የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • bt ምዕ. 22 ገጽ 173-179
  • “የይሖዋ ፈቃድ ይሁን”

በዚህ ክፍል ውስጥ ምንም ቪዲዮ አይገኝም።

ይቅርታ፣ ቪዲዮውን ማጫወት አልተቻለም።

  • “የይሖዋ ፈቃድ ይሁን”
  • ‘ስለ አምላክ መንግሥት በሚገባ መመሥከር’
  • ንዑስ ርዕሶች
  • ተመሳሳይ ሐሳብ ያለው ርዕስ
  • ‘የቆጵሮስን ደሴት’ አልፈው ሄዱ (የሐዋርያት ሥራ 21:1-3)
  • ‘ደቀ መዛሙርቱን ፈልገን አገኘናቸው’ (የሐዋርያት ሥራ 21:4-9)
  • “ለመሞትም እንኳ ዝግጁ ነኝ” (የሐዋርያት ሥራ 21:10-14)
  • “ወንድሞች በደስታ ተቀበሉን” (የሐዋርያት ሥራ 21:15-17)
  • አትፍራ፣ ይሖዋ ረዳትህ ነው
    የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ (የጥናት እትም)—2020
  • ፊልጶስ ቀናተኛ ወንጌላዊ
    የይሖዋን መንግሥት የሚያስታውቅ መጠበቂያ ግንብ—1999
  • ‘ከሰው ሁሉ ደም ንጹሕ ነኝ’
    ‘ስለ አምላክ መንግሥት በሚገባ መመሥከር’
  • “በሚገባ . . . መመሥከር”
    ‘ስለ አምላክ መንግሥት በሚገባ መመሥከር’
ለተጨማሪ መረጃ
‘ስለ አምላክ መንግሥት በሚገባ መመሥከር’
bt ምዕ. 22 ገጽ 173-179

ምዕራፍ 22

“የይሖዋ ፈቃድ ይሁን”

ጳውሎስ የአምላክን ፈቃድ ለመፈጸም ቆርጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ

በሐዋርያት ሥራ 21:1-17 ላይ የተመሠረተ

1-4. ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም የሚጓዘው ለምንድን ነው? እዚያስ ምን ይጠብቀዋል?

ጳውሎስና ሉቃስ ከሚሊጢን በሚነሳው መርከብ ላይ ቆመዋል፤ ስንብቱ በጣም ከባድ ነበር። ከሚወዷቸው የኤፌሶን ሽማግሌዎች ጋር የተለያዩት በግድ ነው! አሁን ሁለቱ ሚስዮናውያን ጉዞ ሊጀምሩ ነው። ለጉዞ የሚያስፈልጓቸውን በርካታ ነገሮች ሸክፈዋል። ከዚህ በተጨማሪ በይሁዳ ላሉ ችግረኛ ክርስቲያኖች የተሰባሰበውን ገንዘብ ይዘዋል፤ ይህን ስጦታ በማስረከብ ኃላፊነታቸውን ለመወጣት ቸኩለዋል።

2 ነፋሱ የመርከቡን ሸራዎች ወጠራቸው፤ መርከቡም በጫጫታ የተሞላውን ወደብ ተሰናብቶ መንቀሳቀስ ጀመረ። እነዚህ ሁለት ሰዎችና ሰባቱ የጉዞ ጓደኞቻቸው፣ ዓይናቸው ከባሕሩ ዳርቻ አልተነቀለም፤ በሐዘን የተዋጡት ወንድሞቻቸው አሁንም እዚያው ናቸው። (ሥራ 20:4, 14, 15) መርከቡ ርቆ ወዳጆቻቸው ከዓይናቸው እስኪሰወሩ ድረስ መንገደኞቹ እጃቸውን ማውለብለባቸውን አላቆሙም።

3 ጳውሎስ ለሦስት ዓመት ያህል በኤፌሶን ካሉ ሽማግሌዎች ጋር በቅርብ ሲሠራ ቆይቷል። አሁን ግን የመንፈስ ቅዱስን አመራር በመከተል ወደ ኢየሩሳሌም እየተጓዘ ነው። በዚያ ምን እንደሚጠብቀው በተወሰነ መጠን ያውቃል። ቀደም ሲል እነዚህን ሽማግሌዎች እንዲህ ብሏቸዋል፦ “እዚያ ምን እንደሚደርስብኝ ባላውቅም መንፈስ ወደ ኢየሩሳሌም እንድሄድ ግድ እያለኝ ነው፤ እርግጥ ነው፣ እስራትና መከራ እንደሚጠብቀኝ መንፈስ ቅዱስ በደረስኩበት ከተማ ሁሉ በተደጋጋሚ ያሳስበኛል።” (ሥራ 20:22, 23) ጳውሎስ አደጋ ቢደቀንበትም ‘መንፈስ ግድ ብሎታል’፤ ሐዋርያው ወደ ኢየሩሳሌም እንዲሄድ መንፈስ የሰጠውን መመሪያ ለመከተል የውዴታ ግዴታ ተሰምቶታል። ጳውሎስ መከራ እንዲደርስበት ባይፈልግም በሕይወቱ ውስጥ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ጉዳይ የአምላክን ፈቃድ መፈጸም ነው።

4 አንተስ እንደዚህ ይሰማሃል? ራሳችንን ለይሖዋ ስንወስን፣ በሕይወታችን ውስጥ ከምንም ነገር በላይ የእሱን ፈቃድ ለማስቀደም ቃል ገብተናል። ሐዋርያው ጳውሎስ የተወውን የታማኝነት ምሳሌ በመመርመር የምናገኘው ትምህርት አለ።

‘የቆጵሮስን ደሴት’ አልፈው ሄዱ (የሐዋርያት ሥራ 21:1-3)

5. ጳውሎስና የጉዞ ጓደኞቹ ወደ ጢሮስ የተጓዙት እንዴት ነው?

5 ጳውሎስና ጓደኞቹ የተሳፈሩበት መርከብ በዚያው ቀን ቆስ ደረሰ፤ ‘የተጓዘው በቀጥታ’ ነው። ተስማሚ ነፋስ ስለነበረ በዚያ እየተነዱ በፍጥነት መጓዝ ችለው ነበር። (ሥራ 21:1) መርከቡ ቆስ ላይ መልሕቁን ጥሎ ያደረ ይመስላል፤ በማግስቱ ወደ ሮድስ ከዚያም ወደ ጳጥራ ጉዞውን ቀጠለ። በትንሿ እስያ ደቡባዊ ዳርቻ ላይ ወደምትገኘው ጳጥራ ሲደርሱ ወንድሞች በአንድ ትልቅ የዕቃ ማጓጓዣ መርከብ ተሳፍረው በፊንቄ ወደምትገኘው ጢሮስ አመሩ። በጉዟቸው ላይ ‘የቆጵሮስን ደሴት በስተ ግራ ትተው’ አለፉ። (ሥራ 21:3) የሐዋርያት ሥራን የጻፈው ሉቃስ ይህን ጉዳይ ለይቶ የጠቀሰው ለምንድን ነው?

6. (ሀ) ጳውሎስ ቆጵሮስን ማየቱ ሊያበረታታው የሚችለው ለምንድን ነው? (ለ) ይሖዋ ምን ያህል እንደባረከህና እንደረዳህ ማሰብህ ምን መደምደሚያ ላይ እንድትደርስ ያደርግሃል?

6 ምናልባት ጳውሎስ ደሴቷን እያሳያቸው በዚያ ያጋጠሙትን ነገሮች ነግሯቸው ሊሆን ይችላል። ከዘጠኝ ዓመት በፊት በመጀመሪያ ሚስዮናዊ ጉዞው ወቅት ከበርናባስና ከዮሐንስ ማርቆስ ጋር ወደዚህች ደሴት ሄዶ ነበር፤ በዚያ ሲያገለግሉ ኤልማስ የተባለ ጠንቋይ የስብከቱን ሥራ ለመቃወም ሞክሮ ነበር። (ሥራ 13:4-12) ጳውሎስ ደሴቲቱን ሲያይ በዚያ ያሳለፈው ትዝታ ወደ አእምሮው መጥቶ ይሆናል፤ ያን ጊዜ መለስ ብሎ ማሰቡ ሳያበረታታው አይቀርም፤ ከፊቱ ለሚጠብቀው ነገርም አጠናክሮት ሊሆን ይችላል። እኛም አምላክ ምን ያህል እንደባረከንና ፈተናዎችን በጽናት እንድንወጣ እንደረዳን መለስ ብለን ማሰባችን ይጠቅመናል። እንዲህ ማድረጋችን የዳዊት ዓይነት ስሜት እንዲያድርብን ያደርጋል፤ ዳዊት “የጻድቅ ሰው መከራ ብዙ ነው፤ ይሖዋ ግን ከመከራው ሁሉ ይታደገዋል” በማለት ጽፏል።—መዝ. 34:19

‘ደቀ መዛሙርቱን ፈልገን አገኘናቸው’ (የሐዋርያት ሥራ 21:4-9)

7. መንገደኞቹ ጢሮስ ሲደርሱ ምን አደረጉ?

7 ጳውሎስ ከክርስቲያን ባልንጀሮቹ ጋር ጊዜ ማሳለፍ ያለውን ጠቀሜታ ያውቃል፤ ስለዚህ በእምነት ከሚዛመዱት ሰዎች ጋር ለመገናኘት ጓጉቶ ነበር። ጢሮስ በደረሱ ጊዜ ‘ደቀ መዛሙርቱን ፈልገው እንዳገኟቸው’ ሉቃስ ጽፏል። (ሥራ 21:4) እነዚህ መንገደኞች በጢሮስ ክርስቲያን ባልንጀሮቻቸው እንዳሉ ስለሚያውቁ ፈልገው አገኟቸው፤ ያረፉትም እነሱ ጋ ሳይሆን አይቀርም። እውነትን ማወቅ ከሚያስገኛቸው ታላላቅ በረከቶች አንዱ፣ የትም ብንሄድ በደስታ የሚቀበሉን የእምነት ባልንጀሮች ማግኘታችን ነው። አምላክን የሚወዱና እውነተኛውን አምልኮ የሚከተሉ ሰዎች በመላው ዓለም ወዳጆች አሏቸው።

8. በሐዋርያት ሥራ 21:4 ላይ ያለውን ሐሳብ እንዴት ልንረዳው ይገባል?

8 መንገደኞቹ በጢሮስ ሰባት ቀናት አሳለፉ፤ በዚያ ስለሆነው ነገር ሉቃስ የጻፈው ዘገባ ላይ ላዩን ሲታይ ግራ ሊያጋባ ይችላል፤ ሉቃስ “[በጢሮስ ያሉት ወንድሞች] በመንፈስ ተመርተው ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይሄድ ደጋግመው ነገሩት” ብሏል። (ሥራ 21:4) ይሖዋ፣ ሐሳቡን ለውጦ ይሆን? ቀድሞውንም ቢሆን ወደ ኢየሩሳሌም እንዲሄድ የመራው እሱ ነው፤ ታዲያ አሁን እንዳይሄድ መመሪያ እየሰጠው ነው? አይደለም። መንፈስ የጠቆመው ጳውሎስ በኢየሩሳሌም እንግልት እንደሚደርስበት ነው፤ ወደ ኢየሩሳሌም አትሂድ አላለውም። መንፈስ ቅዱስ ለጢሮስ ወንድሞች ያሳወቃቸው ነገር አለ፤ ከዚህ በመነሳት ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ችግር እንደሚያጋጥመው የተገነዘቡ ይመስላል። በመሆኑም ለጳውሎስ ደህንነት ስላሳሰባቸው ወደዚያ እንዳይሄድ ጎተጎቱት። ጳውሎስን ከአደጋ ለማዳን መፈለጋቸው የሚጠበቅ ነገር ነው። ጳውሎስ ግን የይሖዋን ፈቃድ ለመፈጸም ስለቆረጠ ወደ ኢየሩሳሌም መጓዙን ቀጠለ።—ሥራ 21:12

9, 10. (ሀ) ጳውሎስ በጢሮስ ያሉ ወንድሞች ያሳሰባቸውን ጉዳይ ሲገልጹ ሲሰማ የትኛው ተመሳሳይ ሁኔታ ትዝ ሳይለው አልቀረም? (ለ) በዛሬው ጊዜ በዓለም ላይ ተስፋፍቶ የሚታየው አመለካከት ምንድን ነው? ይህስ ኢየሱስ ከተናገረው ሐሳብ የሚለየው እንዴት ነው?

9 ጳውሎስ የወንድሞችን ልመና ሲሰማ፣ ኢየሱስ የገጠመውን ነገር ሳያስታውስ አይቀርም፤ ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚሄድ፣ ብዙ መከራ እንደሚደርስበትና እንደሚገደል ለደቀ መዛሙርቱ በነገራቸው ጊዜ ተመሳሳይ ተቃውሞ ገጥሞት ነበር። ጴጥሮስ በስሜታዊነት “ጌታ ሆይ፣ በራስህ ላይ እንዲህ አትጨክን፤ በምንም ዓይነት እንዲህ ያለ ነገር አይደርስብህም” ብሎት ነበር። ኢየሱስ ግን “ወደ ኋላዬ ሂድ፣ ሰይጣን! የሰውን እንጂ የአምላክን ሐሳብ ስለማታስብ እንቅፋት ሆነህብኛል” ብሎታል። (ማቴ. 16:21-23) ኢየሱስ የአምላክን ፈቃድ ለመፈጸምና ሕይወቱን መሥዋዕት አድርጎ ለመስጠት ቆርጦ ነበር። ጳውሎስም የሚሰማው እንዲሁ ነው። ልክ እንደ ሐዋርያው ጴጥሮስ ሁሉ የጢሮስ ወንድሞችም ጳውሎስን የለመኑት በአሳቢነት እንደሆነ አያጠያይቅም፤ ይሁን እንጂ የአምላክን ፈቃድ አልተገነዘቡም ነበር።

አገልግሎት ላይ ያለ አንድ ወንድም በመሰላቸት መንፈስ ሰዓቱን ሲመለከት። አብሮት የሚያገለግለው ወንድም ዞር ብሎ እያየው ነው።

የኢየሱስ ተከታይ መሆን የራስን ጥቅም የመሠዋት መንፈስ ይጠይቃል

10 በዛሬው ጊዜ ብዙዎች በራሳቸው ላይ መጨከን ወይም ምንም ዓይነት መሥዋዕት መክፈል አይፈልጉም። በጥቅሉ ሲታይ ሰዎች የሚመርጡት፣ ለራሳቸው የሚመቻቸውና ከአባላቱ ብዙ የማይጠብቅ ሃይማኖት መከተል ነው። በአንጻሩ ግን ኢየሱስ ከዚህ ፍጹም የተለየ አመለካከት እንዲኖረን አበረታቷል። ደቀ መዛሙርቱን “ሊከተለኝ የሚፈልግ ማንም ቢኖር ራሱን ይካድ፤ የራሱን የመከራ እንጨት ይሸከም፤ ያለማቋረጥም ይከተለኝ” ብሏቸዋል። (ማቴ. 16:24) ኢየሱስን መከተል ትክክለኛና የጥበብ ጎዳና ነው፤ ቀላሉ ጎዳና ነው ማለት ግን አይደለም።

11. በጢሮስ ያሉ ደቀ መዛሙርት ለጳውሎስ ያላቸውን ፍቅርና ድጋፍ የገለጹት እንዴት ነው?

11 ብዙም ሳይቆይ ጳውሎስ፣ ሉቃስና አብረዋቸው ያሉት ሌሎች ወንድሞች ጉዟቸውን የሚቀጥሉበት ጊዜ ደረሰ። ከጢሮስ ሲነሱ ስለነበረው ሁኔታ የሚገልጸው ዘገባ ስሜት የሚነካ ነው። የጢሮስ ወንድሞች ለጳውሎስ ያላቸውን ጥልቅ ፍቅርና በአገልግሎቱ እንዲጸና ለማበረታታት ያላቸውን ፍላጎት በግልጽ አሳይተዋል። በዚያ የነበሩ ወንዶች፣ ሴቶችና ልጆች ጳውሎስንና ጓደኞቹን እስከ ባሕሩ ዳርቻ ድረስ ሸኟቸው። ሁሉም አንድ ላይ ተንበርክከው ከጸለዩ በኋላ ተሰነባበቱ። ከዚያም ጳውሎስ፣ ሉቃስና አብረዋቸው የሚጓዙት ወንድሞች ሌላ መርከብ ተሳፍረው ወደ ጴጤሌማይስ ተጓዙ፤ እዚያም ከወንድሞች ጋር አንድ ቀን ዋሉ።—ሥራ 21:5-7

12, 13. (ሀ) ፊልጶስ ምን የአገልግሎት ታሪክ አስመዝግቧል? (ለ) ፊልጶስ ዛሬ ላሉ ክርስቲያን አባቶች ጥሩ ምሳሌ የሚሆነው እንዴት ነው?

12 በመቀጠል ጳውሎስና አብረውት የሚጓዙት ወንድሞች ወደ ቂሳርያ ማምራታቸውን ሉቃስ ዘግቧል። እዚያ ሲደርሱም “ወደ ወንጌላዊው ፊልጶስ ቤት [ገቡ]።”a (ሥራ 21:8) ፊልጶስን በማግኘታቸው እጅግ ተደስተው መሆን አለበት። ፊልጶስ ከ20 ዓመት ገደማ በፊት የክርስቲያን ጉባኤ ጨቅላ በነበረበት ወቅት ምግብ በማከፋፈሉ ሥራ እንዲረዳ በሐዋርያት ተሹሞ ነበር። ፊልጶስ ለብዙ ዓመታት በቅንዓት ባከናወነው የስብከት ሥራ መልካም ስም አትርፏል። ደቀ መዛሙርቱ በስደት የተነሳ ወደተለያዩ ቦታዎች ሲበታተኑ ፊልጶስ ወደ ሰማርያ ሄዶ በዚያ መስበክ እንደጀመረ አስታውስ። ከጊዜ በኋላ ደግሞ ለኢትዮጵያዊው ጃንደረባ የሰበከለት ከመሆኑም ሌላ አጥምቆታል። (ሥራ 6:2-6፤ 8:4-13, 26-38) በእርግጥም አገልግሎቱን በታማኝነት በመወጣት ረገድ ብዙ ታሪክ አስመዝግቧል!

13 ፊልጶስ ለአገልግሎት ያለው ቅንዓት አልቀዘቀዘም። መኖሪያውን በቂሳርያ ያደረገው ፊልጶስ አሁንም በስብከቱ ሥራ በትጋት እየተሳተፈ ነው፤ ሉቃስ “ወንጌላዊው” ብሎ የጠራው መሆኑ ይህን ያሳያል። በተጨማሪም ትንቢት የሚናገሩ አራት ሴቶች ልጆች አፍርቷል፤ ይህም ልጆቹ የአባታቸውን ፈለግ እንደተከተሉ ያሳያል።b (ሥራ 21:9) በመሆኑም ፊልጶስ የቤተሰቡን መንፈሳዊነት ለመገንባት ብዙ ጥረት አድርጎ መሆን አለበት። በዛሬው ጊዜ ያሉ ክርስቲያን አባቶች የፊልጶስን ምሳሌ መከተላቸው ተገቢ ነው፤ በአገልግሎት ግንባር ቀደም በመሆን ልጆቻቸው የወንጌላዊነቱን ሥራ እንዲወዱት መርዳት ይችላሉ።

14. ጳውሎስ የእምነት ባልንጀሮቹን መጎብኘቱ ምን በጎ ውጤት አስገኝቶ መሆን አለበት? ዛሬስ ምን ተመሳሳይ አጋጣሚዎች አሉ?

14 ጳውሎስ በደረሰበት ቦታ ሁሉ የእምነት ባልንጀሮቹን ለማግኘት ጥረት ያደርጋል፤ ከዚያም አብሯቸው ጊዜ ያሳልፋል። በየቦታው የሚያገኛቸው ወንድሞችም ይህን ሚስዮናዊና የጉዞ ባልደረቦቹን በእንግድነት ለመቀበል እንደሚጓጉ ግልጽ ነው። እንዲህ ያለው ጉብኝት ‘እርስ በርስ ለመበረታታት’ እንዳስቻላቸው ምንም ጥያቄ የለውም። (ሮም 1:11, 12) ዛሬም ቢሆን እንዲህ ዓይነት አጋጣሚዎች አሉ። ቤትህ ትንሽ ቢሆንም እንኳ የወረዳ የበላይ ተመልካቹንና ሚስቱን በእንግድነት መቀበልህ ብዙ ጥቅም ያስገኝልሃል።—ሮም 12:13

ቂሳርያ—የሮም ግዛት የሆነው የይሁዳ አውራጃ ዋና ከተማ

የሐዋርያት ሥራ ዘገባዎች በተከናወኑበት ወቅት፣ ቂሳርያ በሮም የሚተዳደረው የይሁዳ አውራጃ ዋና ከተማ ነበረች፤ የአገረ ገዢው መቀመጫና የሠራዊቱ ዋና መምሪያ የሚገኘውም እዚያ ነበር። ከተማዋን የገነባት ታላቁ ሄሮድስ ሲሆን ለአውግስጦስ ቄሳር መታሰቢያ እንድትሆን በእሱ ስም ሰየማት። ቂሳርያ በዘመኑ የነበሩ አረማውያን የግሪክ ከተሞች ያሏቸው ነገሮች ሁሉ ነበሯት፤ ለቄሳር አምልኮ የሚቀርብበት ቤተ መቅደስ፣ ቲያትር ቤት፣ የፈረስና የሠረገላ መወዳደሪያ ስታዲየም እንዲሁም አምፊቲያትር ነበራት። አብዛኞቹ የከተማዋ ነዋሪዎች አሕዛብ ነበሩ።

ቂሳርያ በቅጥር የተከበበች የወደብ ከተማ ነበረች። አዲስ የተገነባው ወደብ ሰቫስቶስ (በግሪክኛ አውግስጦስ ማለት ነው) ተብሎ ተሰየመ፤ ወደቡን ከኃይለኛ ማዕበል ለመጠበቅ ግዙፍ የመከላከያ ግንብ የተሠራለት ሲሆን ይህም ለመርከቦች እንቅስቃሴ አመቺ አድርጎታል። የሄሮድስ ምኞት እሱ የገነባው ወደብ፣ በምሥራቃዊ ሜድትራንያን አካባቢ እስክንድርያን የሚያስንቅ የንግድ ማዕከል እንዲሆን ነበር። በእርግጥ ቂሳርያ፣ እስክንድርያን አልበለጠችም፤ ይሁንና ታላላቅ የንግድ መስመሮች በሚገናኙበት ስትራቴጂያዊ ቦታ ላይ ስለነበረች በዓለም የታወቀች ከተማ ለመሆን በቅታለች።

ወንጌላዊው ፊልጶስ ምሥራቹን በቂሳርያ ሰብኳል፤ ቤተሰብ መሥርቶ ልጆቹን ያሳደገውም በዚህች ከተማ ሳይሆን አይቀርም። (ሥራ 8:40፤ 21:8, 9) ሮማዊው መቶ አለቃ ቆርኔሌዎስም የሚኖረውና ክርስትናን የተቀበለው እዚሁ ነበር።—ሥራ 10:1

ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ቂሳርያ በተለያዩ አጋጣሚዎች መጥቷል። ክርስትናን ከተቀበለ ብዙም ሳይቆይ ጠላቶቹ ሊገድሉት ሲያሴሩ ደቀ መዛሙርቱ ከኢየሩሳሌም 90 ኪሎ ሜትር ርቃ ወደምትገኘው ቂሳርያ በፍጥነት ወሰዱት፤ ከዚያም በመርከብ ወደ ጠርሴስ ላኩት። ጳውሎስ ሁለተኛና ሦስተኛ ሚስዮናዊ ጉዞውን አጠናቅቆ ወደ ኢየሩሳሌም ሲሄድም በቂሳርያ ወደብ በኩል አልፏል። (ሥራ 9:28-30፤ 18:21, 22፤ 21:7, 8) በተጨማሪም ቂሳርያ ባለው የሄሮድስ ቤተ መንግሥት ለሁለት ዓመት ታስሯል። በዚህ ወቅት ከፊሊክስ፣ ከፊስጦስና ከአግሪጳ ጋር ተነጋግሯል፤ በመጨረሻም በመርከብ ተሳፍሮ ወደ ሮም የተጓዘው ከዚሁ ቦታ ተነስቶ ነው።—ሥራ 23:33-35፤ 24:27 እስከ 25:4፤ 27:1

ሴቶች፣ ክርስቲያን አገልጋዮች መሆን ይችላሉ?

በመጀመሪያው መቶ ዘመን በክርስቲያን ጉባኤ ውስጥ የሴቶች ሚና ምን ነበር? ሴቶች፣ አገልጋዮች መሆን ይችላሉ?

ኢየሱስ፣ ተከታዮቹ ምሥራቹን እንዲሰብኩና ደቀ መዛሙርት እንዲያደርጉ መመሪያ ሰጥቷል። (ማቴ. 28:19, 20፤ ሥራ 1:8) የምሥራቹ አገልጋዮች እንዲሆኑ የሰጠው ይህ ተልእኮ፣ ሁሉንም ክርስቲያኖች ይኸውም በየትኛውም የዕድሜ ክልል ያሉ ወንዶችንና ሴቶችን የሚመለከት ነው። ሐዋርያው ጴጥሮስ በ33 ዓ.ም. በዋለው የጴንጤቆስጤ ዕለት ፍጻሜውን እንዳገኘ የተናገረው የኢዩኤል 2:28, 29 ትንቢት ይህን ያሳያል። ጴጥሮስ እንዲህ ብሏል፦ “አምላክ እንዲህ ይላል፦ ‘በመጨረሻው ቀን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ፤ ወንዶች ልጆቻችሁና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፤ . . . በወንዶች ባሪያዎቼና በሴቶች ባሪያዎቼ ላይ ሳይቀር ከመንፈሴ አፈሳለሁ፤ እነሱም ትንቢት ይናገራሉ።’” (ሥራ 2:17, 18) ቀደም ሲል እንዳየነው ወንጌላዊው ፊልጶስ ትንቢት የሚናገሩ አራት ሴቶች ልጆች ነበሩት።—ሥራ 21:8, 9

በጉባኤ ውስጥ ከማስተማር ጋር በተያያዘ ግን ሁኔታው ይለያል፤ ክርስቲያን የበላይ ተመልካቾችና የጉባኤ አገልጋዮች ሆነው መሾም ያለባቸው ወንዶች ብቻ እንደሆኑ የአምላክ ቃል ይናገራል። (1 ጢሞ. 3:1-13፤ ቲቶ 1:5-9) እንዲያውም ጳውሎስ “ሴት ዝም እንድትል እንጂ እንድታስተምር ወይም በወንድ ላይ ሥልጣን እንዲኖራት አልፈቅድም” በማለት ተናግሯል።—1 ጢሞ. 2:12

“ለመሞትም እንኳ ዝግጁ ነኝ” (የሐዋርያት ሥራ 21:10-14)

15, 16. አጋቦስ ያመጣው መልእክት ምንድን ነው? ወንድሞች መልእክቱን ሲሰሙ ምን ተሰማቸው?

15 ጳውሎስ ፊልጶስ ቤት እያለ፣ አጋቦስ የሚባል ሌላ የተከበረ እንግዳ መጣ። በፊልጶስ ቤት የተሰበሰቡት ሰዎች አጋቦስ ነቢይ መሆኑን ያውቃሉ፤ ደግሞም በቀላውዴዎስ ዘመን ታላቅ ረሃብ እንደሚከሰት ተንብዮ ነበር። (ሥራ 11:27, 28) ሰዎቹ አጋቦስ የመጣበት ምክንያት ጥያቄ ፈጥሮባቸው ይሆናል፤ ‘ምን መልእክት ይዞ ይሆን?’ ብለው ሳያስቡ አይቀሩም። ሁሉም በትኩረት እየተመለከቱት ሳለ የጳውሎስን ቀበቶ ወሰደ፤ እዚህ ላይ የተጠቀሰው ቀበቶ ገንዘብና ሌሎች ነገሮች ለመያዝ የሚያገለግል ወገብ ላይ የሚታሰር ረጅም መቀነት ነው። አጋቦስ በቀበቶው የራሱን እግሮችና እጆች አሰረ። ከዚያም ይህን አስደንጋጭ መልእክት ተናገረ፦ “መንፈስ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ ‘አይሁዳውያን የዚህን ቀበቶ ባለቤት በኢየሩሳሌም እንዲህ አድርገው ያስሩታል፤ ለአሕዛብም አሳልፈው ይሰጡታል።’”—ሥራ 21:11

16 ትንቢቱ፣ ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም መሄዱ የማይቀር መሆኑን ያረጋግጣል። በተጨማሪም በዚያ የሚገኙት አይሁዳውያን ‘ለአሕዛብ አሳልፈው’ እንደሚሰጡት ይጠቁማል። ይህ ትንቢት በዚያ የነበሩትን ሁሉ ረበሻቸው። ሉቃስ እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “ይህን ስንሰማ እኛም ሆንን በዚያ የነበሩት ደቀ መዛሙርት ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይወጣ እንለምነው ጀመር። በዚህ ጊዜ ጳውሎስ ‘እያለቀሳችሁ ልቤን ለምን ታባባላችሁ? እኔ ስለ ጌታ ኢየሱስ ስም በኢየሩሳሌም ለመታሰር ብቻ ሳይሆን ለመሞትም እንኳ ዝግጁ ነኝ’ ሲል መለሰ።”—ሥራ 21:12, 13

17, 18. ጳውሎስ ከአቋሙ ፍንክች እንደማይል ያሳየው እንዴት ነው? የወንድሞችስ ምላሽ ምን ነበር?

17 እስቲ ሁኔታውን በዓይነ ሕሊናህ ለመሳል ሞክር። ሉቃስን ጨምሮ ወንድሞች፣ ጳውሎስ ጉዞውን እንዳይቀጥል እየለመኑት ነው። እንዲያውም አንዳንዶቹ ያለቅሳሉ። ጳውሎስ፣ የወንድሞቹን ፍቅርና ስስት ሲያይ “ልቤን ለምን ታባባላችሁ?” አላቸው፤ አንዳንድ ትርጉሞች “ልቤን እየሰበራችሁት ነው” በማለት አስቀምጠውታል። ያም ቢሆን ጳውሎስ ከአቋሙ ፍንክች አላለም፤ በጢሮስም ሆነ እዚህ ያገኛቸው ወንድሞች ለቅሶና ልመና ልቡን እንዲከፍለው አልፈቀደም። ይልቁንም ጉዞውን መቀጠል ያለበት ለምን እንደሆነ አስረዳቸው። ድፍረቱና ቆራጥነቱ እጅግ ይደንቃል! ከእሱ በፊት ኢየሱስ እንዳደረገው ሁሉ ጳውሎስም ወደ ኢየሩሳሌም ለመሄድ ቆርጦ ተነስቷል። (ዕብ 12:2) ጳውሎስ ሰማዕት የመሆን ፍላጎት የለውም፤ ሆኖም ይህ የማይቀር ከሆነ የክርስቶስ ኢየሱስ ተከታይ ሆኖ መሞቱን እንደ ክብር ይቆጥረዋል።

18 የወንድሞች ምላሽ ምን ነበር? በአጭሩ፣ ሐሳቡን አክብረውለታል። ዘገባው እንዲህ ይላል፦ “እሱን ለማሳመን ያደረግነው ጥረት ሳይሳካ በመቅረቱ ‘እንግዲህ የይሖዋ ፈቃድ ይሁን’ ብለን ዝም አልን።” (ሥራ 21:14) ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይሄድ ለማሳመን የጣሩት ወንድሞች ሐሳባቸውን እንዲቀበል አላስገደዱትም። የጳውሎስን ሐሳብ ሰምተው እሱ ባለው ተስማሙ፤ ነገሩ ቢከብዳቸውም የይሖዋን ፈቃድ መቀበል እንዳለባቸው ተገንዝበዋል። ጳውሎስ የጀመረው ጎዳና የኋላ ኋላ ለሞት ሊዳርገው ይችላል። ወዳጆቹ ሁኔታውን ለመቀበል የሚያቀሉለት ይህን እንዳያደርግ ለማግባባት ጥረት ማድረጋቸውን ካቆሙ ነው።

19. ጳውሎስ ካጋጠመው ሁኔታ ምን ጠቃሚ ትምህርት ማግኘት እንችላለን?

19 ጳውሎስ ካጋጠመው ሁኔታ የምናገኘው ጠቃሚ ትምህርት አለ፦ አምላክን ለማገልገል ሲሉ መሥዋዕትነት የሚከፍሉ ክርስቲያኖች የያዙትን ጎዳና እንዲተዉ ለማግባባት ፈጽሞ መሞከር የለብንም። የሞትና የሕይወት ጉዳይ በሆኑ ነገሮች ብቻ ሳይሆን በሌሎች መስኮችም ይህን ሐሳብ ተግባራዊ ማድረግ እንችላለን። አንድ ምሳሌ እንውሰድ፦ ብዙ ክርስቲያን ወላጆች ልጆቻቸው ይሖዋን ለማገልገል ሩቅ ወደሆነ አካባቢ ሲሄዱ ሁኔታው እንደሚከብዳቸው የታወቀ ነው፤ ያም ቢሆን እነሱን ተስፋ ላለማስቆረጥ ይጠነቀቃሉ። በእንግሊዝ የምትኖረው ፊሊስ አንድ ልጇ ሚስዮናዊት ሆና ለማገልገል ወደ አፍሪካ ስትሄድ ምን እንደተሰማት አትረሳውም። እንዲህ ብላለች፦ “ስሜቴ እጅግ ተረብሾ ነበር። ከእኔ በጣም ርቃ እንደምትሄድ መቀበል ከበደኝ። በአንድ በኩል አዘንኩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ኩራት ተሰማኝ። ስለዚህ ጉዳይ ብዙ ጊዜ ጸለይኩ። ሆኖም ውሳኔውን ለእሷ ተውኩት፤ ሐሳቧን ለማስቀየር አልሞከርኩም። ደግሞም እኮ ያስተማርኳት የአምላክን መንግሥት እንድታስቀድም ነው! ላለፉት 30 ዓመታት በተለያዩ አገሮች አገልግላለች፤ በታማኝነት በመጽናቷም ይሖዋን በየቀኑ አመሰግነዋለሁ።” የራሳቸውን ጥቅም የሚሠዉ የእምነት ባልንጀሮቻችንን ማበረታታት በእርግጥም ልናደርገው የሚገባ ነገር ነው!

ፎቶግራፎች፦ ሚስዮናውያን ባልና ሚስት እና ወላጆቻቸው። 1. ወላጆች ለልጆቻቸው ሲደውሉ። 2. ሚስዮናውያኑ ከተመደቡበት አገር ሆነው ወላጆቻቸውን በስልክ ሲያነጋግሩ። ወላጆችም ሆኑ ልጆች በስልክ በመገናኘታቸው ተደስተዋል።

መሥዋዕትነት የሚከፍሉ የእምነት ባልንጀሮቻችንን ማበረታታት አስፈላጊ ነው

“ወንድሞች በደስታ ተቀበሉን” (የሐዋርያት ሥራ 21:15-17)

20, 21. ጳውሎስ ከወንድሞች ጋር የመሆን ፍላጎት እንደነበረው የሚያሳየው ምንድን ነው? ከእምነት ባልንጀሮቹ ጋር መሆን የፈለገውስ ለምንድን ነው?

20 አስፈላጊው ዝግጅት ከተጠናቀቀ በኋላ ጳውሎስ ጉዞውን ቀጠለ፤ አንዳንድ የቂሳርያ ወንድሞችም አብረውት ናቸው፤ እነዚህ ታማኝ ወንድሞች በዚህ መንገድ አጋርነታቸውን አሳይተዋል። ጳውሎስና የጉዞ ጓደኞቹ ወደ ኢየሩሳሌም ባደረጉት ጉዞ በደረሱበት ሁሉ ክርስቲያን ወንድሞቻቸውንና እህቶቻቸውን ለማግኘት ጥረት ያደርጉ ነበር። በጢሮስ ደቀ መዛሙርቱን አግኝተው ከእነሱ ጋር ለሰባት ቀናት ቆይተዋል። በጴጤሌማይስ እህቶችንና ወንድሞችን ሰላም ካሉ በኋላ አብረዋቸው ውለዋል። በቂሳርያ በፊልጶስ ቤት ለበርካታ ቀናት ተቀምጠዋል። ቀጥሎ ደግሞ በቂሳርያ ያሉ አንዳንድ ደቀ መዛሙርት ጳውሎስንና ጓደኞቹን እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ሸኟቸው፤ እዚያ ሲደርሱም ከቀድሞዎቹ ደቀ መዛሙርት አንዱ በሆነው በምናሶን ቤት አረፉ። ሉቃስ እንደዘገበው በኢየሩሳሌም “ወንድሞች በደስታ [ተቀበሏቸው]።”—ሥራ 21:17

21 በግልጽ ማየት እንደሚቻለው ጳውሎስ ከእምነት ባልንጀሮቹ ጋር መሆን ያስደስተው ነበር። ዛሬ ወንድሞቻችን የብርታት ምንጭ እንደሚሆኑን ሁሉ ሐዋርያው ጳውሎስም ከወንድሞቹና ከእህቶቹ ጋር ጊዜ ሲያሳልፍ ይበረታታል። ይህ ማበረታቻ፣ ጳውሎስ ሊገድሉት የሚፈልጉ ኃይለኛ ተቃዋሚዎቹን ለመጋፈጥ የሚያስችል ጥንካሬ እንደሰጠው ምንም አያጠያይቅም።

a “ቂሳርያ—የሮም ግዛት የሆነው የይሁዳ አውራጃ ዋና ከተማ” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።

b “ሴቶች፣ ክርስቲያን አገልጋዮች መሆን ይችላሉ?” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።

    አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
    ውጣ
    ግባ
    • አማርኛ
    • አጋራ
    • የግል ምርጫዎች
    • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
    • የአጠቃቀም ውል
    • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
    • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
    • JW.ORG
    • ግባ
    አጋራ