ወግ ሁልጊዜ ከእውነት ጋር ይጋጫልን?
ማርቲን ሉተር እርሱ ትክክል እንደሆነ አጥብቆ ያምን ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ የሚደግፈው መስሎት ነበር። በሌላ በኩል የፖላንዱ የከዋክብት ተመራማሪ ኮፐርኒከስ በጊዜው የነበረው በወግ ላይ የተመሠረተ እምነት ስህተት እንደሆነ ያስብ ነበር።
የትኛው እምነት? መሬት የጽንፈ ዓለሙ እምብርት ስትሆን ሌሎች ነገሮች ሁሉ በእርሷ ዙሪያ ይዞራሉ የሚለው እምነት ነው። እውነቱ ኮፐርኒከስ መሬት ራሷ በፀሐይ ዙሪያ እንደምትዞር የተናገረው ነበር። ሉተር እንደሚከተለው በማለት ይህንን እውነት እንደማይቀበለው አሳይቷል፦ “ሰዎች የሰማይ አካላት የሆኑት ፀሐይና ጨረቃ ሳይሆኑ መሬት እንደምትዞር ለማሳየት ደፋ ቀና ለሚል ዛሬ ለበቀለ የከዋክብት ተመራማሪ ጆሯቸውን ይሰጣሉ።”—ሂስትሪ ኦቭ ዌስተርን ፊሎዞፊ
በወግ ላይ የተመሠረቱ እምነቶች ብዙውን ጊዜ ከሐቁ ወይም ከእውነቱ ጋር ይጋጫሉ። እንዲያውም ሰዎች ጎጂ የሆኑ ነገሮችን እንዲፈጽሙ ያደርጋሉ።
እንዲህ ሲባል ግን ወግ ሁልጊዜ ከእውነት ጋር ይጋጫል ማለት አይደለም። እንዲያውም ሐዋርያው ጳውሎስ እርሱ ያስተላለፋቸውን ወጎች እንዲጠብቁ በዘመኑ የነበሩትን ክርስቲያኖች እንደሚከተለው በማለት አበረታቷቸዋል፦ “አሳልፌ እንደ ሰጠኋችሁ ወግን ፈጽማችሁ ስለ ያዛችሁ አመሰግናችኋለሁ።”—1 ቆሮንቶስ 11:2፤ በተጨማሪም 2 ተሰሎንቄ 2:15፤ 3:6 ተመልከት።
ጳውሎስ “ወግ” ብሎ ሲናገር ምን ማለቱ ነበር? ቅዱሳን ጽሑፎችን ጠለቅ ብሎ ማስተዋል ጥራዝ 2 ገጽ 1118 ጳውሎስ “ወግን” ለማመልከት የተጠቀመበት የግሪክኛ ቃል ፓራዶሲስ እንደሆነ ይገልጻል። ፓራዶሲስ ማለት “በአፈ ታሪክ ወይም በጽሑፍ የተላለፈ” ማለት ነው። የእንግሊዝኛው ቃል “ከወላጆች ወደ ልጆች የተላለፈ እውቀት፣ መሠረተ ትምህርት ወይም ድርጊት አለዚያም የተለመደ አስተሳሰብ ወይም ተግባር” ያመለክታል።a ሐዋርያው ጳውሎስ ያስተላለፋቸው ወጎች ምንጫቸው ጥሩ ስለነበር ክርስቲያኖች አጥብቀው ቢይዟቸው ይጠቀሙ ነበር።
ያም ሆነ ይህ ወግ እውነት ወይም ውሸት፣ ጥሩ ወይም መጥፎ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ የእንግሊዙ ፈላስፋ በርትራንድ ራስል በወግ ላይ የተመሠረቱ እምነቶችን አጠያያቂ ለማድረግ በ16ኛው መቶ ዘመን ይኖር እንደነበረው እንደ ኮፐርኒከስ የመሳሰሉትን ሐቀኛና ደፋር ሰዎች አመስግኗል። እነዚህ ሰዎች “ከጥንት ዘመን ጀምሮ ይታመንባቸው የነበሩ ነገሮች ውሸት ሊሆኑ እንደሚችሉ የሚያሳይ አስተሳሰብ” አስፋፍተዋል። አንተስ ወግን በጭፍን መከተል ጥበብ አለመሆኑ ይታይሃልን?—ከማቴዎስ 15:1–9, 14 ጋር አወዳድር።
ስለ ሃይማኖታዊ እምነቶችና ልማዶችስ ምን ለማለት ይቻላል? ትክክልና ጉዳት እንደሌለባቸው አድርገን መውሰድ እንችላለንን? ከእውነት ጋር እንደሚጋጩና እንደማይጋጩ እንዴት ማወቅ እንችላለን? ሃይማኖታዊ ወጎች ከእውነት ጋር እንደሚጋጩ ካወቅን ምን ማድረግ አለብን? የሚቀጥለው ርዕስ እነዚህን ጥያቄዎች ይመረምራል።
[የግርጌ ማስታወሻ]
a ኒው ዮርክ በሚገኘው የመጠበቂያ ግንብ የመጽሐፍ ቅዱስና ትራክት ማኅበር የተዘጋጀ።
[ምንጭ]
Cover: Jean-Leon Huens © National Geographic Society
[ምንጭ]
Universität Leipzig