ሀብታምና ጠቢብ የነበረ ንጉሥ
ሀብት ደስተኛ ያደርገኛል ብለህ ታስባለህን? አንድ ሰው ብዙ ገንዘብ ቢሰጥህ ደስ አይልህም? ደስ እንደሚልህ አያጠራጥርም። እንዲያውም እንዴት አድርገህ ጥቅም ላይ ልታውለው እንደምትችል እንደምታስብ የታወቀ ነው።
በእርግጥ ሕይወትን ምቾት ያለውና አስደሳች ለማድረግ ስትል የምትገዛቸው ብዙ ነገሮች አሉ። በተጨማሪም ገንዘብ ድንገት ለሚከሰቱ እንደ ሕመም ወይም ሥራ አጥነት ከመሳሰሉት ችግሮች “ጥላ” ሆኖ ሊያገለግል ይችላል።—መክብብ 7:12
ይሁን እንጂ በገንዘብና በደስታ መካከል ያለው ዝምድና ምንድን ነው? ብዙዎች እንደሚያስቡት ደስታን የሚያስገኘው ሀብት ነው ብለህ ታስባለህ? ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት ከባድ ሊሆን ይችላል። ምክንያቱም ገንዘብን በቀላሉ መመዘን ወይም መቁጠር ይቻላል፤ ደስታን ግን አይቻልም። ደስታን በሚዛን ልትመዝነው አትችልም።
ከዚህም በላይ አንዳንድ ሀብታም ሰዎች ደስተኛ የሆኑ ይመስላሉ፤ ሌሎቹ ደግሞ ብስጩዎች ናቸው። ድሃ በሆኑ ሰዎችም ረገድ ተመሳሳይ ነገር ይታያል። ያም ሆኖ ግን አብዛኞቹ ሰዎች፣ ሀብታም የሆኑትም ሳይቀሩ ብዙ ገንዘብ ባገኙ ቁጥር ደስታቸው የዚያኑ ያህል እንደሚጨምር ያስባሉ።
በጥንቷ እስራኤል ንጉሥ የነበረው ሰሎሞን ስለ እነዚህ ጉዳዮች ጽፏል። በምድር ላይ ከኖሩት እጅግ ሀብታም ሰዎች መካከል አንዱ ነበር። በመጽሐፍ ቅዱሱ የአንደኛ ነገሥት መጽሐፍ ምዕራፍ 10 ላይ ስለ ሀብቱ ብዛት የሰፈረውን መግለጫ ማንበብ ትችላለህ። ለምሳሌ ያህል ቁጥር 14 ምን እንደሚል ልብ በል:- “በየዓመቱ ለሰሎሞን የሚመጣለት የወርቅ ሚዛን ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት መክሊት ወርቅ ነበረ።” (በሰያፍ የጻፍነው እኛ ነን።) ይህ 25 ቶን ወርቅ ማለት ነው። በዛሬው ጊዜ ይህን የሚያክል ወርቅ ከ200,000,000 የአሜሪካ ዶላር በላይ ያወጣል!
ይሁንና ሰሎሞን ሀብታም ሰው ብቻ አልነበረም፤ አምላክ ጥበብ በመስጠት ባርኮት ነበር። መጽሐፍ ቅዱስ “ንጉሡም ሰሎሞን በባለጠግነትና በጥበብ ከምድር ነገሥታት ሁሉ በልጦ ነበር። ምድርም ሁሉ እግዚአብሔር በልቡ ያኖረለትን ጥበቡን ይሰማ ዘንድ የሰሎሞንን ፊት ይመኝ ነበር” ይላል። (1 ነገሥት 10:23, 24) እሱ የጻፋቸው ነገሮች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በመሆናቸው እኛም ከሰሎሞን ጥበብ ልንጠቀም እንችላለን። በሀብትና በደስታ መካከል ያለውን ዝምድና አስመልክቶ የተናገረውን እንመልከት።
[በገጽ 3 ላይ የሚገኝ ሥዕል]
Reproduced from Die Heilige Schrift - Übersetzt von Dr. Joseph Franz von Allioli. Druck und Verlag von Eduard Hallberger, Stuttgart