የመንግሥቱ አዋጅ ነጋሪዎች ሪፖርት
“የደወልሽው ቁጥር የተሳሳተ ነው”
በጆሀንስበርግ ደቡብ አፍሪካ ሌስሊ እና ካሮላይን በቀላሉ መግባት በማይፈቀድበት የጡረተኞች መንከባከቢያ መንደር ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች ተራ በተራ በስልክ ይመሰክሩ ነበር። አብዛኛውን ጊዜ ሰዎቹ እቤታቸው ስለማይገኙና ቢገኙም ለክርስቲያናዊው መልእክት እምብዛም ፍላጎት ስለማያሳዩ አንዲት ሴት ስልኩን አንስታ ስታነጋግራት ካሮላይን ደስ አላት።
ካሮላይን “ወ/ሮ እገሊት ነዎት?” ስትል ጠየቀች።
“አይ፣ አይደለሁም፤ ወ/ሮ እገሊት ነኝ። የደወልሽው ቁጥር የተሳሳተ ነው” የሚል በአክብሮታዊ መንገድ የቀረበ ምላሽ አገኘች።
ካሮላይን የሴትየዋ አነጋገር ወዳጃዊ ስሜት እንዳለው በመገንዘብ እንዲህ አለች:- “ወ/ሮ እገሊትን የፈለግኩበትን ጉዳይ ለእርስዎም ልነግርዎት እችላለሁ።” ከዚያም የአምላክ መንግሥት ስለሚያመጣቸው በረከቶች ነገረቻቸው። አምላክ ከእኛ የሚፈልገው ምንድን ነው? የተባለውን ብሮሹር ልትሰጣቸው ከተነጋገሩ በኋላ ሴትየዋ እንዲህ የሚል ጥያቄ አቀረቡ:- “በነገራችን ላይ የየትኛው ሃይማኖት ተከታይ ነሽ?”
ካሮላይን “የይሖዋ ምሥክሮች ነን” በማለት መለሰች።
“ይሄማ የምጠላው ሃይማኖት ነው! ከእናንተ ጋር መወያየት አልፈልግም።”
“ግን እኮ ላለፉት 20 ደቂቃዎች የአምላክ መንግሥት በቅርቡ ለሰው ልጆች ስለሚያደርጋቸው ነገሮች ከመጽሐፍ ቅዱስ በመጥቀስ በጣም አስደናቂ ስለሆነው ተስፋ ስነግርዎት ነበር። እነዚህን ነገሮች በመስማትዎ በጣም ተደስተው እንዲያውም ይበልጥ ለማወቅ ሁሉ ጓጉተው ነበር። ለመሆኑ ስለ ይሖዋ ምሥክሮች ምን ያህል ያውቃሉ? ቢታመሙ ለበሽታዎ መፍትሔ ለማግኘት መካኒክ ያማክራሉ? የይሖዋ ምሥክሮች ምን ብለው እንደሚያምኑ ለምን እኔ ራሴ አልነግርዎትም?” በማለት ካሮላይን ስሜት ቀስቃሽ ጥያቄ ጠየቀቻቸው።
ከጥቂት ጊዜ ዝምታ በኋላ ሴትየዋ እንዲህ ሲሉ መለሱ:- “እንደሱ ሳይሻል አይቀርም። መጥተሽ ብንነጋገር ጥሩ ነው። እምነቴን በፍጹም እንደማታስለውጪኝ ግን እወቂ!”
ካሮላይን “ወ/ሮ እገሊት እኔ ብፈልግ እንኳን በፍጹም ሃይማኖትዎን ላስቀይርዎ አልችልም። እንደዚያ ማድረግ የሚችለው ይሖዋ ብቻ ነው” በማለት መለሰች።
በቀጠሯቸው መሠረት ብሮሹሩን የወሰደችላቸው ሲሆን ሴትየዋም (ቤቲ ይባላሉ) በድጋሚ መጥታ እንድታነጋግራቸው ተስማሙ። በሚቀጥለው ጊዜ ካሮላይን ተመልሳ ስትሄድ ቤቲ በጡረተኞቹ መመገቢያ አዳራሽ ውስጥ አብረዋቸው ለሚቀመጡት ሴቶች ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር እየተወያዩ እንደሆነ ሲነግሯቸው ሴቶቹ “እንዴ ምን ነካሽ? እነዚህ ሰዎች በኢየሱስ እንኳን አያምኑም!” በማለት እንዳጣጣሏቸው ነገሯት።
ካሮላይን ወዲያው ባለፈው ስለ አምላክ መንግሥት ካደረጉት ውይይት ላይ አንድ ዓቢይ ሐሳብ አስታወሰቻቸው።
“የዚህ መንግሥት ንጉሥ ማን ነው?” ስትል ጠየቀቻቸው።
“ኢየሱስ ነዋ!” በማለት ቤቲ መለሱ።
“ትክክል ነዎት” አለችና ከዚያም የይሖዋ ምሥክሮች፣ ኢየሱስ ከአምላክ ጋር የሚተካከል የሥላሴ ክፍል ሳይሆን የአምላክ ልጅ መሆኑን እንደሚያምኑ አብራራችላቸው።—ማርቆስ 13:32፤ ሉቃስ 22:42፤ ዮሐንስ 14:28
ምንም እንኳን ቤቲ ብሩህና ደስተኛ መንፈስ ያላቸው ቢሆንም የጤናቸው ሁኔታ ጥሩ እንዳልነበረ የተወሰኑ ተመላልሶ መጠይቆች ከተደረጉላቸው በኋላ ታወቀ። የካንሰር በሽታ ስላለባቸው ከአሁን አሁን እሞታለሁ እያሉ ይፈሩ ነበር። “እነዚህን ነገሮች ከዓመታት በፊት ሰምቻቸው ቢሆንና እንደ አንቺ ዓይነት እምነት ቢኖረኝ እንዴት ደስ ባለኝ ነበር” በማለት ተናግረዋል። ካሮላይን ሞት ከከባድ እንቅልፍ ጋር ሊመሳሰል እንደሚችልና የሞተ ሰው በትንሣኤ እንደሚነሳ የሚገልጹ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችን በማሳየት አጽናናቻቸው። (ዮሐንስ 11:11, 25) በዚህ በጣም የተበረታቱት ቤቲ አሁን በቋሚነት መጽሐፍ ቅዱስን ያጠናሉ። በመንግሥት አዳራሽ ተገኝተው በስብሰባ እንዳይካፈሉ ያገዳቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሽቆለቆለ የሚሄደው የጤናቸው ሁኔታ ብቻ ነው።
ካሮላይን እንዲህ በማለት ትናገራለች:- “ይህን ሥራ የሚመሩት መላእክት እንደሆኑ ይበልጥ ግልጽ ሆኖልኛል። ቤቲን ያገኘኋቸው ‘የተሳሳተ ቁጥር’ በመደወሌ ምክንያት ነበር። በዚያ ላይ የ89 ዓመት አረጋዊ ናቸው!”—ራእይ 14:6