የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • be ጥናት 36 ገጽ 209-ገጽ 211 አን. 1
  • ጭብጡን ማዳበር

በዚህ ክፍል ውስጥ ምንም ቪዲዮ አይገኝም።

ይቅርታ፣ ቪዲዮውን ማጫወት አልተቻለም።

  • ጭብጡን ማዳበር
  • በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
  • ተመሳሳይ ሐሳብ ያለው ርዕስ
  • አርዕስቱንና ዋና ዋና ነጥቦችን ማጉላት
    ቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት መመሪያ መጽሐፍ
  • አስተዋጽኦ ማዘጋጀት
    በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
  • ዋና ዋና ነጥቦች ጎላ ብለው እንዲታዩ ማድረግ
    ለማንበብ እና ለማስተማር የተቻለህን ሁሉ ጥረት አድርግ
  • አስተዋጽኦ ማዘጋጀት
    ቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት መመሪያ መጽሐፍ
ለተጨማሪ መረጃ
በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
be ጥናት 36 ገጽ 209-ገጽ 211 አን. 1

ጥናት 36

ጭብጡን ማዳበር

ምን ማድረግ ይኖርብሃል?

ጭብጡን አለፍ አለፍ እያልክ መጥቀስ እንዲሁም በንግግርህ መሃል በምታነሳቸው የተለያዩ ነጥቦች ሰፋ አድርገህ ማብራራት ይኖርብሃል።

አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

ንግግርህ አንድ ወጥ ይሆናል፤ እንዲሁም አድማጮችህ በቀላሉ ሊረዱትና ሊያስታውሱት ይችላሉ።

ልምድ ያላቸው ተናጋሪዎች አንድ ጭብጥ ይዞ መናገር ምን ያህል ጠቃሚ እንደሆነ ያውቃሉ። ንግግር በሚዘጋጁበት ጊዜ በተወሰኑ ነጥቦች ላይ ብቻ በማተኮር በዚያ ላይ በጥልቀት እንዲያሰላስሉ ይረዳቸዋል። ይህም ብዙ ነጥቦችን ላይ ላዩን ጠቅሰው ከማለፍ ይልቅ አድማጮቻቸውን ይበልጥ በሚጠቅም መንገድ ትምህርቱን ለማዳበር ያስችላቸዋል። እያንዳንዱ ዋና ነጥብ ከጭብጡ ጋር የተያያዘና ጭብጡን የሚያዳብር በሚሆንበት ጊዜ አድማጮች ነጥቦቹን ለማስታወስና የተጠቀሱበትን ዓላማ ለመገንዘብ ቀላል ይሆንላቸዋል።

ጭብጡ የንግግርህ ርዕሰ ጉዳይ ነው ሊባል ይችል ይሆናል። ይሁን እንጂ የንግግርህ ጭብጥ የርዕሰ ጉዳዩ አንድ ነጥብ ብቻ መሆኑን ከተገነዘብህ ጥሩ ንግግር መስጠት ትችላለህ። የአምላክ መንግሥት፣ መጽሐፍ ቅዱስ እና ትንሣኤ ሰፊ ርዕሰ ጉዳዮች ናቸው። ከእነዚህ ርዕሰ ጉዳዮች ብዙ ጭብጥ ሊወጣ ይችላል። ጥቂት ምሳሌዎችን እንጥቀስ:- “የአምላክ መንግሥት እውን መስተዳድር ነው፣” “የአምላክ መንግሥት ምድርን ገነት ያደርጋል፣” “መጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው በአምላክ መንፈስ እርዳታ ነው፣” “መጽሐፍ ቅዱስ ለዘመናችን የሚሆን ጠቃሚ መመሪያ ነው፣” “የትንሣኤ ተስፋ በሐዘን የተደቆሱትን ያጽናናል” እንዲሁም “የትንሣኤ ተስፋ ስደት ሲያጋጥመን እንድንጸና ይረዳናል።” እነዚህን ሁሉ ጭብጦች የምናዳብርበት አቅጣጫ የተለያየ ነው።

ኢየሱስ ክርስቶስ ምድር መጥቶ ሲያገለግል በስብከቱ ጎላ አድርጎ የገለጸው “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለች” የሚለውን ጭብጥ ነው ይህ ከአጠቃላዩ የመጽሐፍ ቅዱስ ጭብጥ ጋር ይስማማል። (ማቴ. 4:​17) ይህ ጭብጥ እየተብራራና ግልጽ እየሆነ የሄደው እንዴት ነው? በአራቱ ወንጌሎች ውስጥ ስለ አምላክ መንግሥት ከ110 ጊዜ በላይ ተጠቅሷል። ይሁንና ኢየሱስ “መንግሥት” የሚለውን ቃል ደጋግሞ በመጥቀስ ብቻ አልተወሰነም። ትምህርቶቹም ሆኑ የፈጸማቸው ተዓምራት ይሖዋ መንግሥቱን የሚሰጠው የአምላክ ልጅና መሲሕ እርሱ መሆኑን የሚያረጋግጡ ነበሩ። በእርሱ አማካኝነት ሌሎችም የመንግሥቱ ወራሽ የመሆን አጋጣሚ እንደሚያገኙ ግልጽ አድርጓል። ይህንን መብት የሚያገኙ ሰዎች ምን ዓይነት ባሕርይ ማሳየት እንዳለባቸውም አስተምሯል። ባስተማራቸው ትምህርቶችና በፈጸማቸው ድንቅ ተዓምራት አማካኝነት የአምላክ መንግሥት የእያንዳንዱን ሰው ሕይወት እንዴት እንደሚነካ ያሳየ ሲሆን በመንፈስ ቅዱስ እርዳታ አጋንንትን ማውጣቱም ‘የአምላክ መንግሥት ወደ አድማጮቹ እንደደረሰች’ የሚያረጋግጥ መሆኑን አስረድቷል። (ሉቃስ 11:​20) ኢየሱስ ተከታዮቹን ስለዚህ መንግሥት እንዲመሰክሩ አዝዟቸዋል።​—⁠ማቴ. 10:​7፤ 24:​14

ተስማሚ ጭብጥ። መጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንዳለው አንድን ጭብጥ በሰፊው ማብራራት አይጠበቅብህም። ሆኖም ለንግግርህ ተስማሚ ጭብጥ መኖሩ በጣም አስፈላጊ ነው።

ጭብጡን የምትመርጠው አንተ ከሆንክ በመጀመሪያ የንግግርህ ዓላማ ምን እንደሆነ አስብ። በንግግርህ አስተዋጽኦ ውስጥ የምታካትታቸው ዋና ዋና ነጥቦች የመረጥከውን ጭብጥ የሚደግፉ መሆን ይኖርባቸዋል።

ጭብጡ ከተሰጠህ ትምህርቱን ከምን አቅጣጫ ማዳበር እንዳለብህ ለማወቅ በደንብ ልታጤነው ይገባል። ጭብጡ ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነና እንዴት ሊዳብር እንደሚችል በደንብ ለመረዳት ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል። የተሰጠህን ጭብጥ ለማዳበር የሚረዱትን ነጥቦች የምትመርጠው አንተ ከሆንክ ጭብጡ እንዳይድበሰበስ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብሃል። በሌላ በኩል ደግሞ ጭብጡን የሚያዳብሩት ነጥቦች ቀርበውልህ ከሆነ ከጭብጡ ጋር በሚስማማ መንገድ እንዴት እንደምትጠቀምባቸው ማጤን ያስፈልግሃል። እንዲሁም ትምህርቱ ለአድማጮችህ አስፈላጊ የሆነው ለምን እንደሆነና የምታቀርብበት ዓላማም ምን እንደሆነ ማሰብ ይኖርብሃል። ይህ በንግግርህ አጽንዖት የምትሰጣቸውን ነጥቦች ለመምረጥ ይረዳሃል።

ጭብጡን ማጉላት የሚቻልበት መንገድ። ጭብጡን በተገቢው መንገድ ለማጉላት መሠረት መጣል ያለብህ ገና ነጥቦችህን ስትመርጥና ስታዋቅር ነው። ጭብጡን የሚደግፉ ነጥቦችን ብቻ ከተጠቀምህና ጥሩ አስተዋጽኦ ማዘጋጀት የሚቻልበትን መመሪያ ከተከተልህ ያለችግር ልታጎላው እንደምትችል የታወቀ ነው።

መደጋገም ጭብጡ ይበልጥ ጎላ ብሎ እንዲታይ ሊረዳ ይችላል። ጭብጥ እየተደጋገመ እንደሚመጣ የአንድ ዘፈን አዝማች ተደርጎ ሊገለጽ ይችላል። አዝማቹ የሚደገመው በተመሳሳይ መንገድ ላይሆን ይችላል። አንዳንድ ጊዜ አንድ ወይም ሁለት ሐረግ ብቻ ይደገም ይሆናል ወይም አዝማቹ ትንሽ ለውጥ ብቻ ይኖረዋል። ያም ሆነ ይህ የሙዚቃው አቀናባሪ አዝማቹ የሙዚቃው አካል ሆኖ እንዲዘልቅ ያደርጋል። የአንድ ንግግር ጭብጥም እንዲሁ መሆን አለበት። የጭብጡን ቁልፍ ቃላት መደጋገምን በዘፈን ውስጥ አለፍ አለፍ እያለ ከሚመጣው አዝማች ጋር ማመሳሰል ይቻላል። እነዚህን ቃላት በተመሳሳይ ቃላት እየተኩ መናገር ወይም ጭብጡን ትንሽ ለወጥ አድርጎ መግለጽ በተለያየ መንገድ ለመደጋገም ያስችላል። እንዲህ ካደረግህ ጭብጡ በአድማጮች አእምሮ ውስጥ ተቀርጾ ይቀራል።

እነዚህን ሐሳቦች ንግግር ስታቀርብ ብቻ ሳይሆን አገልግሎት ላይም ልትሠራባቸው ትችላለህ። ውይይቱ አጠር ያለ ቢሆንም እንኳ ጭብጡ ጎልቶ እንዲታይ ከተደረገ ሐሳቡ ቶሎ አይረሳም። መጽሐፍ ቅዱስ ስናስጠና ጭብጡን ካጎላን ትምህርቱ በቀላሉ የሚታወስ ይሆናል። ተስማሚ ጭብጥ ለመምረጥና ያንን ለማዳበር የምታደርገው ጥረት ንግግር የመስጠትና የአምላክን ቃል የማስተማር ችሎታህን በማሻሻል ረገድ ትልቅ ድርሻ ይኖረዋል።

የአንድ ታላቅ መጽሐፍ ዋና ጭብጥ

ጭብጥ ያለውን ሚና ለመገንዘብ ይሖዋ አምላክ ሰብዓዊ ጸሐፊዎችን ተጠቅሞ በ66ቱ የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት ውስጥ በሙሉ አንድ ዋና ጭብጥ እንዴት ጎላ ብሎ እንዲታይ እንዳደረገ መመርመሩ ጠቃሚ ይሆናል። ይህ ጭብጥ ይሖዋ በሰው ልጆች ላይ ያለው የመግዛት መብት ስለመረጋገጡና ዓላማው በመንግሥቱ አማካኝነት እውን ስለመሆኑ የሚገልጽ ነው።

የዚህ ጭብጥ ፍንጭ መጀመሪያ የተጠቀሰው በዘፍጥረት መጽሐፍ የመክፈቻ ምዕራፎች ላይ ሲሆን በቀሩት የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት ውስጥ ይበልጥ እየዳበረ ሄዷል። መለኮታዊው ስም ብቻ ከ7, 000 ጊዜ በላይ ተደጋግሞ ተጠቅሷል። የይሖዋ የመግዛት መብት ስለ ፍጥረት በሚናገረው ዘገባ ውስጥ ተንጸባርቆ ይገኛል። አገዛዙን በተመለከተ የተነሳው ግድድር እንዲሁም አለመታዘዝ የሚያስከትለው መዘዝ ተገልጿል። ይሖዋ ከፍጥረታት ጋር በተያያዘ ያደረጋቸው ነገሮች አቻ የማይገኝለትን ፍቅሩን፣ ጥበቡን፣ ፍትሑንና ታላቅ ኃይሉን አንጸባርቀዋል። አምላክን መታዘዝ ያለውን ጥቅምና እርሱን አለመታዘዝ የሚያስከትለውን መዘዝ የሚያሳዩ በርካታ ምሳሌዎች አሉ። በፍጥረታቱ ላይ ያለውን ሉዓላዊነት አምነው ለመቀበል አሻፈረኝ በሚሉ ክፉ መናፍስትና ሰዎች ላይ እርምጃ ስለሚወስደው የይሖዋ ሰማያዊ መንግሥትም ብዙ ዝርዝር ጉዳዮች ተጠቅሰዋል። ይሖዋ ምድር ገነት እንድትሆንና እርሱን በሚወዱና በሚያመልኩ እንዲሁም እርስ በርሳቸው በሚዋደዱ ሰዎች እንድትሞላ ዓላማ አለው። የአምላክ መንግሥት ይህን ዓላማውን ዳር እንደሚያደርስ ተገልጿል።

ጭብጡን ማዳበር የሚቻልበት መንገድ

  • ንግግርህን በምትዘጋጅበት ጊዜ የምትመርጣቸው ዋና ዋና ነጥቦችና ተጨማሪ ሐሳቦች ጭብጡን ለማዳበር የሚረዱ መሆን ይኖርባቸዋል።

  • አቀራረብህን በምትለማመድበት ጊዜ የት ላይና እንዴት ጭብጡን እንደምታጎላ ማሰብ ያስፈልግሃል። ለዚህ ዓላማ የመረጥካቸውን ቦታዎች ምልክት ልታደርግባቸውም ትችል ይሆናል።

  • አለፍ አለፍ እያልክ የጭብጡን ሐሳብ ወይም ቁልፍ ቃላት ጥቀስ።

መልመጃ፦ በአገልግሎት የምትጠቀምበት አንድ ጭብጥ ምረጥ። ይህ ጭብጥ በቅርቡ በመጠበቂያ ግንብ ወይም ንቁ! ላይ ከወጣ አንድ ርዕስ ጋር የሚስማማ ይሁን። አድማጭህ ለዚህ ጭብጥ ጉጉት እንዲያድርበት የሚያደርግ መግቢያ ይኑርህ። በውይይቱ ወቅት ጭብጡን የሚያዳብሩ አንድ ወይም ሁለት ነጥቦች ተጠቀም። መደምደሚያህ ላይ ደግሞ ጠቀሜታውን ጎላ አድርገህ ግለጽ።

    አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
    ውጣ
    ግባ
    • አማርኛ
    • አጋራ
    • የግል ምርጫዎች
    • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
    • የአጠቃቀም ውል
    • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
    • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
    • JW.ORG
    • ግባ
    አጋራ