አዲስ የወረዳ ስብሰባ ፕሮግራም
ፍርሃት የሚለው ቃል አንዱ ትርጉም “በተለይ ለአምላክ የምናሳየውን ጥልቅ አክብሮታዊ ፍርሃት” ያመለክታል። ይህ በቅዱሳን ጽሑፎች ውስጥ “የጥበብ መጀመሪያ” ተብሎ የተጠቀሰውን ጤናማ ፍርሃት ያመለክታል። (መዝ. 111:10) ከዚህ በተቃራኒው ደግሞ በዙሪያችን ያለው የሰይጣን ዓለም በሌላ ዓይነት ፍርሃት ተውጧል። ለይሖዋ ጥልቅ የሆነ አክብሮታዊ ፍርሃት በማዳበር ከዚህ ጤናማ ያልሆነ ፍርሃት መራቅ የምንችለው እንዴት ነው? የ2002 የአገልግሎት ዓመት የወረዳ ስብሰባ ፕሮግራም ለዚህ ጥያቄ መልስ ይሰጣል። ጭብጡ “እግዚአብሔርን ፍሩ ክብርንም ስጡት” የሚል ነው። (ራእይ 14:7) ይሖዋን መፍራት በግለሰብም ሆነ በድርጅት ደረጃ ሊጠቅመን የሚችልባቸውን መንገዶች እንማራለን።
ምንም እንኳን ፍርሃት መሸበርን ወይም ወኔ ማጣትንና አስቸጋሪ ሁኔታዎችን ከመጋፈጥ ወደኋላ ማለትን ሊያመለክት ቢችልም መጽሐፍ ቅዱስ “እግዚአብሔርን የሚፈሩት ሁሉ . . . ምስጉኖች [“ደስተኞች፣” NW ] ናቸው” በማለት ይናገራል። (መዝ. 128:1) የስብሰባው ፕሮግራም ከእውነተኛው አምልኮ ጋር በተያያዘ የሚመጡ ፈታኝ ሁኔታዎችን እንዴት በተሳካ መንገድ እንደምንወጣ ይጠቁመናል። አዲሶች አምላክን በሙሉ ልባቸው፣ ነፍሳቸው፣ አሳባቸውና ኃይላቸው ለማገልገል እንዲነሳሱ የሚገፋፋቸውን ይህን ጤናማ የሆነ አምላካዊ ፍርሃት እንዲያዳብሩ እንዴት መርዳት እንደምንችል እንመለከታለን። (ማር. 12:30) የመጀመሪያው ቀን ስብሰባ “ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ ወደምትወዷቸው ቅረቡ” በሚል ርዕስ የአውራጃ የበላይ ተመልካቹ በሚያቀርበው ንግግር ይደመደማል። ወንድም በንግግሩ ላይ ዲያብሎስ እኛን ከይሖዋ፣ ከቤተሰባችንና ከክርስቲያናዊ ወንድሞቻችን ለማራቅ የሚያደርገውን ጥረት እንዴት በንቃት መከታተል እንደምንችል ያብራራል።
በሁለተኛው ቀን የሚቀርበው ባለ አራት ክፍል ሲምፖዚየም ርዕሱ “ሰዎችን ሳይሆን ይሖዋን ፍሩ” የሚል ነው። ይህ ሲምፖዚየም አገልግሎታችንን በተሟላ መንገድ እንዳናከናውን ወይም በትምህርት ቤትና በሥራ ቦታ የሥነ ምግባር አቋማችንንና ንጹህ ሕሊናችንን እንዳንጠብቅ እንቅፋት የሚሆንብንን ማንኛውም ዓይነት ፍርሃት ለምንና እንዴት ማስወገድ እንዳለብን ያብራራል። የሕዝብ ንግግሩ “አምላክን ፍሩ ትእዛዛቱንም ጠብቁ” የሚል ርዕስ ያለው ሲሆን በራእይ ምዕራፍ 14 ውስጥ በተገለጹት ተከታታይ ክንውኖች ላይ የተመሠረተ ነው። የወረዳ ስብሰባው “ይሖዋን በመፍራት መመላለሳችሁን ቀጥሉ” በሚለው አበረታች ንግግር ይደመደማል።
የቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት፣ የናሙና የአገልግሎት ስብሰባ፣ የጥምቀት ንግግርና የመጠበቂያ ግንብ ፍሬ ሐሳብ ሊያመልጡህ የማይገቡ ሌሎች የፕሮግራሙ ክፍሎች ናቸው። የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶችህ አብረውህ በስብሰባው ላይ እንዲገኙ ጋብዛቸው። ለመጠመቅ የሚፈልጉ ሁሉ ለሰብሳቢ የበላይ ተመልካቹ አሁኑኑ ማሳወቅ አለባቸው። ሁላችንም ከዚህ ግሩም ስብሰባ አንድም ክፍል እንዳያመልጠን በማድረግ ለይሖዋ ጤናማ ፍርሃት እንዳለንና ለእርሱም ክብር እንደምንሰጥ እናሳያለን!