ዓርብ፣ መስከረም 5
ይሖዋ ሊወድቁ የተቃረቡትን ሁሉ ይደግፋል፤ ያጎነበሱትንም ሁሉ ቀና ያደርጋል።—መዝ. 145:14
የሚያሳዝነው፣ ምንም ያህል ተነሳሽነትም ሆነ ራስን የመግዛት ችሎታ ቢኖረን እንቅፋት ሊያጋጥመን ይችላል። ለምሳሌ “ያልተጠበቁ ክስተቶች” ግባችን ላይ ለመሥራት የመደብነውን ጊዜ ሊሻሙብን ይችላሉ። (መክ. 9:11) ተስፋ የሚያስቆርጥና ጉልበታችንን የሚያዳክም ፈተና ሊያጋጥመን ይችላል። (ምሳሌ 24:10) ፍጹም ያልሆነው ሥጋችን ከግባችን ጋር የሚቃረን ድርጊት እንድንፈጽም ሊያደርገን ይችላል። (ሮም 7:23) ወይም ደግሞ ሊደክመን ይችላል። (ማቴ. 26:43) ታዲያ የሚያጋጥመንን እንቅፋት ወይም ያልተጠበቀ ሁኔታ ለመወጣት ምን ይረዳናል? እንቅፋት አጋጥሞሃል ማለት ግብህ ላይ መድረስ አትችልም ማለት እንዳልሆነ አስታውስ። መጽሐፍ ቅዱስ አስቸጋሪ ሁኔታዎች በተደጋጋሚ ሊያጋጥሙን እንደሚችሉ ይናገራል። ያም ቢሆን መልሰን መነሳት እንደምንችል በግልጽ ይናገራል። በእርግጥም፣ እንቅፋት ቢያጋጥምህም እንኳ ግብህ ላይ መሥራትህን መቀጠልህ ይሖዋን ማስደሰት እንደምትፈልግ ያሳያል። ይሖዋ ግብህ ላይ ለመድረስ ጥረት ማድረግህን እንደቀጠልክ ሲመለከት ምንኛ ይደሰት ይሆን! w23.05 30 አን. 14-15
ቅዳሜ፣ መስከረም 6
ለመንጋው ምሳሌ [ሁኑ]።—1 ጴጥ. 5:3
ወጣት ወንድሞች በአቅኚነት ማገልገላቸው ከተለያዩ ዓይነት ሰዎች ጋር ተባብሮ መሥራት የሚቻለው እንዴት እንደሆነ ለመማር ይረዳቸዋል። በተጨማሪም ምክንያታዊ የሆነ በጀት ማውጣትና በበጀታቸው መመራት የሚችሉበትን መንገድ ያስተምራቸዋል። (ፊልጵ. 4:11-13) በረዳት አቅኚነት ማገልገላችሁ የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ለመጀመር ይረዳችኋል። ረዳት አቅኚ መሆናችሁ የዘወትር አቅኚነት ለመጀመር ዝግጁ እንድትሆኑ ይረዳችኋል። አቅኚነት ወደ ሌሎች የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ዘርፎች ለመግባት መንገድ ሊከፍትላችሁ ይችላል፤ ይህም የግንባታ አገልጋይ ወይም ቤቴላዊ መሆንን ይጨምራል። ክርስቲያን ወንዶች የጉባኤ ሽማግሌዎች ሆነው ወንድሞቻቸውንና እህቶቻቸውን የማገልገል ግብ ሊኖራቸው ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ፣ እዚህ ግብ ላይ ለመድረስ የሚጣጣሩ ወንድሞች ‘መልካም ሥራን እንደሚመኙ’ ይናገራል። (1 ጢሞ. 3:1) በመጀመሪያ አንድ ወንድም ብቃቱን አሟልቶ የጉባኤ አገልጋይ መሆን አለበት። የጉባኤ አገልጋዮች በተለያዩ መንገዶች የጉባኤ ሽማግሌዎችን ይረዳሉ። ሽማግሌዎችም ሆኑ የጉባኤ አገልጋዮች ወንድሞቻቸውንና እህቶቻቸውን በትሕትና ያገለግላሉ፤ እንዲሁም በአገልግሎት በቅንዓት ይካፈላሉ። w23.12 28 አን. 14-16
እሁድ፣ መስከረም 7
ገና ልጅ ሳለ የአባቱን የዳዊትን አምላክ መፈለግ ጀመረ።—2 ዜና 34:3
ንጉሥ ኢዮስያስ ይሖዋን መፈለግ የጀመረው ገና በአሥራዎቹ ዕድሜ እያለ ነው። ስለ ይሖዋ መማርና የእሱን ፈቃድ ማድረግ ይፈልግ ነበር። ያም ቢሆን፣ ለዚህ ወጣት ንጉሥ ሕይወት ቀላል አልነበረም። የሐሰት አምልኮ በተስፋፋበት ዘመን ከንጹሑ አምልኮ ጎን መቆም ነበረበት። ያደረገውም ይህንኑ ነው! ኢዮስያስ ገና 20 ዓመት ሳይሞላው በፊት የሐሰት አምልኮን ከይሁዳ ማስወገድ ጀመረ። (2 ዜና 34:1, 2) ገና ልጅ ብትሆንም እንኳ ይሖዋን በመፈለግና ስለ ባሕርያቱ በመማር የኢዮስያስን ምሳሌ መከተል ትችላለህ። እንዲህ ማድረግህ ራስህን ለእሱ ለመወሰን ያነሳሳሃል። ራስህን ለይሖዋ መወሰንህ በዕለት ተዕለት ሕይወትህ ላይ ምን ተጽዕኖ ያሳድራል? በ14 ዓመቱ የተጠመቀው ሉክ እንዲህ ብሏል፦ “ከአሁን ጀምሮ በሕይወቴ ውስጥ የይሖዋን አገልግሎት አስቀድማለሁ፤ እሱን ለማስደሰትም ጥረት አደርጋለሁ።” (ማር. 12:30) አንተም እንዲህ ማድረግ የምትፈልግ ከሆነ ትልቅ በረከት ታገኛለህ! w23.09 11 አን. 12-13