በእርግጥ ስለ እኛ የሚያስብ ይኖር ይሆን?
“የተገፉት ሰዎች እንባ” እንደ ጅረት እየፈሰሰ ነው። ይህ በመላው ዓለም ላይ በሚፈጸመው “ግፍ” የተጠቁ ሰዎች የሚያነቡት እንባ ነው። እነዚህ ሰዎች አብዛኛውን ጊዜ “የሚያጽናናቸው” እንደሌለ በሌላ አባባል ስለ እነርሱ ማንም እንደማያስብ ይሰማቸዋል።—መክብብ 4:1
ምንም እንኳ እንባ እንዲህ እንደ ጅረት ቢፈስም አንዳንዶች እንደ እነርሱ ባሉ ሰብዓዊ ፍጡራን ላይ የሚደርሰው ሥቃይና መከራ ምንም ደንታ አይሰጣቸውም። ኢየሱስ ክርስቶስ በወንበዴዎች ተደብድቦ መንገድ ዳር ተጥሎ ስለነበረው ሰው በተናገረው ምሳሌ ላይ እንደተጠቀሱት ካህንና ሌዋዊ እነዚህም ሌሎች ሰዎች የሚደርስባቸውን ሥቃይ አይተው እንዳላዩ ሆነው ያልፋሉ። (ሉቃስ 10:30-32) ዘመዶቻቸውና ቤተሰቦቻቸው ደህና እስከሆኑ ድረስ ስለ ሌሎች ምንም ግድ አይሰጣቸውም። ሁኔታቸው “ሌላው የራሱ ጉዳይ” የሚሉ ያህል ነው።
ይህ ሁኔታ ፈጽሞ ሊያስደንቀን አይገባም። ሐዋርያው ጳውሎስ “በመጨረሻው ቀን” ብዙ ሰዎች “የተፈጥሮ ፍቅር” እንደሚጎድላቸው ተንብዮአል። (2 ጢሞቴዎስ 3:1, 3 NW) አንድ ታዛቢ እየታየ ያለውን የግዴለሽነት ዝንባሌ በተመለከተ አማርረው ተናግረዋል። “ተሳስቦና ተካፍሎ መኖር የሚለው የጥንቱ የአይሪሾች ግብረገብና ባህል አሁን ከራስ በላይ ንፋስ በሚለው አዲስ ፈሊጥ ተተክቷል” ብለዋል። በዓለም ዙሪያ ሰዎች ለሌሎች ችግር ደንታ ቢስ በመሆን የራሳቸውን ጥቅም የሚያሳድዱ ሆነዋል።
ለሌሎች የሚያስብ አካል ያስፈልጋል
ለሌሎች የሚያስብ አካል መኖር እንዳለበት ምንም ጥያቄ የለውም። ለምሳሌ ያህል “ከሞተ ከአምስት ዓመት በኋላ ቴሌቪዥኑ ፊት ለፊት ቁጭ እንዳለ በገና ዕለት ስለተገኘው” በጀርመን ይኖር ስለነበረው ብቸኛ ሰው አስብ። በሕይወቱ ውስጥ በደረሰበት አሳዛኝ ገጠመኝ የተደቆሰው “ትዳሩ የፈረሰበትና የአካል ጉዳተኛ የሆነ ይህ ብቸኛ ሰው” ለቤት አከራዮቹ የሚከፍለው በባንክ ያስቀመጠው ገንዘብ እስኪያልቅ ድረስ ማንም ያስታወሰው አልነበረም። በእርግጥም፣ የት ወደቀ ብሎ ያሰበው ሰው አልነበረም።
በተጨማሪም ስግብግብ በሆኑ ፈላጭ ቆራጭ ገዥዎች እጅ እየተሰቃዩ ስላሉት ምስኪን ሰዎች አስብ። በአንድ አካባቢ የሚኖሩ 200,000 (የሕዝቡ አንድ አራተኛ) የሚሆኑ ሰዎች መሬታቸውን በኃይል ከተነጠቁ በኋላ “በደረሰባቸው ጭቆናና ረሃብ አልቀዋል።” ወይም ለማመን የሚከብድ አረመኔያዊ የጭካኔ ድርጊት ሲፈጸም የተመለከቱትን ሕፃናት ወደ አእምሮህ ልታመጣ ትችላለህ። አንድ ሪፖርት ሲናገር “አልፎ አልፎ ልጆች ጭምር የተካፈሉበት እንደ ግድያ፣ ድብደባ፣ አስገድዶ መድፈር የመሳሰሉትን በጣም ሰቅጣጭ የሆኑ ድርጊቶች ሲፈጸሙ የተመለከቱ [በአንድ አገር] የሚኖሩ ሕፃናትን ብዛት ለመገመት የሚያዳግት ነው” ብሏል። ይህ ዓይነት ግፍ የተፈጸመበት ሰው እንባው በጉንጮቹ ላይ እየፈሰሰ “በእርግጥ ስለእኔ የሚያስብ ይኖራልን?” ብሎ የሚጠይቅበት ምክንያት ሊገባህ ይችላል።
የተባበሩት መንግሥታት ባወጣው ሪፖርት መሠረት በታዳጊ አገሮች የሚኖሩ 1.3 ቢልዮን ሰዎች ኑሯቸውን የሚገፉት በቀን ከአንድ የአሜሪካ ዶላር ባነሰ ገቢ ነው። እነዚህ ሰዎች የሚያስብልን ይኖራል ብለው ለመገመት እንደሚቸገሩ የታወቀ ነው። ዚ አይሪሽ ታይምስ መጽሔት ላይ የወጣ አንድ ዘገባ እንደገለጸው “በጣም አስቀያሚ በሆነ ካምፕ ወይም ጥሩ ፊት በማያሳዩአቸው ባዕድ አገር እንቆይ ወይስ በጦርነት ወይም በጎሳ ግጭት ወደተገነጣጠለችው [ወይም ወደተከፋፈለችው] ትውልድ አገራችን እንመለስ በሚለው ለመወሰን አስቸጋሪ በሆነ አጣብቂኝ ውስጥ የገቡት” በሺህ የሚቆጠሩ ስደተኞች ሁኔታም ተመሳሳይ ነው። ይኸው ሪፖርት የሚከተለውን አስደንጋጭ ስሌት ይዞ ነበር:- “ዓይንህን ጨፍንና እስከ ሦስት ቁጠር፣ በዚች ቅጽበት አንድ ልጅ ሞቷል። ዛሬ በተመጣጠነ ምግብ እጥረት ወይም በቀላሉ ሊድን በሚችል በሽታ ከሚሞቱት 35,000 ሕፃናት መካከል ይህ አንዱ ብቻ ነው።” ብዙዎች በጭንቀትና በምሬት እሮሮ ማሰማታቸው ምንም አያስደንቅም!—ከኢዮብ 7:11 ጋር አወዳድር።
መጀመሪያውኑም ይህ ሁሉ እንዲህ እንዲሆን ታስቦ ነበርን? ነገሩን ምክንያታዊ ሆነን ካየነው ሥቃይን ለማስቆምና በሰዎች ላይ እየደረሱ ያሉትን ሕመሞች ለመፈወስ ችሎታ ያለው አንድም አካል የለም ማለት ነው?
[በገጽ 2 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]
Cover and page 32: Reuters/Nikola Solic/Archive Photos
[ምንጭ]
A. Boulat/Sipa Press