ጥናት 28
በጭውውት መልክ መናገር
ሰዎች ከወዳጆቻቸው ጋር የሚጨዋወቱት ዘና ብለው ነው። እንዴት ብዬ ልናገር ብለው አይጨነቁም። አንዳንዶች በጣም ተጫዋች ሲሆኑ ሌሎች ደግሞ ትንሽ ቁጥብ ሊሆኑ ይችላሉ። ያም ሆነ ይህ ለጆሮ ደስ የሚለው አንድ ሰው በራሱ ተፈጥሮአዊ አነጋገር ሲያወራ ነው።
ይሁንና ከማታውቀው ሰው ጋር ስትነጋገር እንደ ቆሎ ጓደኛህ አድርገህ ልትመለከተው አይገባም። እንዲያውም በአንዳንድ ባሕሎች ከማታውቀው ሰው ጋር ስትነጋገር መጀመሪያ ላይ የምትጠቀምባቸው ቃላት አክብሮትህን የሚያሳዩ ናቸው። እየተወያያችሁ ስትሄዱ ግን ዘና ባለ መንገድ በጭውውት መልክ መነጋገሩ ጥሩ ሊሆን ይችላል።
ንግግር ስታቀርብም ቢሆን መጠንቀቅ ይኖርብሃል። አነጋገርህ ተራ ወሬ ከመሰለ የስብሰባውን አክብሮት የሚቀንስ ከመሆኑም በላይ መልእክቱ ክብደት እንዳይኖረው ሊያደርግ ይችላል። በአንዳንድ ቋንቋዎች ከትልቅ ሰው፣ ከመምህር፣ ከባለ ሥልጣን ወይም ከወላጅ ጋር ስትነጋገር አንዳንድ መግለጫዎችን መጠቀም ይጠበቅብሃል። (በሥራ 7:2 እና 13:16 ላይ የተሠራባቸውን ቃላት ልብ በል።) ከትዳር ጓደኛህ ወይም ከቅርብ ወዳጅህ ጋር ስትነጋገር የምትጠቀምባቸው መግለጫዎች ደግሞ የተለዩ ናቸው። ንግግር ስትሰጥ አነጋገርህ አክብሮት የተሞላበት ሊሆን ይገባል። ይሁንና ከልክ በላይ ስለ ቋንቋ ሕግጋት መጨነቅ አለብህ ማለት አይደለም።
ይሁንና የአንድ ሰው አነጋገር ድርቅ ያለ እንዲሆን ምክንያት ሊሆኑ የሚችሉ ነገሮች አሉ። ከእነዚህ አንዱ የዓረፍተ ነገሩ አወቃቀር ወይም የሐረጎቹ አቀማመጥ ነው። ብዙውን ጊዜ በጽሑፍ ቋንቋና በንግግር ቋንቋ መካከል ልዩነት ስላለ አንድ ተናጋሪ ጽሑፍ ላይ ያለውን በቀጥታ ለመናገር የሚሞክር ከሆነ ንግግሩ ድርቅ ያለ ይሆናል። በአብዛኛው ንግግሩን ለመዘጋጀት ምርምር በምታደርግበት ጊዜ የተለያዩ ጽሑፎችን እንደምትጠቀም የታወቀ ነው። ንግግሩን የምታቀርበውም ተዘጋጅቶ ከተሰጠህ አስተዋጽኦ ሊሆን ይችላል። ይሁን እንጂ ቃል በቃል ከጽሑፍ የተወሰደ አነጋገር ለመጠቀም የምትሞክር ወይም በንግግርህ ወቅት ከአስተዋጽኦው በቀጥታ የምታነብብ ከሆነ ንግግርህ በጭውውት መልክ የቀረበ ሊሆን እንደማይችል የታወቀ ነው። ሐሳቡን በራስህ አባባል የምትናገርና የምትጠቀምባቸው ዓረፍተ ነገሮች ቀለል ያሉ ከሆኑ ንግግርህ የጭውውት መልክ ያለው ይሆናል።
ሌላው ምክንያት ደግሞ የአነጋገር ፍጥነትህ ነው። በየቃላቱ መካከል ያለው ክፍተት እኩል ከሆነና ፍጥነትህም አንድ ወጥ ከሆነ ንግግሩ ድርቅ ያለ ይሆናል። ዕለት ተዕለት ከሰዎች ጋር ስንጨዋወት የምንናገረው ፍጥነታችንን እየለዋወጥንና በተለያዩ ቦታዎች እንደሁኔታው ቆም እያልን ነው።
እርግጥ የአድማጮችህ ቁጥር ብዙ በሚሆንበት ጊዜ በትኩረት እንዲከታተሉህ ለማድረግ በጭውውት መልክ ከመናገርም በተጨማሪ የድምፅህን መጠንና ኃይል ልትጨምር እንዲሁም በጋለ ስሜት ልትናገር ይገባል።
ለአገልግሎትም የሚጠቅምህን በጭውውት መልክ የመናገር ችሎታ ለማዳበር በየዕለቱ ጥሩ የአነጋገር ልማድ ሊኖርህ ይገባል። ይህን ለማድረግ የግድ ከፍተኛ ትምህርት ያለህ መሆን አያስፈልግህም። ይሁንና ሌሎች በአክብሮት እንዲያዳምጡህ የሚያደርግ ጥሩ የአነጋገር ልማድ ሊኖርህ ይገባል። ከዚህ አንጻር በዕለት ተዕለት አነጋገርህ ልታሻሽላቸው የሚገቡ ነገሮች ይኖሩ እንደሆነ ለመመርመር የሚከተሉትን ነጥቦች ልብ በል።
ከሰዋስው ሕግ ውጭ የሆነ ወይም የአምላክን ሕግ የሚያቃልል አኗኗር ካላቸው ሰዎች የሚያስመድብ የአነጋገር ልማድ እንዳይኖርህ ተጠንቀቅ። በቆላስይስ 3:8 ላይ በሚገኘው ምክር መሠረት ሸካራ ከሆነና ከብልግና አነጋገር ራቅ። በሌላ በኩል ግን በተለመደው የዕለት ተዕለት አነጋገር መጠቀም ምንም ስህተት የለበትም። ይህ ዓይነቱ አነጋገር ሙሉ በሙሉ የቋንቋውን ሥርዓት የጠበቀ ላይሆን ቢችልም ተቀባይነት አለው።
የተለያዩ ሐሳቦችን የምትገልጸው ሁልጊዜ ተመሳሳይ ቃላትና ሐረጎችን እየተጠቀምህ መሆን የለበትም። ከዚህ ይልቅ መናገር የፈለግኸውን ሐሳብ ቁልጭ አድርገው የሚገልጹ ቃላትን መጠቀም ልመድ።
የተናገርከውን ሳያስፈልግ ወደኋላ ተመልሶ የመድገም ልማድ ካለህ ልታስወግደው ይገባል። ይህንንም ማድረግ እንድትችል ከመናገርህ በፊት መጀመሪያ ሐሳቡ ግልጽ ሊሆንልህ ያስፈልጋል።
ቃላት በማብዛት ጠቃሚ የሆነው ሐሳብ እንዲድበሰበስ አታድርግ። ሌሎች እንዲያስታውሱት የምትፈልገውን ነጥብ በአጭር ቃል የመናገር ልማድ ይኑርህ።
ለሰዎች አክብሮት እንዳለህ በሚያሳይ መንገድ ተናገር።