የጥናት ርዕስ 19
መዝሙር 6 ሰማያት የአምላክን ክብር ይናገራሉ
ታማኝ መላእክትን ምሰሉ
“መላእክቱ ሁሉ፣ ይሖዋን አወድሱ።”—መዝ. 103:20
ዓላማ
ከታማኞቹ መላእክት ምሳሌ የትኞቹን ትምህርቶች እንደምናገኝ እንመረምራለን።
1-2. (ሀ) ከመላእክት የምንለየው በምንድን ነው? (ለ) ከመላእክት ጋር የሚያመሳስለን ምንድን ነው?
የይሖዋ ሕዝቦች እንደመሆናችን መጠን የእሱን አገልጋዮች ያቀፈ አፍቃሪ ቤተሰብ አባላት ነን። ይህ ቤተሰብ በዓለም ዙሪያ ያሉትን ወንድሞቻችንን እና እህቶቻችንን እንዲሁም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ታማኝ መላእክትን ያካትታል። (ዳን. 7:9, 10) ስለ መላእክት ስናስብ ቶሎ ወደ አእምሯችን የሚመጣው እነሱ ከእኛ ጋር ያላቸው ልዩነት ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ መላእክት የተፈጠሩት ሰዎች ከመፈጠራቸው ከረጅም ጊዜ በፊት ነው። (ኢዮብ 38:4, 7) የመላእክት ኃይል ከእኛ በእጅጉ ይበልጣል። በተጨማሪም መላእክት እጅግ ቅዱስና ጻድቅ ናቸው፤ እኛ ፍጹማን ያልሆንን ሰዎች መቼም ቢሆን በእነሱ ደረጃ ቅዱስና ጻድቅ መሆን አንችልም።—ሉቃስ 9:26
2 ይሁንና እነዚህ ልዩነቶች ቢኖሩም ከመላእክት ጋር የሚያመሳስሉን ብዙ ነገሮች አሉ። ለምሳሌ እኛም እንደ መላእክት የይሖዋን ግሩም ባሕርያት ማንጸባረቅ እንችላለን። እንደ መላእክት ሁሉ እኛም የመምረጥ ነፃነት አለን። እንደ እነሱ ሁሉ እኛም የየራሳችን ስምና ባሕርይ እንዲሁም የተለያዩ ኃላፊነቶች አሉን። በተጨማሪም ከመላእክት ጋር በሚመሳሰል ሁኔታ እኛም ፈጣሪያችንን ማምለክ ያስፈልገናል።—1 ጴጥ. 1:12
3. ከታማኝ መላእክት ምን ትምህርት እናገኛለን?
3 ከመላእክት ጋር በተለያዩ መንገዶች የምንመሳሰል ከመሆኑ አንጻር ከእነሱ ግሩም ምሳሌ ማበረታቻና በርካታ ጠቃሚ ትምህርቶችን ማግኘት እንችላለን። በዚህ ርዕስ ውስጥ የታማኝ መላእክትን ትሕትና፣ ለሰዎች ያላቸውን ፍቅር፣ ጽናታቸውን እንዲሁም የጉባኤው ንጽሕና እንዲጠበቅ ለመርዳት የሚያደርጉትን ጥረት መኮረጅ የምንችለው እንዴት እንደሆነ እንመለከታለን።
መላእክት ትሑት ናቸው
4. (ሀ) መላእክት ትሕትና የሚያሳዩት እንዴት ነው? (ለ) መላእክት ትሑት የሆኑት ለምንድን ነው? (መዝሙር 89:7)
4 ታማኝ መላእክት ትሑት ናቸው። ብዙ ተሞክሮ ያላቸው፣ ኃያልና ጥበበኛ ቢሆኑም ይሖዋ የሚሰጣቸውን መመሪያ ይቀበላሉ። (መዝ. 103:20) ኃላፊነታቸውን በሚወጡበት ጊዜ፣ ስላከናወኗቸው ነገሮች ጉራ አይነዙም፤ ወይም ያላቸውን አስደናቂ ችሎታ በማሳየት ወደ ራሳቸው ትኩረት ለመሳብ አይሞክሩም። ሌሎች ስማቸውን ባያውቁም እንኳ የአምላክን ፈቃድ በደስታ ይፈጽማሉ።a (ዘፍ. 32:24, 29፤ 2 ነገ. 19:35) ለይሖዋ ሊሰጥ የሚገባውን ክብር ለመቀበል ፈጽሞ ፈቃደኞች አይደሉም። መላእክት ይህን ያህል ትሑት የሆኑት ለምንድን ነው? ይሖዋን ስለሚወዱትና በጥልቅ ስለሚያከብሩት ነው።—መዝሙር 89:7ን አንብብ።
5. አንድ መልአክ ለሐዋርያው ዮሐንስ እርማት በሰጠበት ወቅት ትሕትና ያሳየው እንዴት ነው? (ሥዕሉንም ተመልከት።)
5 የመላእክትን ትሕትና የሚያሳይ አንድ ምሳሌ እንመልከት። በስም የማይታወቅ አንድ መልአክ በ96 ዓ.ም. ገደማ ለሐዋርያው ዮሐንስ አስደናቂ ራእይ አሳይቶት ነበር። (ራእይ 1:1) ዮሐንስ ይህን ራእይ ሲያይ ምን አደረገ? ለመልአኩ ለመስገድ ተነሳሳ። ሆኖም ያ ታማኝ መንፈሳዊ ፍጡር ወዲያውኑ “ተጠንቀቅ! ፈጽሞ እንዳታደርገው! እኔ ከአንተም ሆነ [ከወንድሞችህ] ጋር አብሬ የማገለግል ባሪያ ነኝ። ለአምላክ ስገድ!” በማለት ከለከለው። (ራእይ 19:10) እንዴት ያለ ትሕትና የሚንጸባረቅበት ምላሽ ነው! መልአኩ ክብር ወይም ውዳሴ የመቀበል ፍላጎት አልነበረውም። ወዲያውኑ የዮሐንስ ትኩረት በይሖዋ አምላክ ላይ እንዲያርፍ አደረገ። በሌላ በኩል ደግሞ መልአኩ ዮሐንስን አልናቀውም። መልአኩ በይሖዋ አገልግሎት ያሳለፈው ጊዜም ሆነ ኃይሉ ከዮሐንስ እጅግ የሚበልጥ ቢሆንም ከእሱ ጋር አብሮ የሚያገለግል ባሪያ እንደሆነ በትሕትና ገልጿል። በተጨማሪም መልአኩ ለዮሐንስ እርማት መስጠት ቢኖርበትም ይህን አረጋዊ ሐዋርያ አልተቆጣውም፤ ወይም ሸካራ በሆኑ ቃላት አላነጋገረውም። ከዚህ ይልቅ በደግነት አነጋግሮታል። ዮሐንስ ለእሱ ለመስገድ የተነሳሳው በአድናቆት ስለተዋጠ እንደሆነ ተገንዝቦ መሆን አለበት።
መልአኩ ዮሐንስን የያዘው ትሕትና በሚንጸባረቅበት መንገድ ነው (አንቀጽ 5ን ተመልከት)
6. የመላእክትን ትሕትና መኮረጅ የምንችለው እንዴት ነው?
6 የመላእክትን ትሕትና መኮረጅ የምንችለው እንዴት ነው? እኛም ኃላፊነታችንን በምንወጣበት ጊዜ፣ ጉራ ከመንዛት ወይም ላከናወንነው ነገር እውቅና ለማግኘት ከመሞከር መቆጠብ እንችላለን። (1 ቆሮ. 4:7) በተጨማሪም በይሖዋ አገልግሎት ባሳለፍነው ጊዜ ርዝመት ወይም ባሉን የአገልግሎት መብቶች የተነሳ ከሌሎች እንደምንበልጥ ሊሰማን አይገባም። እንዲያውም ያለን ኃላፊነት በጨመረ መጠን ራሳችንን ይበልጥ ዝቅ አድርገን መመልከት ይኖርብናል። (ሉቃስ 9:48) እንደ መላእክት ሁሉ የእኛም ፍላጎት ሌሎችን ማገልገል እንጂ ለራሳችን ክብር ማግኘት አይደለም።
7. ለአንድ ሰው እርማት ወይም ምክር መስጠት ሲያስፈልገን ትሕትና ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?
7 በተጨማሪም ለአንድ ሰው፣ ለምሳሌ ለእምነት ባልንጀራችን ወይም ለልጃችን እርማት ወይም ምክር መስጠት ሲያስፈልገን ትሕትና ማሳየት እንችላለን። አንዳንድ ጊዜ ቀጥተኛ ምክር መስጠት ያስፈልገን ይሆናል። ሆኖም ለዮሐንስ በደግነት እርማት እንደሰጠው መልአክ ሁሉ እኛም የምንመክረውን ግለሰብ ስሜቱን ሳንጎዳ ቀጥተኛ ምክር መስጠት እንችላለን። ከግለሰቡ እንደምንበልጥ አድርገን ራሳችንን የማንመለከት ከሆነ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተውን ምክር አክብሮትና ርኅራኄ በሚንጸባረቅበት መንገድ መስጠት እንችላለን።—ቆላ. 4:6
መላእክት ሰዎችን ይወዳሉ
8. (ሀ) በሉቃስ 15:10 መሠረት መላእክት ለሰዎች ያላቸውን ፍቅር የሚያሳዩት እንዴት ነው? (ለ) መላእክት በስብከቱ ሥራ ምን ሚና ይጫወታሉ? (ሥዕሉንም ተመልከት።)
8 መላእክት ለሰዎች ግድ የማይሰጣቸው ወይም ከሰዎች የራቁ አይደሉም። ሰዎችን ይወዳሉ። አንድ ኃጢአተኛ ንስሐ ሲገባ፣ ማለትም የጠፋ በግ ወደ ይሖዋ ሲመለስ ወይም አንድ ሰው አካሄዱን አስተካክሎ ወደ እውነት ሲመጣ ይደሰታሉ። (ሉቃስ 15:10ን አንብብ።) በተጨማሪም መላእክት በመንግሥቱ የስብከት ሥራ በንቃት ይሳተፋሉ። (ራእይ 14:6) ለሰዎች በቀጥታ ባይሰብኩም እንኳ አንድን አስፋፊ ስለ ይሖዋ መማር ወደሚፈልግ ሰው ሊመሩት ይችላሉ። እርግጥ ነው፣ ከየትኛውም ሁኔታ ጋር በተያያዘ ‘የመላእክት እጅ አለበት’ ብለን በእርግጠኝነት መናገር አንችልም። ምክንያቱም ይሖዋ ሰዎችን ለመርዳት ወይም አገልጋዮቹን ለመምራት ቅዱስ መንፈሱን ጨምሮ ሌሎች መንገዶችንም ሊጠቀም ይችላል። (ሥራ 16:6, 7) ያም ቢሆን፣ ከስብከቱ ሥራ ጋር በተያያዘ ይሖዋ መላእክቱን በስፋት እንደሚጠቀም እናውቃለን። ስለዚህ ምሥራቹን በምንሰብክበት ጊዜ የመላእክት ድጋፍ እንደማይለየን እርግጠኞች መሆን እንችላለን።—“ጸሎታቸው ተመልሶላቸዋል” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።b
አንድ ባልና ሚስት በጋሪ ምሥክርነት ተካፍለው ጨርሰው እየተመለሱ ነው። በመንገድ ላይ ሳሉ እህት በጭንቀት የተዋጠች የምትመስል ሴት አየች። እህታችን፣ መላእክት መንፈሳዊ እርዳታ እየፈለጉ ወዳሉ ሰዎች ሊመሩን እንደሚችሉ በመገንዘብ ሴትየዋን ለማጽናናት ተነሳሳች (አንቀጽ 8ን ተመልከት)
9. መላእክት ለሰዎች ያላቸውን ፍቅር መኮረጅ የምንችለው እንዴት ነው?
9 መላእክት ለሰዎች ያላቸውን ፍቅር መኮረጅ የምንችለው እንዴት ነው? አንድ ሰው ከውገዳ እንደተመለሰ የሚገልጽ ማስታወቂያ ስንሰማ እንደ መላእክት መደሰት እንችላለን። ለወንድማችን ጥሩ አቀባበል ለማድረግና ለእሱ ያለንን ፍቅር ለማረጋገጥ ለየት ያለ ጥረት ማድረግ እንችላለን። (ሉቃስ 15:4-7፤ 2 ቆሮ. 2:6-8) በስብከቱ ሥራ አቅማችን የፈቀደውን ሁሉ በማድረግም የመላእክትን ምሳሌ መከተል እንችላለን። (መክ. 11:6) በተጨማሪም ምሥራቹን በምንሰብክበት ጊዜ መላእክት እንደሚረዱን ሁሉ እኛም ወንድሞቻችንን እና እህቶቻችንን በአገልግሎት ረገድ ለመርዳት የሚያስችሉ መንገዶችን እንፈልጋለን። ለምሳሌ እምብዛም ተሞክሮ ከሌለው አስፋፊ ጋር ለማገልገል ቀጠሮ መያዝ እንችል ይሆን? በዕድሜ የገፉ ወይም የአቅም ገደብ ያለባቸው ወንድሞችና እህቶች በአገልግሎት እንዲካፈሉ ልንረዳቸው እንችል ይሆን?
10. ከሣራ ተሞክሮ ምን ትምህርት እናገኛለን?
10 ይሁንና ያለንበት ሁኔታ አገልግሎታችንን ቢገድብብንስ? በዚህ ወቅትም ቢሆን ከመላእክት ጋር አብረን በስብከቱ ሥራ መካፈል የምንችልባቸውን መንገዶች መፈለግ እንችላለን። በሕንድ የምትኖረውን የሣራንc ተሞክሮ እንመልከት። ሣራ ለ20 ዓመታት ገደማ በአቅኚነት ካገለገለች በኋላ ታማ የአልጋ ቁራኛ ሆነች። በዚህ ወቅት በሐዘን ተዋጠች። ሆኖም ከመንፈሳዊ ቤተሰቧ ያገኘችው ፍቅራዊ ድጋፍ እንዲሁም አዘውትራ መጽሐፍ ቅዱስን ማንበቧ ቀስ በቀስ በድጋሚ አዎንታዊ አመለካከት መያዝ እንድትችል ረዳት። እርግጥ ነው፣ ካለችበት ሁኔታ አንጻር በአገልግሎቷ ላይ ማስተካከያ ማድረግ አስፈልጓታል። ቀና ብላ ተቀምጣ ደብዳቤ መጻፍ ስለማትችል አገልግሎቷ በስልክ ምሥክርነት ብቻ የተገደበ ነበር። ስለዚህ ለተመላልሶዎቿ ደወለችላቸው፤ እነሱም የመጽሐፍ ቅዱስን መልእክት መስማት ሊፈልጉ የሚችሉ ሌሎች ሰዎችን ጠቆሟት። ውጤቱስ ምን ሆነ? በተወሰኑ ወራት ውስጥ ሣራ 70 የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶችን አገኘች! እነዚህን ሁሉ ጥናቶች ማስጠናት እንደማትችል የታወቀ ነው። በመሆኑም አንዳንዶቹን ጥናቶች በጉባኤ ውስጥ ላሉ ሌሎች አስፋፊዎች አስረከበች። ጥናት ከጀመሩት ሰዎች መካከል ብዙዎቹ በአሁኑ ወቅት በስብሰባዎቻችን ላይ ይገኛሉ። መላእክት እንደ ሣራ በስብከቱ ሥራ ለመካፈል አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ ከሚያደርጉ ወንድሞችና እህቶች ጋር አብረው መሥራት በጣም እንደሚያስደስታቸው ምንም ጥያቄ የለውም።
መላእክት ጽናት ያሳያሉ
11. ታማኝ መላእክት አስደናቂ ጽናት ያሳዩት እንዴት ነው?
11 ታማኝ መላእክት በጽናት ረገድ ግሩም ምሳሌ ናቸው። በሺዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት የፍትሕ መጓደልንና ክፋትን በጽናት ተቋቁመዋል። ሰይጣንን ጨምሮ በአንድ ወቅት አብረዋቸው ያገለግሉ የነበሩ በርካታ መንፈሳዊ ፍጥረታት በይሖዋ ላይ ሲያምፁ ተመልክተዋል። (ዘፍ. 3:1፤ 6:1, 2፤ ይሁዳ 6) መጽሐፍ ቅዱስ፣ አንድ ታማኝ መልአክ ከአንድ ኃያል ጋኔን ቀጥተኛ ተቃውሞ እንዳጋጠመው ይናገራል። (ዳን. 10:13) በተጨማሪም መላእክት በሰው ዘር ታሪክ ውስጥ አብዛኞቹ ሰዎች እውነተኛውን አምልኮ ለመከተል እንዳልመረጡ ተመልክተዋል። እነዚህ ሁሉ ነገሮች ቢኖሩም ታማኝ መላእክት ይሖዋን በደስታና በቅንዓት ማገልገላቸውን ቀጥለዋል። አምላክ በትክክለኛው ጊዜ ሁሉንም የፍትሕ መጓደል እንደሚያስወግድ ያውቃሉ።
12. ለመጽናት ምን ሊረዳን ይችላል?
12 የመላእክትን ጽናት መኮረጅ የምንችለው እንዴት ነው? እንደ መላእክት ሁሉ እኛም የፍትሕ መጓደል ሲደርስ እንመለከት ይሆናል። ሆኖም እንደ መላእክት፣ አምላክ በትክክለኛው ጊዜ ክፋትን ሁሉ እንደሚያስወግድ እንተማመናለን። ስለዚህ ታማኝ የሆኑ መላእክትን ምሳሌ በመከተል “ተስፋ ቆርጠን መልካም ሥራ መሥራታችንን [አንተውም]።” (ገላ. 6:9) ደግሞም አምላክ ለመጽናት እንደሚረዳን ቃል ገብቶልናል። (1 ቆሮ. 10:13) ይሖዋ መንፈሱን እንዲሰጠን መጸለይ እንችላለን፤ የይሖዋ መንፈስ ደግሞ ትዕግሥትንና ደስታን እንድናፈራ ይረዳናል። (ገላ. 5:22፤ ቆላ. 1:11) ይሁንና ተቃውሞ ቢያጋጥምህስ? በይሖዋ ሙሉ በሙሉ ታመን፤ እንዲሁም በፍርሃት አትሸበር። ይሖዋ ምንጊዜም ይደግፍሃል፤ እንዲሁም ያበረታሃል።—ዕብ. 13:6
መላእክት የጉባኤው ንጽሕና እንዲጠበቅ ይረዳሉ
13. መላእክት በመጨረሻዎቹ ቀናት ምን ለየት ያለ ሥራ ተሰጥቷቸዋል? (ማቴዎስ 13:47-49)
13 በመጨረሻዎቹ ቀናት ይሖዋ ለመላእክት ለየት ያለ ሥራ ሰጥቷቸዋል። (ማቴዎስ 13:47-49ን አንብብ።) የስብከቱ ሥራ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የተለያዩ ዓይነት ሰዎችን ይስባል። ከእነዚህ ሰዎች መካከል አንዳንዶቹ እርምጃ ወስደው እውነተኛ ክርስቲያኖች ይሆናሉ፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲህ አያደርጉም። መላእክት ‘ክፉዎችን ከጻድቃን የመለየት’ ሥራ ተሰጥቷቸዋል። ይህም ሲባል የጉባኤው ንጽሕና እንዲጠበቅ የመርዳት ኃላፊነት አለባቸው ማለት ነው። ይህ ሲባል ግን በማንኛውም ምክንያት ከእኛ ጋር ያለውን ግንኙነት ያቋረጠ ሰው መመለስ አይችልም ወይም ደግሞ በጉባኤው ውስጥ ፈጽሞ ችግሮች አይከሰቱም ማለት አይደለም። ያም ቢሆን መላእክት የጉባኤዎቻችን ንጽሕና እንዲጠበቅ ለመርዳት በትጋት እየሠሩ እንዳሉ እርግጠኞች መሆን እንችላለን።
14-15. እንደ መላእክት የጉባኤው ሥነ ምግባራዊና መንፈሳዊ ንጽሕና እንደሚያሳስበን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው? (ሥዕሎቹንም ተመልከት።)
14 እንደ መላእክት የጉባኤው ንጽሕና እንደሚያሳስበን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው? የጉባኤያችን ሥነ ምግባራዊና መንፈሳዊ ንጽሕና እንዲጠበቅ የበኩላችንን አስተዋጽኦ በማበርከት ነው። ለዚህም ሲባል፣ ጥሩ ጓደኞችን በመምረጥና ከበካይ ተጽዕኖ በመራቅ ልባችንን ለመጠበቅ ጥረት እናደርጋለን። (መዝ. 101:3) የእምነት አጋሮቻችን ለይሖዋ ያላቸውን ታማኝነት እንዲጠብቁ መርዳትም እንችላለን። ለምሳሌ አንድ የእምነት አጋራችን ከባድ ኃጢአት እንደፈጸመ ብናውቅ ምን ማድረግ ይኖርብናል? ለእሱ ባለን ፍቅር በመነሳሳት ሽማግሌዎችን እንዲያነጋግር እንመክረዋለን። ይህን ሳያደርግ ከቀረ ደግሞ ጉዳዩን ለሽማግሌዎች እናሳውቃለን። በመንፈሳዊ የደከሙ የእምነት አጋሮቻችን በፍጥነት እርዳታ እንዲያገኙ እንፈልጋለን።—ያዕ. 5:14, 15
15 የሚያሳዝነው፣ ከባድ ኃጢአት የፈጸሙ አንዳንድ ሰዎች ከጉባኤው መወገድ ሊኖርባቸው ይችላል። እንዲህ ያለ ሁኔታ ካጋጠመ ከእነሱ ጋር ‘መግጠማችንን እንተዋለን።’d (1 ቆሮ. 5:9-13) ይህ ዝግጅት የጉባኤው ንጽሕና እንዲጠበቅ ይረዳል። ከዚህም ሌላ፣ ከተወገዱ ሰዎች ጋር ያለንን ግንኙነት ስናቋርጥ ለእነሱ ደግነት እያሳየን ነው ሊባል ይችላል። ቆራጥ አቋም መያዛችን ወደ ልቦናቸው እንዲመለሱ ሊያነሳሳቸው ይችላል። እንዲህ ካደረጉ ደግሞ ከይሖዋና ከመላእክቱ ጋር አብረን እንደሰታለን።—ሉቃስ 15:7
አንድ የእምነት አጋራችን ከባድ ኃጢአት እንደፈጸመ ብናውቅ ምን ማድረግ ይኖርብናል? (አንቀጽ 14ን ተመልከት)e
16. የመላእክትን ምሳሌ መከተል የምትፈልገው በየትኞቹ አቅጣጫዎች ነው?
16 በእምነት ዓይናችን መንፈሳዊውን ዓለም ማየትና ከመላእክት ጋር አብሮ መሥራት መቻል እንዴት ያለ ታላቅ መብት ነው! መላእክት ያሏቸውን ግሩም ባሕርያት ማለትም ትሕትናቸውን፣ ለሰዎች ያላቸውን ፍቅር፣ ጽናታቸውን እንዲሁም ለጉባኤው ሥነ ምግባራዊና መንፈሳዊ ንጽሕና ያላቸውን ተቆርቋሪነት ለመኮረጅ ጥረት እናድርግ። የታማኝ መላእክትን ምሳሌ ከተከተልን እኛም የይሖዋ አገልጋዮችን ያቀፈው ቤተሰብ አባላት ሆነን ለዘላለም መኖር እንችላለን።
መዝሙር 123 ለቲኦክራሲያዊ ሥርዓት በታማኝነት መገዛት
a በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ መላእክት ቢኖሩም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በስም የተጠቀሱት ሁለቱ ማለትም ሚካኤል እና ገብርኤል ብቻ ናቸው።—ዳን. 12:1፤ ሉቃስ 1:19
b ተጨማሪ ተሞክሮዎችን ለማግኘት የመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ጽሑፎች ማውጫ (እንግሊዝኛ) ላይ “መላእክት” በሚለው ርዕስ ሥር ያለውን “የመላእክት አመራር (ምሳሌዎች)” የሚለውን ንዑስ ርዕስ ተመልከት።
c ስሟ ተቀይሯል።
d በ2024 የበላይ አካሉ ሪፖርት ቁጥር 2 ላይ እንደተገለጸው አንድ የተወገደ ሰው በጉባኤ ስብሰባ ላይ ከተገኘ አስፋፊዎች በመጽሐፍ ቅዱስ የሠለጠነ ሕሊናቸውን በመጠቀም ለእሱ አጠር ያለ ሰላምታ ለመስጠት ሊወስኑ ይችላሉ።
e የሥዕሉ መግለጫ፦ አንዲት እህት፣ ጓደኛዋ ሽማግሌዎችን እንድታነጋግር ታበረታታታለች። የተወሰነ ጊዜ ካለፈ በኋላም ጓደኛዋ ይህን ሳታደርግ በመቅረቷ እህት ጉዳዩን ለሽማግሌዎች ትናገራለች።