የአምላክ ቃል ለማስተማር ይጠቅማል
1. በ2014 የአገልግሎት ዓመት የምናደርገው የወረዳ ስብሰባ ጭብጥ ምንድን ነው? በስብሰባው ላይ የትኛው ጥያቄ ይብራራል?
1 በአጽናፈ ዓለም ውስጥ እንደ ይሖዋ ያለ ታላቅ “አስተማሪ” የለም። (ኢሳ. 30:20, 21) ይሁንና ይሖዋ የሚያስተምረን እንዴት ነው? ከየትኛውም መጽሐፍ የላቀ አንድ መጽሐፍ ሰጥቶናል፤ ይህ መጽሐፍ በመንፈስ መሪነት የተጻፈው ቃሉ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። ለመሆኑ መለኮታዊው ትምህርት ለአካላችን፣ ለአእምሯችን፣ ለስሜታችንና ለመንፈሳዊነታችን የሚጠቅመን እንዴት ነው? የዚህ ጥያቄ መልስ በ2014 የአገልግሎት ዓመት በሚደረገው የወረዳ ስብሰባ ላይ ይብራራል። የስብሰባው ጭብጥ “የአምላክ ቃል ለማስተማር ይጠቅማል” የሚል ሲሆን በ2 ጢሞቴዎስ 3:16 ላይ የተመሠረተ ነው።
2. ዋና ዋና ነጥቦቹን ለማወቅ የሚያስችለን ለየትኞቹ ጥያቄዎች የምንሰጠው መልስ ነው?
2 ዋና ዋና ነጥቦቹን ፈልጋችሁ ለማግኘት ሞክሩ፦ በፕሮግራሙ ላይ የሚቀርቡትን ዋና ዋና ነጥቦች ለማወቅ የሚረዳን ለሚከተሉት ጥያቄዎች የምንሰጠው መልስ ነው፦
• መለኮታዊው ትምህርት በሕይወታችን ውስጥ ምን ለውጥ ያመጣል? (ኢሳ. 48:17, 18)
• ይሖዋን በሙሉ ጊዜ ለማገልገል ስንል በሕይወታችን ውስጥ ማስተካከያዎችን ማድረግ በምንፈልግበት ጊዜ ስለ ምን ነገር እርግጠኞች መሆን እንችላለን? (ሚል. 3:10)
• ‘እንግዳ ትምህርቶች’ ሲያጋጥሙን ምን ምላሽ መስጠት ይኖርብናል? (ዕብ. 13:9)
• ኢየሱስን “በትምህርት አሰጣጡ” ልንመስለው የምንችለው እንዴት ነው? (ማቴ. 7:28, 29)
• በጉባኤ ውስጥ የሚያስተምሩ ወንድሞች ራሳቸውን ማስተማር የሚኖርባቸው ለምንድን ነው? (ሮም 2:21)
• የአምላክ ቃል ለምን ነገር ይጠቅማል? (2 ጢሞ. 3:16)
• የብሔራት ‘መናወጥ’ ሰዎችን የሚነካው እንዴት ነው? (ሐጌ 2:6, 7)
• ይሖዋ በእኛ ላይ ምን እምነት አለው? (ኤፌ. 5:1)
• ከይሖዋ ትምህርት ላለመውጣት ጥረት ማድረግ ያለብን ለምንድን ነው? (ሉቃስ 13:24)
3. ወቅታዊ በሆነው በዚህ ስብሰባ ላይ ለመገኘትና በጥሞና ለማዳመጥ ቁርጥ ውሳኔ ማድረግ የሚኖርብን ለምንድን ነው?
3 ጳውሎስ በ2 ጢሞቴዎስ ምዕራፍ 3 ላይ የስብሰባው ጭብጥ የተመሠረተበትን ሐሳብ ከመናገሩ በፊት የመጨረሻዎቹን ቀኖች ለይቶ ስለሚያሳውቀው በዓይነቱ ልዩ ስለሆነው ዘመን ሲገልጽ እንዲህ ብሎ ነበር፦ “ክፉ ሰዎችና አስመሳዮች እያሳሳቱና እየተሳሳቱ በክፋት ላይ ክፋት እየጨመሩ ይሄዳሉ።” (2 ጢሞ. 3:13) ስለዚህ እንዳንሳሳት ከፈለግን መለኮታዊውን ትምህርት ማዳመጣችንና በሥራ ላይ ማዋላችን ምንኛ አስፈላጊ ነው! እንግዲያው ወቅታዊ በሆነው በዚህ ስብሰባ ላይ ለመገኘትና ትምህርቱን በጥሞና ለማዳመጥ ቁርጥ ውሳኔ እናድርግ።