የአንባቢያን ጥያቄዎች
ይሖዋ በቅርቡ በብሔራት ልብ ውስጥ የሚያኖረው “ሐሳብ” ምንድን ነው?
ራእይ 17:16, 17 ታላቁ መከራ የሚጀምርበትን ጊዜ አስመልክቶ ሲናገር እንዲህ ይላል፦ “ያየሃቸው አሥሩ ቀንዶችና አውሬውም አመንዝራዋን ይጠሏታል፤ ከዚያም ይበዘብዟታል፤ ራቁቷንም ያስቀሯታል፤ እንዲሁም ሥጋዋን ይበላሉ፤ ሙሉ በሙሉም በእሳት ያቃጥሏታል። አምላክ . . . ሐሳቡን ዳር እንዲያደርሱ አዎ፣ መንግሥታቸውን ለአውሬው በመስጠት አንድ የሆነውን የራሳቸውን ሐሳብ እንዲፈጽሙ ይህን በልባቸው አኑሯልና።” ከዚህ ቀደም ጽሑፎቻችን፣ ይሖዋ በብሔራት ልብ ውስጥ የሚያኖረው “ሐሳብ” የሐሰት ሃይማኖትን የማጥፋት ሐሳብ እንደሆነ ይገልጹ ነበር።
ይሁንና ማስተካከያ ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል። ይሖዋ በብሔራት ልብ ውስጥ የሚያኖረው “ሐሳብ” ‘መንግሥታቸውን ለአውሬው የመስጠት’ ሐሳብ ነው። ይህ ትንቢት ፍጻሜውን የሚያገኘው እንዴት እንደሆነ ለመረዳት የሚከተሉትን ጥያቄዎች እንመልከት።
በትንቢቱ ውስጥ የተጠቀሱት ዋና ዋና ገጸ ባሕርያት እነማን ናቸው? “አመንዝራዋ” ማለትም “ታላቂቱ ባቢሎን” በዓለም ላይ ያሉ የሐሰት ሃይማኖቶችን በሙሉ ታመለክታለች። ‘ደማቁ ቀይ አውሬ’ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትን ያመለክታል። ይህ ድርጅት መጀመሪያ ላይ የተቋቋመው በ1919 ሲሆን በወቅቱ “የመንግሥታት ቃል ኪዳን ማኅበር” ተብሎ ይጠራ ነበር፤ ዓላማውም የዓለምን ሰላም ማስጠበቅ ነው። (ራእይ 17:3-5) “አሥሩ ቀንዶች” አውሬውን የሚደግፉትን መንግሥታት በሙሉ ያመለክታሉ።
በአመንዝራዋና በደማቁ ቀይ አውሬ መካከል ያለው ዝምድና ምንድን ነው? አመንዝራዋ በአውሬው ላይ “ተቀምጣ” ነበር፤ ይህም አውሬውን እንደምትደግፍና ልትቆጣጠረው እንደምትሞክር ያመለክታል።
አመንዝራዋ ምን ይደርስባታል? አውሬው እንዲሁም የሚደግፉት አሥር ቀንዶች “አመንዝራዋን ይጠሏታል።” በጥላቻ ተነሳስተው ሀብቷን ይበዘብዛሉ፤ እንዲሁም ክፋቷን ያጋልጣሉ። ከዚያም እሷን ሙሉ በሙሉ በማጥፋት ይሖዋ በእሷ ላይ ያስተላለፈው ፍርድ እንዲፈጸም ያደርጋሉ። (ራእይ 17:1፤ 18:8) ይህ የሐሰት ሃይማኖት መጨረሻ ይሆናል። ይህ ከመሆኑ በፊት ግን ይሖዋ ብሔራት በሰው ዘር ታሪክ ውስጥ ሆኖ የማያውቅ ነገር እንዲያደርጉ ያነሳሳቸዋል።
ይሖዋ ብሔራት ምን እንዲያደርጉ ያነሳሳቸዋል? በአሥሩ ቀንዶች ልብ ውስጥ “ሐሳቡን” ይኸውም ‘ኃይላቸውንና ሥልጣናቸውን ለደማቁ ቀይ አውሬ’ ማለትም ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የመስጠት ሐሳብ ያኖራል። (ራእይ 17:13) ይህ ምን ማለት እንደሆነ አስበው። የዓለም መንግሥታት ኃይላቸውንና ሥልጣናቸውን ለአውሬው የሚሰጡት በራሳቸው ተነሳስተው አይደለም። ትንቢቱ እንደሚያሳየው ይህን እንዲያደርጉ የሚያነሳሳቸው አምላክ ራሱ ነው። (ምሳሌ 21:1፤ ከኢሳይያስ 44:28 ጋር አወዳድር።) ይህ ቀስ በቀስ የሚደረግ የሥልጣን ሽግግር አይደለም። ከዚህ ይልቅ ድንገተኛና አፋጣኝ ለውጥ ይሆናል። ከዚያም በአዲስ መልክ ሥልጣን ያገኘው አውሬ የሐሰት ሃይማኖት ድርጅቶችን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በማጥፋት የይሖዋን ፍርድ ያስፈጽማል።
ታዲያ ወደፊት ምን እንደሚሆን መጠበቅ እንችላለን? ብሔራት ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሚሰጡትን ድጋፍ ቀስ በቀስ እየጨመሩ እንደመጡ የሚገልጹ የዜና ዘገባዎችን እንደምንሰማ መጠበቅ አይኖርብንም። ታዲያ ምን መጠበቅ እንችላለን? በድንገት ይሖዋ ብሔራት ሥልጣናቸውን ለአውሬው እንዲሰጡ ያደርጋቸዋል። ይህ በሚሆንበት ጊዜ ታላቁ መከራ ሊጀምር እንደሆነ እናውቃለን። እስከዚያው ግን “ነቅተን እንኑር እንዲሁም የማስተዋል ስሜታችንን እንጠብቅ”፤ ምክንያቱም በቅርቡ ድንገተኛ ለውጥ ይከሰታል!—1 ተሰ. 5:6