ቲኦክራሲያዊ ዜናዎች
ኬንያ፦ ከሚያዝያ 10 እስከ ሚያዝያ 14,1994 ድረስ ናይሮቢ በሚገኘው ቅርንጫፍ ቢሮ የሆስፒታል አገናኝ ኮሚቴ ሴሚናር ተካሂዷል። ሥልጠናው የተሰጣቸው ወንድሞች በቅርንጫፉ ሥር ካሉት ከአብዛኞቹ አገሮች እንዲሁም ከህንድ፣ ከፓኪስታንና ከስሪላንካ የመጡ ነበሩ። በብሩክሊን ከሚገኘው የማኅበሩ ዋና መሥሪያ ቤት የመጡ አስተማሪዎች ጥሩ ሥልጠና ሰጥተዋቸዋል። በኢትዮጵያ ውስጥ የተቋቋመው የሆስፒታል አገናኝ ኮሚቴም ሥራውን ስለጀመረ በዚህ ዝግጅት አማካኝነት ብዙ ጥቅም እንደምናገኝ እንጠብቃለን።
ግንቦት 1, 1994 በምሥራቅ አፍሪካ ለመጀመሪያ ጊዜ በተካሄደው የአገልጋዮች ማሠልጠኛ ትምህርት ቤት የተካፈሉ 25 ተማሪዎች የምረቃ ቀን ነበር። በምረቃው ላይ የተገኙት 294 ተሰብሳቢዎች በቀረበው የሚያነቃቃ ፕሮግራም የተደሰቱ ሲሆን ተማሪዎቹ ወደ ተመደቡባቸው በምሥራቅ አፍሪካ የሚገኙ 6 አገሮች ሲሄዱ መልካሙን ሁሉ ተመኝተውላቸዋል። ከተማሪዎቹም መካከል ከኢትዮጵያ የሄዱ ሁለት ተማሪዎች ነበሩ።
ጃፓን፦ የካቲት ብዙ በረዶ የጣለበትና ከፍተኛ ቅዝቃዜ የነበረበት ወር ነበር። ይሁን እንጂ 188,844 የሚሆን አዲስ ከፍተኛ የአስፋፊዎች ቁጥር ላይ ተደርሷል። በተመላልሶ መጠየቆች፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶችና በዘወትር አቅኚዎችም በኩል ከፍተኛ ቁጥር ነበራቸው።