“በፈተና የሚጸና ሰው ደስተኛ ነው”
1 ሁሉም ክርስቲያኖች ፈተናዎችን መጋፈጥ ይኖርባቸዋል። (2 ጢሞ. 3:12) ፈተናው ጤና ማጣት፣ የኢኮኖሚ ችግርና ስደት ወይም ደግሞ ሌላ ዓይነት ሊሆን ይችላል። ሰይጣን ፈተናዎችን የሚያመጣብን በመንፈሳዊ እንዳናድግ፣ ክርስቲያናዊ አገልግሎታችንን ችላ እንድንል አልፎ ተርፎም አምላክን ማገልገላችንን እንድናቆም ለማድረግ ነው። (ኢዮብ 1:9-11) ታዲያ በፈተና መጽናት ደስታ የሚያስገኘው እንዴት ነው?—2 ጴጥ. 2:9
2 ለፈተና ተዘጋጁ:- ይሖዋ ስለ ኢየሱስ ሕይወትና ትምህርቶች የሚናገሩትን ዘገባዎች ያካተተውን የእውነት ቃሉን ሰጥቶናል። የኢየሱስን ቃል በማዳመጥና ተግባራዊ በማድረግ ጠንካራ መሠረት መጣል እንችላለን፤ እንዲህ ማድረጋችን ደግሞ ራሳችንን ለፈተናዎች እንድናዘጋጅ ያስችለናል። (ሉቃስ 6:47-49) ከዚህም በተጨማሪ ከክርስቲያን ወንድሞቻችን፣ ከጉባኤ ስብሰባዎች እንዲሁም ታማኝና ልባም ባሪያ ከሚያዘጋጃቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረቱ ጽሑፎች ብርታት ማግኘት እንችላለን። አምላክ የሰጠንን መብት ተጠቅመን አዘውትረን እንጸልያለን።—ማቴ. 6:13
3 ከዚህም ባሻገር ይሖዋ ተስፋ ሰጥቶናል። ይሖዋ በገባው ቃል ላይ ጠንካራ እምነት ስንገነባ ተስፋችን እንደ “ነፍስ መልሕቅ . . . ጽኑና አስተማማኝ” ይሆንልናል። (ዕብ. 6:19) በመጽሐፍ ቅዱስ ዘመን መርከቦች ጥሩ የአየር ሁኔታ ቢኖርም እንኳ መልሕቅ ሳይዙ በፍጹም ከወደብ አይንቀሳቀሱም ነበር። መርከቦች ድንገት አውሎ ነፋስ ሲነሳ መልሕቃቸውን መጣላቸው በባሕር ዳርቻዎች አካባቢ ካለ ቋጥኝ ጋር ከመላተም ያድናቸዋል። እኛም በተመሳሳይ በአሁኑ ጊዜ አምላክ በሰጣቸው ተስፋዎች ላይ እምነት መገንባታችን እንደ አውሎ ነፋስ ያለ ችግር በሚያጋጥመን ጊዜ እንድንረጋጋ ያስችለናል። ድንገት ችግሮች ሊያጋጥሙን ይችላሉ። ጳውሎስና በርናባስ በልስጥራን በሰበኩበት ወቅት መጀመሪያ ላይ ጥሩ ምላሽ አግኝተው የነበረ ቢሆንም ተቃዋሚዎች የሆኑ አይሁዳውያን በቦታው በደረሱ ጊዜ ሁኔታው ወዲያውኑ ተቀይሯል።—ሥራ 14:8-19
4 ጽናት ደስታ ያስገኛል:- ተቃውሞ እያለም እንኳ በአገልግሎት ጸንተን መቀጠላችን የአእምሮ ሰላም ይሰጠናል። ለክርስቶስ ስንል ውርደትን ለመቀበል በመብቃታችን ደስ ይለናል። (ሥራ 5:40, 41) በፈተና መጽናታችን ትሕትናን፣ ታዛዥነትንና ትዕግሥትን ይበልጥ በተሟላ ሁኔታ እንድናዳብር ይረዳናል። (ዘዳ. 8:16፤ ዕብ. 5:8፤ ያዕ. 1:2, 3) ጽናት በይሖዋ እንድንታመን፣ በሰጣቸው ተስፋዎች ላይ እምነት እንድንጥልና እሱን መጠጊያችን እንድናደርግ ያስተምረናል።—ምሳሌ 18:10
5 የሚደርሱብን ፈተናዎች ጊዜያዊ እንደሆኑ እናውቃለን። (2 ቆሮ. 4:17, 18) ፈተናዎች ለይሖዋ ያለን ፍቅር ምን ያህል ጥልቅ እንደሆነ ለማሳየት የሚያስችል አጋጣሚ ይከፍቱልናል። በፈተና በመጽናት ሰይጣን ላስነሳቸው ክሶች መልስ መስጠት እንችላለን። በመሆኑም ተስፋ አንቆርጥም! “በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ [“ደስተኛ፣” NW] ነው፤ ምክንያቱም ፈተናን ሲቋቋም . . . የሕይወትን አክሊል ያገኛል።”—ያዕ. 1:12