ረቡዕ፣ መስከረም 3
ዮሴፍ . . . የይሖዋ መልአክ ባዘዘው . . . መሠረት ሚስቱን ወደ ቤቱ ወሰዳት።—ማቴ. 1:24
ዮሴፍ የይሖዋን መመሪያ ለመከተል ፈቃደኛ ነበር፤ ይህም ጥሩ ባል እንዲሆን ረድቶታል። አምላክ ቢያንስ ሦስት ጊዜ ለዮሴፍ ቤተሰቡን የሚነካ መመሪያ ሰጥቶታል። ትልቅ ለውጥ ማድረግ ቢጠይቅበትም እንኳ በሦስቱም ጊዜያት የይሖዋን መመሪያ ወዲያውኑ ታዟል። (ማቴ. 1:20፤ 2:13-15, 19-21) ዮሴፍ የአምላክን መመሪያ በመከተል ማርያምን ከጉዳት ጠብቋታል፣ ደግፏታል እንዲሁም የሚያስፈልጋትን ነገር አሟልቶላታል። ዮሴፍ ያደረገው ነገር ማርያም ለእሱ ያላትን ፍቅርና አክብሮት ምንኛ አጠናክሮት ይሆን! ባሎች፣ ቤተሰቦቻችሁን ከምትንከባከቡበት መንገድ ጋር በተያያዘ የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያ በመፈለግ የዮሴፍን ምሳሌ መከተል ትችላላችሁ። ለውጥ ማድረግ ቢጠይቅባችሁም እንኳ የመጽሐፍ ቅዱስን ምክር የምትከተሉ ከሆነ ለሚስቶቻችሁ ያላችሁን ፍቅር ታሳያላችሁ፤ ትዳራችሁንም ታጠናክራላችሁ። በትዳር ዓለም ከ20 ዓመት በላይ ያሳለፈች በቫኑዋቱ የምትኖር እህት እንዲህ ብላለች፦ “ባለቤቴ የይሖዋን መመሪያ ለማግኘት ጥረት ሲያደርግና መመሪያውን በሥራ ላይ ሲያውል ለእሱ ያለኝ አክብሮት ይጨምራል። እተማመንበታለሁ፤ እንዲሁም ጥሩ ውሳኔ እንደሚያደርግ እርግጠኛ ነኝ።” w23.05 21 አን. 5
ሐሙስ፣ መስከረም 4
በዚያም አውራ ጎዳና ይኖራል፤ ደግሞም “የቅድስና ጎዳና” ተብሎ ይጠራል።—ኢሳ. 35:8
ከባቢሎን ወደ አገራቸው የተመለሱት አይሁዳውያን ለአምላካቸው “ቅዱስ ሕዝብ” መሆን ነበረባቸው። (ዘዳ. 7:6) ይህ ሲባል ግን፣ ይሖዋን ለማስደሰት ምንም ዓይነት ማስተካከያ ማድረግ አይጠበቅባቸውም ማለት አይደለም። በባቢሎን የተወለዱት አብዛኞቹ አይሁዳውያን ከባቢሎናውያን አስተሳሰብና መሥፈርቶች ጋር ተላምደው ሊሆን ይችላል። የመጀመሪያዎቹ አይሁዳውያን ወደ እስራኤል ከተመለሱ ከአሥርተ ዓመታት በኋላ ገዢው ነህምያ፣ እስራኤል ውስጥ የተወለዱ አንዳንድ ልጆች የአይሁዳውያንን ቋንቋ እንኳ እንደማይችሉ ሲገነዘብ በጣም ደንግጦ ነበር። (ዘዳ. 6:6, 7፤ ነህ. 13:23, 24) የአምላክ ቃል በዋነኝነት የተጻፈው በዕብራይስጥ ከመሆኑ አንጻር እነዚህ ልጆች ዕብራይስጥ ሳይችሉ ለይሖዋ ፍቅር ማዳበርና እሱን ማምለክ የሚችሉት እንዴት ነው? (ዕዝራ 10:3, 44) ስለዚህ እነዚህ አይሁዳውያን ትልቅ ለውጥ ማድረግ ነበረባቸው። ይሁንና ከባቢሎን ይልቅ ንጹሑ አምልኮ ቀስ በቀስ መልሶ እየተቋቋመ ባለበት በእስራኤል እንዲህ ያለውን ለውጥ ማድረግ ቀላል ነው።—ነህ. 8:8, 9፤ w23.05 15 አን. 6-7
ዓርብ፣ መስከረም 5
ይሖዋ ሊወድቁ የተቃረቡትን ሁሉ ይደግፋል፤ ያጎነበሱትንም ሁሉ ቀና ያደርጋል።—መዝ. 145:14
የሚያሳዝነው፣ ምንም ያህል ተነሳሽነትም ሆነ ራስን የመግዛት ችሎታ ቢኖረን እንቅፋት ሊያጋጥመን ይችላል። ለምሳሌ “ያልተጠበቁ ክስተቶች” ግባችን ላይ ለመሥራት የመደብነውን ጊዜ ሊሻሙብን ይችላሉ። (መክ. 9:11) ተስፋ የሚያስቆርጥና ጉልበታችንን የሚያዳክም ፈተና ሊያጋጥመን ይችላል። (ምሳሌ 24:10) ፍጹም ያልሆነው ሥጋችን ከግባችን ጋር የሚቃረን ድርጊት እንድንፈጽም ሊያደርገን ይችላል። (ሮም 7:23) ወይም ደግሞ ሊደክመን ይችላል። (ማቴ. 26:43) ታዲያ የሚያጋጥመንን እንቅፋት ወይም ያልተጠበቀ ሁኔታ ለመወጣት ምን ይረዳናል? እንቅፋት አጋጥሞሃል ማለት ግብህ ላይ መድረስ አትችልም ማለት እንዳልሆነ አስታውስ። መጽሐፍ ቅዱስ አስቸጋሪ ሁኔታዎች በተደጋጋሚ ሊያጋጥሙን እንደሚችሉ ይናገራል። ያም ቢሆን መልሰን መነሳት እንደምንችል በግልጽ ይናገራል። በእርግጥም፣ እንቅፋት ቢያጋጥምህም እንኳ ግብህ ላይ መሥራትህን መቀጠልህ ይሖዋን ማስደሰት እንደምትፈልግ ያሳያል። ይሖዋ ግብህ ላይ ለመድረስ ጥረት ማድረግህን እንደቀጠልክ ሲመለከት ምንኛ ይደሰት ይሆን! w23.05 30 አን. 14-15