በማንኛውም ጊዜ የይሖዋ ምሥክሮች ነን
1. ኢየሱስ በውኃ ጉድጓድ አጠገብ ላገኛት ሴት እንደመሠከረ ከሚናገረው ዘገባ ምን ትምህርት ማግኘት እንችላለን?
1 ኢየሱስ ለሰዓታት በእግሩ ስለተጓዘ ደክሞታል እንዲሁም ጠምቶታል። ደቀ መዛሙርቱ ምግብ ለመግዛት ሄደው ሳለ ትንሽ አረፍ ለማለት ከሳምራውያን ከተማ ውጭ በሚገኝ አንድ የውኃ ጉድጓድ አጠገብ ተቀመጠ። ኢየሱስ ወደ ሰማርያ የሄደው ለመስበክ አልነበረም፤ ከዚህ ይልቅ በገሊላ የሚያደርገውን አገልግሎት ለመቀጠል በሰማርያ በኩል ማለፍ ስለነበረበት ነው። ይሁንና ይህን አጋጣሚ ተጠቅሞ ውኃ ልትቀዳ ለመጣች አንዲት ሴት መሠከረላት። (ዮሐ. 4:5-14) ለምን? ኢየሱስ ‘የታመነና እውነተኛ የይሖዋ ምሥክር’ መሆኑን ዘንግቶ ስለማያውቅ ነው። (ራእይ 3:14) እኛም በማንኛውም ጊዜ የይሖዋ ምሥክሮች በመሆን የኢየሱስን አርዓያ እንከተላለን።—1 ጴጥ. 2:21
2. መደበኛ ባልሆነ መንገድ ለመመሥከር ዝግጁ መሆን የምንችለው እንዴት ነው?
2 ዝግጁ ሁኑ፦ እኛም ሁልጊዜ ጽሑፎች እንዳይለዩን በማድረግ መደበኛ ባልሆነ መንገድ ለመመሥከር ዝግጁ መሆን እንችላለን። በርካታ አስፋፊዎች ሁልጊዜ ትራክቶችን ይዘው በመሄድ በሱቆችና በነዳጅ ማደያዎች ውስጥ ለሚሠሩ እንዲሁም በቀኑ ውስጥ ለሚያገኟቸው ሌሎች ሰዎች ያበረክታሉ። (መክ. 11:6) ብዙ ጊዜ ወደ ተለያዩ ቦታዎች የምትጓዝ አንዲት እህት አነስተኛ መጠን ያለው መጽሐፍ ቅዱስና የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት የተባለውን መጽሐፍ ሁልጊዜ በቦርሳዋ ውስጥ ትይዛለች፤ እንዲሁም አጠገቧ ከሚቀመጡ ሰዎች ጋር ውይይት ለመጀመር ጥረት ታደርጋለች።
3. ውይይት መጀመር የምንችለው እንዴት ነው?
3 ውይይት ጀምሩ፦ መደበኛ ባልሆነ መንገድ ስንመሠክር መጀመሪያ ላይ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ርዕስ ማንሳት አያስፈልገንም። ኢየሱስ በውኃው ጉድጓድ አጠገብ ላገኛት ሴት መሲሕ መሆኑን በመንገር ውይይቱን አልጀመረም። ከዚህ ይልቅ የማወቅ ፍላጎቷን ለማነሳሳት ሲል የሚጠጣ ውኃ እንድትሰጠው ጠየቃት። (ዮሐ. 4:7-9) አንዲት እህት ዓመት በዓል እንዴት እንደነበር ስትጠየቅ ተመሳሳይ የሆነ አቀራረብ መጠቀሟ ውይይት ለመጀመር እንደሚያስችላት ተገንዝባለች። የይሖዋ ምሥክር በመሆኗ በዓሉን እንዳላከበረች ከመግለጽ ይልቅ “በዓሉን ላለማክበር የራሴን ውሳኔ አድርጌያለሁ” በማለት ትመልሳለች። ጠያቂው ጉጉት ስለሚያድርበት ብዙ ጊዜ ምክንያቱን ይጠይቃታል፤ ይህ ደግሞ እህት ለመመሥከር የሚያስችል አጋጣሚ ይከፍትላታል።
4. በማቴዎስ 28:18-20 ላይ ያለው ሐሳብ ለሥራ የሚያነሳሳህ ለምንድን ነው?
4 ኢየሱስ በምድር የነበረውን ቅንዓት የተሞላበት አገልግሎት ቢያጠናቅቅም በዚህ ዘመን በመከናወን ላይ ላለው የስብከት ሥራ አሁንም ትኩረት መስጠቱን ቀጥሏል። (ማቴ. 28:18-20) ስለሆነም እኛም ምሳሌያችን እንደሆነው እንደ ኢየሱስ በማንኛውም ጊዜ ስለ እምነታችን በይፋ ለማወጅ ዝግጁ በመሆን ምንጊዜም ስለ እርሱ እንመሠክራለን።—ዕብ. 10:23