የጥያቄ ሣጥን
◼ ጉባኤዎች ወይም ግለሰቦች፣ የይሖዋ ምሥክሮች ድርጅት ሕጋዊ ኮርፖሬሽኖች የሚጠቀሙባቸውን አርማዎች መጠቀማቸው ተገቢ ነው?
አርማ አንድ ድርጅት በቀላሉ ተለይቶ የሚታወቅበት ስም፣ መለያ ወይም የንግድ ምልክት ነው። የመጠበቂያ ግንብ አርማ፣ ዎችታወር ባይብል ኤንድ ትራክት ሶሳይቲ ኦቭ ፔንሲልቬንያን እንዲሁም ድርጅቱ የሚጠቀምባቸውን ሌሎች ኮርፖሬሽኖች ይወክላል። ዘ ክርስቺያን ኮንግሪጌሽን ኦቭ ጀሆቫስ ዊትነስስ የተሰኘው ኮርፖሬሽን፣ በሚጽፋቸው ደብዳቤዎች ላይ የሚጠቀምበት አርማ የተከፈተ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። የይሖዋ ምሥክሮች የሚጠቀሙባቸው ሌሎች ኮርፖሬሽኖች ደግሞ ከዚህ የተለዩ አርማዎች አሏቸው።
ጉባኤዎች ወይም ግለሰቦች በመንግሥት አዳራሾቻቸው፣ ሕንጻው የመንግሥት አዳራሽ መሆኑን በሚጠቁሙ ምልክቶች፣ በደብዳቤዎቻቸው ወይም በግል ዕቃዎቻቸውና በመሳሰሉት ነገሮች ላይ የሕጋዊ ኮርፖሬሽኖቻችንን አርማ ወይም ስም አሊያም ከእነዚህ ጋር በጣም የሚመሳሰሉ ምልክቶችን መጠቀም አይገባቸውም። የድርጅቱን ምልክቶች መጠቀም የመንግሥት ባለ ሥልጣናት፣ አስፋፊዎች እንዲሁም ሌሎች ሰዎች ጉባኤው ድርጅቱ ከሚጠቀምባቸው ሕጋዊ ኮርፖሬሽኖች ጋር ስላለው ግንኙነት ግራ እንዲጋቡ ሊያደርጋቸው ይችላል። በተመሳሳይም አንድ ግለሰብ ወይም ጉባኤ በሚልካቸው ደብዳቤዎች ላይ እነዚህን አርማዎች መጠቀሙ ደብዳቤውን ከዋናው መሥሪያ ቤት ወይም ከቅርንጫፍ ቢሮው የተላከ ሊያስመስለው ይችላል።
ወደፊት የሚሠራ አንድ የመንግሥት አዳራሽ ንብረትነቱ የመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ቢሆንም እንኳ በመንግሥት አዳራሹ ላይ የማኅበሩን አርማ ወይም ከዚያ ጋር ተመሳሳይነት ያለውን ሌላ ምልክት መጠቀም ተገቢ አይደለም። በአሁኑ ጊዜ በመንግሥት አዳራሾቻቸው ላይ የመጠበቂያ ግንብ አርማ ያላቸው ጉባኤዎች እነዚህን ምልክቶችና ዲዛይኖች መቀየር ብዙ ጊዜ፣ ጉልበትና ወጪ ሊጠይቅ ስለሚችል አፋጣኝ ለውጥ ለማድረግ መሞከር አያስፈልጋቸውም። ይሁን እንጂ የሚደረገው ነገር ቀላልና ብዙ ሥራ የማይጠይቅ ከሆነ አስፈላጊው ለውጥ ለማድረግ ለጉዳዩ ትኩረት ቢሰጥ ጥሩ ነው። ካልሆነ ግን ሕንጻው ወይም ምልክቱ በሚታደስበት ጊዜ ይህን ማድረግ ይቻላል።