ለመዝናኛ ገደብ አብጁ
1 በእነዚህ አስቸጋሪ ቀናት ሁላችንም በየጊዜው ፋታ ማግኘት ያስፈልገናል። በተወሰነ መጠን መዝናናት ተገቢ ነው። ይሁን እንጂ አንድ ሰው በመዝናኛና በማኅበራዊ ጉዳዮች የሚያጠፋው ጊዜ ከልክ ካለፈ ለመንፈሳዊ ጉዳዮች የሚውለው ጊዜ በጣም እየቀነሰ ሊሄድ ይችላል። ለመዝናኛ የምናውለው ጊዜ በልክ ሊሆን ይገባል። (ማቴ. 5:3) እንዲህ ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው? በኤፌሶን 5:15-17 ላይ የሚገኘውን ምክር በመከተል ነው።
2 ገደብ አብጁለት:- ጳውሎስ ክርስቲያኖች ሕይወታቸውን እንዴት በጥበብ እንደሚመሩ ‘በጥንቃቄ ሊጠበቁ’ እንደሚገባ ጽፏል። መዝናኛ ከልኩ እንዳያልፍ ገደብ ለማበጀት ልከኝነትና ራስን መግዛት አስፈላጊ ነው። ትርፍ ጊዜያችንን የምናሳልፍበትን መንገድ በተመለከተ በቁም ነገር ልናስብበት ይገባል። መዝናኛ፣ ጊዜያችንን በከንቱ እንዳባከንን እንዲሰማን ወይም በድካም እንድንዝል የሚያደርገን ሳይሆን ጠቃሚ ዓላማ የሚያከናውን ሊሆን ይገባል። በአንድ ዓይነት እንቅስቃሴ ከተካፈልን በኋላ የባዶነት ስሜት ከተሰማን እንዲሁም እርባና እንዳልነበረውና ጸጸት ብቻ እንዳተረፍን ከተሰማን በጊዜ አጠቃቀም ረገድ ማስተካከያ ማድረግ ያስፈልገናል።
3 ምክንያታዊ ሁኑ:- ጳውሎስ ‘ምክንያተ ቢስ’ [NW ] እንዳንሆን ይልቁንም በሕይወታችን ውስጥ ይበልጥ አስፈላጊ ለሆኑት ነገሮች ‘ጊዜ እንድንዋጅ’ ምክር ሰጥቷል። ራሳቸውን የወሰኑ ክርስቲያኖች ሕይወታቸው በመዝናኛ ላይ እንዲያተኩር መፍቀድ አይኖርባቸውም። ዕረፍትና መዝናኛ ኃይላችንን ሊያድስልን ቢችልም መንፈሳዊ ኃይል የምናገኝበት ምንጭ የአምላክ አንቀሳቃሽ ኃይል ነው። (ኢሳ. 40:29-31) መንፈሱን የምናገኘው በቲኦክራሲያዊ እንቅስቃሴዎች በመሳተፍ ይኸውም መጽሐፍ ቅዱስን በማጥናት፣ በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ በመገኘትና በመስክ አገልግሎት ላይ በመካፈል እንጂ በመዝናናት አይደለም።
4 ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ነገሮች አስቀድሙ:- ጳውሎስ “የጌታ ፈቃድ ምን እንደ ሆነ አስተውሉ” ሲል ክርስቲያኖችን መክሯል። ኢየሱስ ለአምላክ መንግሥት በሕይወታችን ቀዳሚውን ቦታ በመስጠት ሌሎች ተግባሮቻችን በዚያ ላይ ያተኮሩ መሆን እንዳለባቸው አስተምሯል። (ማቴ. 6:33) ሕይወታችንን ለይሖዋ ስንወስን ከገባነው ቃል ጋር በሚስማማ መንገድ መኖር ለሚያስችሉን ጉዳዮች ቅድሚያ መስጠታችን ግድ ነው። ከዚያ በኋላ መዝናኛ በተገቢው ቦታ ሊቀመጥ ይችላል። እንዲህ ስናደርግ መዝናኛ በጎ ውጤት ይኖረዋል እኛም ይበልጥ ደስታ የምናገኝበት ይሆንልናል።—መክ. 5:12