የጥያቄ ሣጥን
◼ የተመደበው የሕዝብ ተናጋሪ በስብሰባ ላይ በሰዓቱ በማይገኝበት ጊዜ ምን መደረግ ይኖርበታል?
አንድ ወንድም ከአቅም በላይ የሆኑ ሁኔታዎች አጋጥመውት በሰዓቱ ደርሶ ንግግሩን እንዳያቀርብ ሊያደርጉት ይችላሉ። ተናጋሪው ሰዓት አሳልፎ ይመጣል ብለው ካሰቡ ሽማግሌዎች የመጠበቂያ ግንብ ጥናት ለማስቀደም ሊወስኑ ይችሉ ይሆናል። ከዚያም ሕዝባዊ ስብሰባው ሊከተል ይችላል። ይሁን እንጂ ተናጋሪው ጨርሶ እንደማይመጣ ቢታወቅስ? በጉባኤ ያለ አንድ ተናጋሪ አስቀድሞ የተዘጋጀውን ማንኛውንም ዓይነት ንግግር ሊያቀርብ ይችላል።
ቀደም ሲል የተደረገ ጥንቃቄ የተሞላበት እቅድ እንዲህ የመሰለ ችግር እንዳይከሰት ሊከላከል ይችላል። የሕዝብ ንግግር ተናጋሪዎችን የሚጋብዘው ወንድም እያንዳንዱን የሕዝብ ንግግር ተናጋሪ ቢያንስ አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ማስታወስ ይኖርበታል። ከሚያስታውሳቸው ነገሮች መካከል ስብሰባው የሚጀምርበትን ሰዓት፣ መንግሥት አዳራሹ የሚገኝበትን ቦታና ስልክ ቁጥሩን ያካትታል። እንዲሁም መሰብሰቢያ ቦታውን እንዴት ሊያገኝ እንደሚችል ግልጽ የሆነ አቅጣጫ ሊያመለክተው ይገባል። ተናጋሪውም እነዚህን ዝርዝሮች በጥንቃቄ በማስታወሻ ደብተሩ ላይ መመዝገብ ይገባዋል። ኃላፊነቱን ሙሉ በሙሉ ለመወጣት እንዲችል ለግል ጉዳዮቹ ተገቢ የሆነ ማስተካከያዎችን በማድረግ የተሰጠውን የሥራ ድርሻ በቁም ነገር መያዝ ይኖርበታል። ንግግሩን ለማቅረብ እንዳይችል የሚያደርጉ ከአቅም በላይ የሆኑ ችግሮች ካጋጠሙት በእርሱ ምትክ ሌላ ተናጋሪ ማዘጋጀት እንዲችል የሕዝብ ንግግር እንዲያቀርብ የጋበዘውን ወንድም አግኝቶ ማነጋገር ይኖርበታል። በመጨረሻው ደቂቃ ላይ ንግግሩ እንዳይሰረዝ ማንኛውንም ዓይነት ጥረት ማድረግ ይገባል። ተናጋሪው ዘግይቶ ጥቂት ደቂቃዎችን የሚያሳልፍ ከሆነ ወንድሞች ምን ነገር ማድረግ እንዳለባቸው እንዲወስኑ ስልክ ሊደውልላቸው ይችላል።
የሕዝብ ንግግር ለማቅረብ የተሰጠንን ኃላፊነት በአድናቆት ማየት፣ ቀደም ብሎ እቅድ ማውጣትና ተናጋሪዎችን ቀደም ብሎ ማስታወስ እንዲሁም ጥንቃቄ የተሞላበት ቁጥጥር ማድረግ ጉባኤው ጠቃሚ የሆኑ የሕዝብ ንግግሮች በየሳምንቱ እንዲኖረው ያስችላሉ።