እሁድ፣ ሐምሌ 20
ሐሳቤ እንደ ሐሳባችሁ . . . አይደለም።—ኢሳ. 55:8
በጸሎት የጠየቅነውን ነገር ካላገኘን ‘ጥያቄዬ ተገቢ ነው?’ ብለን ራሳችንን ልንጠይቅ እንችላለን። ብዙውን ጊዜ፣ የሚበጀንን ነገር እንደምናውቅ ይሰማናል። ሆኖም የጠየቅናቸው ነገሮች ላይጠቅሙን ይችላሉ። የምንጸልየው ስለ አንድ ችግር ከሆነ ለዚያ ችግር እኛ ከጠየቅነው የተሻለ መፍትሔ ሊኖር ይችላል። የምንጠይቃቸው አንዳንድ ነገሮች ደግሞ ከይሖዋ ፈቃድ ጋር ላይስማሙ ይችላሉ። (1 ዮሐ. 5:14) ልጃቸው እውነት ውስጥ እንዲቆይ ይሖዋን በጸሎት የጠየቁ ወላጆችን እንደ ምሳሌ እንመልከት። ጥያቄያቸው ተገቢ ይመስላል። ይሁንና ይሖዋ ማናችንንም እንድናገለግለው አያስገድደንም። ልጆቻችንን ጨምሮ ሁላችንም እሱን ለማገልገል እንድንመርጥ ይፈልጋል። (ዘዳ. 10:12, 13፤ 30:19, 20) በመሆኑም እነዚህ ወላጆች የልጃቸውን ልብ ለመንካት እንዲረዳቸው ይሖዋን ቢጠይቁ የተሻለ ነው፤ ይህም ልጃቸው ይሖዋን እንዲወደውና የእሱ ወዳጅ እንዲሆን ሊያነሳሳው ይችላል።—ምሳሌ 22:6፤ ኤፌ. 6:4፤ w23.11 21 አን. 5፤ 23 አን. 12
ሰኞ፣ ሐምሌ 21
ሁልጊዜ እርስ በርሳችሁ ተጽናኑ።—1 ተሰ. 4:18
ሌሎችን ማጽናናት አስፈላጊ የፍቅር መግለጫ የሆነው ለምንድን ነው? አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ማመሣከሪያ እንደገለጸው፣ ጳውሎስ የተጠቀመበት “ማጽናናት” የሚለው ቃል “አንድ ሰው ከባድ ፈተና ሲያጋጥመው ከጎኑ ቆሞ እሱን ማበረታታት” የሚል ትርጉም አለው። በመሆኑም ማጽናኛ በመስጠት በጭንቀት የተዋጠ የእምነት አጋራችን ተነስቶ በሕይወት መንገድ ላይ መጓዙን እንዲቀጥል እንረዳዋለን። አንድ ወንድማችንን ወይም እህታችንን ባጽናናን ቁጥር ለእነሱ ያለንን ፍቅር እናሳያለን። (2 ቆሮ. 7:6, 7, 13) ርኅራኄ እና ማጽናኛ በጥብቅ የተቆራኙ ነገሮች ናቸው። በምን መንገድ? ሩኅሩኅ ሰው ሌሎችን ለማጽናናትና መከራቸውን ለማቅለል ይነሳሳል። ስለዚህ ርኅራኄ ካለን ሌሎችን ለማጽናናት እንነሳሳለን። ጳውሎስ የይሖዋን ርኅራኄ ከሚሰጠው ማጽናኛ ጋር ያያያዘው እንዴት እንደሆነ ልብ በል። ጳውሎስ፣ ይሖዋ “ከርኅራኄ የመነጨ ምሕረት አባትና የመጽናናት ሁሉ አምላክ” እንደሆነ ገልጿል።—2 ቆሮ. 1:3፤ w23.11 9-10 አን. 8-10
ማክሰኞ፣ ሐምሌ 22
በመከራ ውስጥ እያለንም እጅግ እንደሰት።—ሮም 5:3
ሁሉም የክርስቶስ ተከታዮች መከራ እንደሚደርስባቸው ሊጠብቁ ይገባል። የሐዋርያው ጳውሎስን ምሳሌ እንመልከት። በተሰሎንቄ ለሚኖሩ ክርስቲያኖች እንዲህ ብሏቸዋል፦ “አብረናችሁ በነበርንበት ጊዜ መከራ መቀበላችን እንደማይቀር አስቀድመን እንነግራችሁ ነበር፤ ደግሞም እንደምታውቁት ይኸው ነገር ደርሷል።” (1 ተሰ. 3:4) በቆሮንቶስ ለሚኖሩ ክርስቲያኖች ደግሞ “ወንድሞች . . . ስለደረሰብን መከራ እንድታውቁ እንፈልጋለን። . . . በሕይወት የመትረፍ ተስፋችን እንኳ ተሟጦ ነበር” ብሏቸዋል። (2 ቆሮ. 1:8፤ 11:23-27) በዛሬው ጊዜ ያሉ ክርስቲያኖችም በሆነ መልኩ መከራ እንደሚደርስባቸው ሊጠብቁ ይገባል። (2 ጢሞ. 3:12) አንተም በኢየሱስ በማመንህና እሱን በመከተልህ የተነሳ ጓደኞችህና ዘመዶችህ ስደት አድርሰውብህ ሊሆን ይችላል። በሁሉም ነገር ሐቀኛ ለመሆን ያደረግከው ውሳኔ በሥራ ቦታህ ችግር አስከትሎብሃል? (ዕብ. 13:18) ተስፋህን ለሌሎች በማካፈልህ የተነሳ የመንግሥት ባለሥልጣናት ተቃውመውሃል? ይሁንና የሚደርስብን መከራ ምንም ይሁን ምን ጳውሎስ ልንደሰት እንደሚገባ ገልጿል። w23.12 10-11 አን. 9-10