ቅዳሜ፣ መስከረም 6
ለመንጋው ምሳሌ [ሁኑ]።—1 ጴጥ. 5:3
ወጣት ወንድሞች በአቅኚነት ማገልገላቸው ከተለያዩ ዓይነት ሰዎች ጋር ተባብሮ መሥራት የሚቻለው እንዴት እንደሆነ ለመማር ይረዳቸዋል። በተጨማሪም ምክንያታዊ የሆነ በጀት ማውጣትና በበጀታቸው መመራት የሚችሉበትን መንገድ ያስተምራቸዋል። (ፊልጵ. 4:11-13) በረዳት አቅኚነት ማገልገላችሁ የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ለመጀመር ይረዳችኋል። ረዳት አቅኚ መሆናችሁ የዘወትር አቅኚነት ለመጀመር ዝግጁ እንድትሆኑ ይረዳችኋል። አቅኚነት ወደ ሌሎች የሙሉ ጊዜ አገልግሎት ዘርፎች ለመግባት መንገድ ሊከፍትላችሁ ይችላል፤ ይህም የግንባታ አገልጋይ ወይም ቤቴላዊ መሆንን ይጨምራል። ክርስቲያን ወንዶች የጉባኤ ሽማግሌዎች ሆነው ወንድሞቻቸውንና እህቶቻቸውን የማገልገል ግብ ሊኖራቸው ይገባል። መጽሐፍ ቅዱስ፣ እዚህ ግብ ላይ ለመድረስ የሚጣጣሩ ወንድሞች ‘መልካም ሥራን እንደሚመኙ’ ይናገራል። (1 ጢሞ. 3:1) በመጀመሪያ አንድ ወንድም ብቃቱን አሟልቶ የጉባኤ አገልጋይ መሆን አለበት። የጉባኤ አገልጋዮች በተለያዩ መንገዶች የጉባኤ ሽማግሌዎችን ይረዳሉ። ሽማግሌዎችም ሆኑ የጉባኤ አገልጋዮች ወንድሞቻቸውንና እህቶቻቸውን በትሕትና ያገለግላሉ፤ እንዲሁም በአገልግሎት በቅንዓት ይካፈላሉ። w23.12 28 አን. 14-16
እሁድ፣ መስከረም 7
ገና ልጅ ሳለ የአባቱን የዳዊትን አምላክ መፈለግ ጀመረ።—2 ዜና 34:3
ንጉሥ ኢዮስያስ ይሖዋን መፈለግ የጀመረው ገና በአሥራዎቹ ዕድሜ እያለ ነው። ስለ ይሖዋ መማርና የእሱን ፈቃድ ማድረግ ይፈልግ ነበር። ያም ቢሆን፣ ለዚህ ወጣት ንጉሥ ሕይወት ቀላል አልነበረም። የሐሰት አምልኮ በተስፋፋበት ዘመን ከንጹሑ አምልኮ ጎን መቆም ነበረበት። ያደረገውም ይህንኑ ነው! ኢዮስያስ ገና 20 ዓመት ሳይሞላው በፊት የሐሰት አምልኮን ከይሁዳ ማስወገድ ጀመረ። (2 ዜና 34:1, 2) ገና ልጅ ብትሆንም እንኳ ይሖዋን በመፈለግና ስለ ባሕርያቱ በመማር የኢዮስያስን ምሳሌ መከተል ትችላለህ። እንዲህ ማድረግህ ራስህን ለእሱ ለመወሰን ያነሳሳሃል። ራስህን ለይሖዋ መወሰንህ በዕለት ተዕለት ሕይወትህ ላይ ምን ተጽዕኖ ያሳድራል? በ14 ዓመቱ የተጠመቀው ሉክ እንዲህ ብሏል፦ “ከአሁን ጀምሮ በሕይወቴ ውስጥ የይሖዋን አገልግሎት አስቀድማለሁ፤ እሱን ለማስደሰትም ጥረት አደርጋለሁ።” (ማር. 12:30) አንተም እንዲህ ማድረግ የምትፈልግ ከሆነ ትልቅ በረከት ታገኛለህ! w23.09 11 አን. 12-13
ሰኞ፣ መስከረም 8
በመካከላችሁ በትጋት እየሠሩና በጌታ ሥራ አመራር እየሰጧችሁ ያሉትን [አክብሯቸው]።—1 ተሰ. 5:12
ሐዋርያው ጳውሎስ ይህን ደብዳቤ በጻፈበት ወቅት የተሰሎንቄ ጉባኤ ከተቋቋመ አንድ ዓመትም አልሞላውም ነበር። በመሆኑም በዚያ ጉባኤ የነበሩት የተሾሙ ወንዶች ተሞክሮ ስለሚጎድላቸው አንዳንድ ስህተቶችን ሠርተው ሊሆን ይችላል። ያም ቢሆን አክብሮት ሊሰጣቸው ይገባ ነበር። ታላቁ መከራ እየተቃረበ ሲመጣ ከዋናው መሥሪያ ቤትም ሆነ ከቅርንጫፍ ቢሮው መመሪያ ማግኘት አንችል ይሆናል፤ ስለዚህ በዚያ ወቅት ከአሁኑ ይበልጥ መመሪያ የምናገኝበት ዋነኛ መስመር ሽማግሌዎቻችን ሊሆኑ ይችላሉ። በመሆኑም ከአሁኑ ለሽማግሌዎቻችን ፍቅርና አክብሮት ማዳበራችን አስፈላጊ ነው። ምንም ነገር ቢመጣ የማስተዋል ስሜታችንን እንጠብቅ፤ በእነዚህ ታማኝ ወንድሞች አለፍጽምና ላይ ሳይሆን ይሖዋ በክርስቶስ አማካኝነት እየመራቸው በመሆኑ ላይ ትኩረት እናድርግ። የራስ ቁር የአንድን ወታደር ጭንቅላት እንደሚጠብቅለት ሁሉ የመዳን ተስፋችንም አስተሳሰባችንን ይጠብቅልናል። ይህ ዓለም የሚያቀርብልን ማንኛውም ነገር ከንቱ እንደሆነ እንገነዘባለን። (ፊልጵ. 3:8) ተስፋችን እንድንረጋጋና ሚዛናችንን እንድንጠብቅ ይረዳናል። w23.06 11-12 አን. 11-12