የጥያቄ ሣጥን
◼ በውጭ አገር ቋንቋ የሚመራ ቡድን ማቋቋም አስፈላጊ የሚሆነው መቼ ነው?
በአንድ የጉባኤ ክልል ውስጥ በውጭ አገር ቋንቋ የሚናገሩ በርካታ ሰዎች ካሉ የጉባኤው ሽማግሌዎች በዚያ ቋንቋ ምሥራቹ የሚሰበክበትን ሁኔታ ለማመቻቸት የሚችሉትን ሁሉ ማድረግ አለባቸው። በውጭ አገር ቋንቋ የሚናገረው ኅብረተሰብ በሁለት ወይም ከዚያ በላይ በሆኑ ጉባኤዎች ክልል ውስጥ ተሠራጭቶ የሚገኝ ሊሆን ይችላል። እንዲህ በሚሆንበት ጊዜ የወረዳ የበላይ ተመልካቾች አስፈላጊውን መመሪያ በመስጠት ጉባኤዎቹ በስብከቱ ሥራ ተባብረው የሚሠሩበትን ሁኔታ ያመቻቻሉ። በዚያ ቋንቋ ስብሰባ ቢካሄድ ምን ያህል ሰዎች ሊገኙ እንደሚችሉ ለማወቅ አልፎ አልፎ የሕዝብ ንግግር ወይም የመጠበቂያ ግንብ ጥናት ማድረግ ይቻላል።
የሚከተሉት መሥፈርቶች የሚሟሉ ከሆነ በውጭ አገር ቋንቋ የሚመራ ቡድን ማቋቋም ይቻላል። (1) በቋንቋው ምሥራቹን በሚገባ ለመረዳት የሚችሉ አስፋፊዎች ወይም ፍላጎት ያሳዩ ሰዎች ሲኖሩ። (2) ቡድኑን በበላይነት መቆጣጠርና ቢያንስ በሳምንት አንድ ጊዜ ስብሰባ መምራት የሚችል ብቃት ያለው ሽማግሌ ወይም የጉባኤ አገልጋይ ሲኖር። (3) የሽማግሌዎች አካል ቡድኑን ለመርዳት ፈቃደኛ ሆኖ ሲገኝ። እነዚህ መሥፈርቶች ከተሟሉ ሽማግሌዎች ቡድኑ እውቅና እንዲያገኝና ተጨማሪ መመሪያዎችም እንዲላኩላቸው ለቅርንጫፍ ቢሮው ማሳወቅ አለባቸው።
አብዛኞቹ ቡድኖች በየሳምንቱ የጉባኤ የመጽሐፍ ጥናት በማድረግ ይጀምራሉ። ከጊዜ በኋላ ሽማግሌዎች እንደ ሕዝባዊ ስብሰባና የመጠበቂያ ግንብ ጥናት ያሉ ተጨማሪ ስብሰባዎች እንዲደረግ ሊወስኑ ይችላሉ። ቋንቋውን መናገር የሚችል ብቃት ያለው ሽማግሌ ወይም የጉባኤ አገልጋይ ምክር በመስጠት ለመርዳት የሚችል ከሆነ በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ክፍል ቁጥር 2, 3 እና 4ን በሁለተኛ አዳራሽ እንዲቀርብ ማድረግ ይቻላል። ይሁን እንጂ የንግግር ባሕርይን አስመልክቶ ለሚቀርበው ንግግር፣ ለማስተማሪያ ንግግር፣ ለመጽሐፍ ቅዱስ ጎላ ያሉ ነጥቦችና ለአገልግሎት ስብሰባ ቡድኑ ከዋናው ጉባኤ ጋር አብሮ ይሰበሰባል። ቡድኑ የራሱን የመስክ አገልግሎት ስምሪት ስብሰባዎችም እንዲያደርግ ማመቻቸት ይቻላል።
ሁሉም የቡድኑ አባላት በሽማግሌዎች አካል አመራር ሥር ተቀራርበው ይሠራሉ። ሽማግሌዎች ሚዛናዊ አመራር መስጠት የሚገባቸው ሲሆን ቡድኑ የሚያስፈልጉትን ነገሮች ለሟሟላት በንቃት ይከታተላሉ። የወረዳ የበላይ ተመልካቹ ዋናውን ጉባኤ ሲጎበኝ ቡድኑን በመንፈሳዊ ለመገንባት አብሯቸው በመስክ አገልግሎት የሚሠራበትን ሁኔታ ያመቻቻል። የይሖዋ በረከት ታክሎበት ይህ በውጭ አገር ቋንቋ የሚመራ ቡድን ከጊዜ በኋላ ጉባኤ ሊሆን ይችላል።