ክርስቲያናዊ ሕይወት | ለአዲሱ የአገልግሎት ዓመት ግብ አውጡ
አቅኚነት
መንፈሳዊ ግቦች ማውጣታችን ጉልበታችንን በጥበብ ለመጠቀም ይረዳናል። (1ቆሮ 9:26) ግብ ማውጣት ይህ ሥርዓት ከመደምደሙ በፊት የቀረውን ጊዜ ከሁሉ በተሻለ መንገድ እንድንጠቀምበት ያስችለናል። (ኤፌ 5:15, 16) በቤተሰብ አምልኳችሁ ላይ፣ ለሚቀጥለው የአገልግሎት ዓመት ለምን ግቦች አታወጡም? በዚህ ረገድ እናንተን ለመርዳት ይህ የስብሰባ አስተዋጽኦ ልትደርሱባቸው የምትችሉ አንዳንድ ግቦችን ይዟል። እነዚህ ግቦች ላይ መድረስ ትችሉ እንደሆነ በጸሎት ታግዛችሁ እንድታስቡበት እናበረታታችኋለን።—ያዕ 1:5
ለምሳሌ መላው ቤተሰባችሁ ከተጋገዘ ከመካከላችሁ ቢያንስ አንድ ሰው በዘወትር አቅኚነት መካፈል ይችል ይሆን? የሰዓት ግቡን ማሟላት እንደማትችሉ ከተሰማችሁ ከእናንተ ጋር ተመሳሳይ ሁኔታ ያላቸውን አቅኚዎች ልታማክሩ ትችላላችሁ። (ምሳሌ 15:22) ምናልባትም በቤተሰብ አምልኳችሁ ላይ ለአንድ አቅኚ ቃለ መጠይቅ ማድረግ ትችሉ ይሆናል። ከዚያም ልትከተሏቸው የምትችሏቸውን ፕሮግራሞች በጽሑፍ አስፍሩ። ከዚህ በፊት በአቅኚነት አገልግላችሁ ታውቁ ከነበረ ደግሞ እንደገና በአቅኚነት ለማገልገል ሁኔታችሁ ይፈቅድላችሁ እንደሆነ ቆም ብላችሁ አስቡበት።
ከቤተሰባችሁ መካከል አንዳንዶች ለአንድ ወር ወይም ከዚያ በላይ በረዳት አቅኚነት መካፈል ይችሉ ይሆን? የአቅም ገደብ ካለባችሁ በየቀኑ ለጥቂት ጊዜ በአገልግሎት በማሳለፍ በረዳት አቅኚነት መካፈል ትችሉ ይሆናል። የሙሉ ቀን ሠራተኛ ወይም ተማሪ በመሆናችሁ የተነሳ በሳምንቱ መሃል ባሉት ቀናት ማገልገል ካልቻላችሁ ደግሞ በዓላት ወይም አምስት ቅዳሜና እሁድ ያሏቸውን ወራት መጠቀም ትችላላችሁ። በረዳት አቅኚነት ለማገልገል የምታስቡበትን ጊዜ በቀን መቁጠሪያችሁ ላይ ምልክት አድርጉ፤ እንዲሁም ፕሮግራማችሁን በጽሑፍ አስፍሩ።—ምሳሌ 21:5
ደፋር ሁኑ!—አቅኚዎች የሚለውን ቪዲዮ ተመልከት፤ ከዚያም የሚከተለውን ጥያቄ ለመመለስ ሞክር፦
የእህት አማንድ ተሞክሮ ይሖዋ በአቅኚነት ለመካፈል ሲሉ መሥዋዕት ለሚከፍሉ ክርስቲያኖች ፍቅራዊ እንክብካቤ እንደሚያደርግላቸው የሚያሳየው እንዴት ነው?