ሐሙስ፣ መስከረም 4
በዚያም አውራ ጎዳና ይኖራል፤ ደግሞም “የቅድስና ጎዳና” ተብሎ ይጠራል።—ኢሳ. 35:8
ከባቢሎን ወደ አገራቸው የተመለሱት አይሁዳውያን ለአምላካቸው “ቅዱስ ሕዝብ” መሆን ነበረባቸው። (ዘዳ. 7:6) ይህ ሲባል ግን፣ ይሖዋን ለማስደሰት ምንም ዓይነት ማስተካከያ ማድረግ አይጠበቅባቸውም ማለት አይደለም። በባቢሎን የተወለዱት አብዛኞቹ አይሁዳውያን ከባቢሎናውያን አስተሳሰብና መሥፈርቶች ጋር ተላምደው ሊሆን ይችላል። የመጀመሪያዎቹ አይሁዳውያን ወደ እስራኤል ከተመለሱ ከአሥርተ ዓመታት በኋላ ገዢው ነህምያ፣ እስራኤል ውስጥ የተወለዱ አንዳንድ ልጆች የአይሁዳውያንን ቋንቋ እንኳ እንደማይችሉ ሲገነዘብ በጣም ደንግጦ ነበር። (ዘዳ. 6:6, 7፤ ነህ. 13:23, 24) የአምላክ ቃል በዋነኝነት የተጻፈው በዕብራይስጥ ከመሆኑ አንጻር እነዚህ ልጆች ዕብራይስጥ ሳይችሉ ለይሖዋ ፍቅር ማዳበርና እሱን ማምለክ የሚችሉት እንዴት ነው? (ዕዝራ 10:3, 44) ስለዚህ እነዚህ አይሁዳውያን ትልቅ ለውጥ ማድረግ ነበረባቸው። ይሁንና ከባቢሎን ይልቅ ንጹሑ አምልኮ ቀስ በቀስ መልሶ እየተቋቋመ ባለበት በእስራኤል እንዲህ ያለውን ለውጥ ማድረግ ቀላል ነው።—ነህ. 8:8, 9፤ w23.05 15 አን. 6-7
ዓርብ፣ መስከረም 5
ይሖዋ ሊወድቁ የተቃረቡትን ሁሉ ይደግፋል፤ ያጎነበሱትንም ሁሉ ቀና ያደርጋል።—መዝ. 145:14
የሚያሳዝነው፣ ምንም ያህል ተነሳሽነትም ሆነ ራስን የመግዛት ችሎታ ቢኖረን እንቅፋት ሊያጋጥመን ይችላል። ለምሳሌ “ያልተጠበቁ ክስተቶች” ግባችን ላይ ለመሥራት የመደብነውን ጊዜ ሊሻሙብን ይችላሉ። (መክ. 9:11) ተስፋ የሚያስቆርጥና ጉልበታችንን የሚያዳክም ፈተና ሊያጋጥመን ይችላል። (ምሳሌ 24:10) ፍጹም ያልሆነው ሥጋችን ከግባችን ጋር የሚቃረን ድርጊት እንድንፈጽም ሊያደርገን ይችላል። (ሮም 7:23) ወይም ደግሞ ሊደክመን ይችላል። (ማቴ. 26:43) ታዲያ የሚያጋጥመንን እንቅፋት ወይም ያልተጠበቀ ሁኔታ ለመወጣት ምን ይረዳናል? እንቅፋት አጋጥሞሃል ማለት ግብህ ላይ መድረስ አትችልም ማለት እንዳልሆነ አስታውስ። መጽሐፍ ቅዱስ አስቸጋሪ ሁኔታዎች በተደጋጋሚ ሊያጋጥሙን እንደሚችሉ ይናገራል። ያም ቢሆን መልሰን መነሳት እንደምንችል በግልጽ ይናገራል። በእርግጥም፣ እንቅፋት ቢያጋጥምህም እንኳ ግብህ ላይ መሥራትህን መቀጠልህ ይሖዋን ማስደሰት እንደምትፈልግ ያሳያል። ይሖዋ ግብህ ላይ ለመድረስ ጥረት ማድረግህን እንደቀጠልክ ሲመለከት ምንኛ ይደሰት ይሆን! w23.05 30 አን. 14-15
ቅዳሜ፣ መስከረም 6
ለመንጋው ምሳሌ [ሁኑ]።—1 ጴጥ. 5:3
ወጣት ወንድሞች በአቅኚነት ማገልገላቸው ከተለያዩ ዓይነት ሰዎች ጋር ተባብሮ መሥራት የሚቻለው እንዴት እንደሆነ ለመማር ይረዳቸዋል። በተጨማሪም ምክንያታዊ የሆነ በጀት ማውጣትና በበጀታቸው መመራት የሚችሉበትን መንገድ ያስተምራቸዋል። (ፊልጵ. 4:11-13) በረዳት አቅኚነት ማገልገላችሁ የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ለመጀመር ይረዳችኋል። ረዳት አቅኚ መሆናችሁ የዘወትር አቅኚነት ለመጀመር ዝግጁ እንድትሆኑ ይረዳችኋል። አቅኚነት ወደ ሌሎች የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ዘርፎች ለመግባት መንገድ ሊከፍትላችሁ ይችላል፤ ይህም የግንባታ አገልጋይ ወይም ቤቴላዊ መሆንን ይጨምራል። ክርስቲያን ወንዶች የጉባኤ ሽማግሌዎች ሆነው ወንድሞቻቸውንና እህቶቻቸውን የማገልገል ግብ ሊኖራቸው ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ፣ እዚህ ግብ ላይ ለመድረስ የሚጣጣሩ ወንድሞች ‘መልካም ሥራን እንደሚመኙ’ ይናገራል። (1 ጢሞ. 3:1) በመጀመሪያ አንድ ወንድም ብቃቱን አሟልቶ የጉባኤ አገልጋይ መሆን አለበት። የጉባኤ አገልጋዮች በተለያዩ መንገዶች የጉባኤ ሽማግሌዎችን ይረዳሉ። ሽማግሌዎችም ሆኑ የጉባኤ አገልጋዮች ወንድሞቻቸውንና እህቶቻቸውን በትሕትና ያገለግላሉ፤ እንዲሁም በአገልግሎት በቅንዓት ይካፈላሉ። w23.12 28 አን. 14-16