ሰዎች በሚገኙበት ቦታ ሁሉ መመሥከር
1 ሐዋርያው ጳውሎስ የአምላክ መንፈስ በአገልግሎቱ ውስጥ የተጫወተውን ሚና በመገንዘብ “እግዚአብሔር ያሳድግ ነበር” በማለት ተናግሯል። በተጨማሪም “ከእርሱ ጋር አብረን የምንሠራ ነን” ሲል ገልጿል። (1 ቆሮ. 3:5-9) ይህ ግሩም መብት ነው። ከአምላክ ጋር አብረን መሥራታችንን እንደምናደንቅ በግልጽ ልናሳይ የምንችለው እንዴት ነው? ከቤት ወደ ቤትም ይሁን በየትኛውም ቦታ ለምናገኛቸው ሰዎች ምሥራቹን በማወጅ ነው።
2 ‘ሰዎችን ደቀ መዛሙርት እንድናደርግ’ ታዘናል። (ማቴ. 28:19) በአገልግሎት ላይ የምናገኘው ጥቂት ሰዎችን ብቻ ከሆነ ቶሎ ልንደክምና ብዙም እንዳልሠራን ሊሰማን ይችላል። በሌላ በኩል ደግሞ ብዙ ሰዎችን አግኝተን ከእነርሱ ጋር ለመነጋገር ከቻልን አገልግሎታችን አስደሳች ይሆንልናል። ይህ ደግሞ ሰዎችን ለማግኘት ያሉበት ቦታ ድረስ ለመሄድ የግል ተነሳሽነትን ስለሚጠይቅ ፈታኝ ሊሆን ይችላል።
3 ጠቃሚ ምሳሌዎች፦ በገበያዎች፣ በመናፈሻዎች፣ ሰዎች አረፍ በሚሉባቸው አካባቢዎችና በመጓጓዣ ጣቢያዎች ለምናገኛቸው ሰዎች ልንመሰክር እንችላለን። በሕዝብ መጓጓዣ በምትጠቀምበት ጊዜ በጉዞህ ወቅት ለመመስከር ዝግጁ ነህን? ሁለት ምሥክሮች በተጨናነቀ አውቶቡስ ተሳፍረው ወደ መስክ ስምሪት ስብሰባ በመሄድ ላይ እያሉ እውቀት በተባለው መጽሐፍ ላይ የሚገኘውን የገነት ሥዕል ገልጠው አምላክ ወደፊት እንደሚያመጣ ቃል ስለገባቸው ተስፋዎች ይወያዩ ነበር። እንዳሰቡትም ከአጠገባቸው ቆሞ የነበረ አንድ ወጣት የሚሉትን በማዳመጡ በሰማው ነገር ተነካ። ከአውቶቡስ ከመውረዱ በፊት አንድ መጽሐፍ የወሰደ ሲሆን እቤቱ መጥቶ የሚያነጋግረው ሰው እንደሚፈልግ ገለጸላቸው።
4 ብዙ አስፋፊዎች መደበኛ ባልሆነ መንገድ መመስከርን አስደሳች ሆኖ አግኝተውታል። አንዲት እህት አንድ ቀን ከሰዓት በኋላ በአቅራቢያዋ ወደሚገኝ የገበያ ማዕከል ሄዳ የሚፈልጉትን ነገር ገዝተው የጨረሱትንና የቸኮሉ የማይመስሉትን ሰዎች ቀረብ ብላ ማነጋገር ጀመረች። በቦርሳዋ ውስጥ የነበረውን ጽሑፍ በሙሉ አበረከተች። መኪና ውስጥ ቁጭ ብሎ ሰው ይጠብቅ የነበረ አንድ ሰው መጽሔቶቹን ስትሰጠው ተደሰተ። ከዚህ በፊት በስብሰባዎች ላይ ተገኝቶ ስለሚያውቅ ከእህት ጋር ያደረገው ውይይት ፍላጎቱን እንደገና አነሳስቶለታል።
5 የይሖዋን ስም ማወደስ ልዩ መብት ነው። በስብከቱ ሥራ በቅንዓት በመካፈል አምላክ ያሳየንን ይገባናል የማንለውን ደግነት ዓላማ እንዳልሳትን እናሳያለን። ሌሎችን ለመርዳት “የተወደደው ሰዓት አሁን” ስለሆነ ሰዎች ሊገኙ በሚችሉበት ቦታ ሁሉ በመሄድ ስለ ይሖዋ “የመዳን ቀን” እንመስክርላቸው።—2 ቆሮ. 6:1, 2