካኔ ድርጊት፣ በወንጀል፣ በፍትሕ መዛበት፣ በድህነት፣ በበሽታና የሚያፈቅሩትን የቤተሰብ አባል በሞት በማጣት ምክንያት መከራና የልብ ሰቆቃ ደርሶባቸዋል። በሃያኛው መቶ ዘመናችን ብቻ በተደረጉ ጦርነቶች ከ100 ሚልዮን በላይ ሰዎች ሞተዋል። በመቶ ሚልዮኖች የሚቆጠሩ ሌሎች ሰዎች ደግሞ በጦርነቶቹ ጉዳት ደርሶባቸዋል፣ ወይም ቤት ንብረታቸውን አጥተዋል። በዘመናችን ቁጥር ስፍር በሌላቸው ሰዎች ላይ ታላቅ ኀዘን፣ ብዙ እንባና የተስፋ መቁረጥ ስሜት ያስከተሉ እጅግ ብዙ አሰቃቂ ነገሮች ደርሰዋል።
3, 4. አምላክ መከራ እንዲኖር ስለመፍቀዱ ብዙ ሰዎች ምን ይሰማቸዋል?
3 አንዳንዶች በኀዘን ክፉኛ ከመመረራቸው የተነሣ አምላክ ቢኖርም እንኳ ስለ እኛ ምንም ደንታ የለውም የሚል ስሜት አድሮባቸዋል። ወይም ደግሞ እስከነጭራሹ አምላክ እንደሌለ ይሰማቸው ይሆናል። ለምሳሌ ያህል በመጀመሪያው የዓለም ጦርነት ወቅት የወዳጆቹንና የቤተሰቦቹን ሞት ያስከተለ የጎሣ ስደት ያጋጠመው አንድ ሰው “በችግራችን ጊዜ አምላክ የት ነበረ?”ብሎ ጠይቋል። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት በናዚዎች ከተገደሉት በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች መሃል የተረፈ አንድ ሰው በተመለከተው ስቃይ በጣም አዝኖ “በምላሳችሁ ልቤን ብትቀምሱት መርዝ መርዝ ይላችኋል” ብሏል።
4 እዚህ ላይ እንደምንመለከተው ብዙ ሰዎች አንድ ደግ የሆነ አምላክ መጥፎ ነገሮች እንዲደርሱ ለምን እንደሚፈቅድ ሊገባቸው አይችልም። ስለ እኛ የሚያስብ ስለመሆኑ ወይም ደግሞ ጭራሽኑ መኖሩንም ይጠራጠራሉ። ከእነርሱም መካከል ብዙዎቹ ሥቃይ ምን ጊዜም የሰው ኑሮ ክፍል ሆኖ የሚኖር ይመስላቸዋል።
[በገጽ 2, 3 ላይ የሚገኝ ሥዕል]
መከራ የሌለበት ዓለም በቅርቡ ይመጣልን?