“እምነት ከመስማት ነው”
1 “ለዘላለም ሕይወት ትክክለኛ ዝንባሌ” ያለው ሰው ስናገኝ በሰማው ነገር ላይ ያለውን እምነት ማጠናከር አስፈላጊ ነው። (ሥራ 13:48 አዓት፤ ሮሜ 10:17) ይህንንም ለማድረግ አዳዲስ እትሞችን ይዞ በመሄድና ተጨማሪ ውይይት በማድረግ መጽሔት ላበረከትንላቸው ሰዎች ተመላልሶ መጠየቅ ማድረግ አለብን። ልባዊ ፍላጎት ካሳዩ ኮንትራት እንዲገቡ መጋበዝ ይቻላል። ሆኖም ወደ ዘላለም ሕይወት የሚመራ እውቀት ወይም ለዘላለም መኖር በተባሉት መጻሕፍት አለዚያም በደስታ ኑር! በተባለው ብሮሹር አማካኝነት ጥናት የማስጀመር ግብ ይኑርህ። ከዚህ በታች ጥቂት ጠቃሚ የሆኑ አቀራረቦች ሰፍረዋል:-
2 “የዘላለሙን ንጉሥ አወድሱ!” በሚለው ርዕስ ላይ ተወያይታችሁ ለነበረ ሰው ተመላልሶ መጠየቅ ስታደርግ እንዲህ በማለት መጀመር ትችላለህ:-
◼ “እንደምንዎት? ባለፈው ጊዜ ሁሉን ቻይ አምላክ እንዳለ ከሚያሳዩ ብዙ ማስረጃዎች መካከል ጥቂቶቹን ተመልክተን ነበር። ሆኖም አምላክ መኖሩን ማወቅ ብቻ በቂ አይደለም። ስሙን ማወቅ ያስፈልገናል። አምላክን የሚጠሩት ማን ብለው ነው? [መልስ እንዲሰጥ ፍቀድለት።] በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች ‘ጌታ’ ወይም ‘አምላክ’ ብለው ይጠሩታል፤ እነዚህ ደግሞ የማዕረግ ስሞች ናቸው። ከዚህም በላይ አምላክ በስሙ እንድናውቀው ይፈልጋል። [መዝሙር 83:18ን አንብብ።] (የ1980 ትርጉም በገጽ 301 ላይ በሚገኘው የቃላት መፍቻው እግዚአብሔር የሚለው ቃል ይሖዋ የሚለውን ስም እንደሚያመለክት ይናገራል።) በዚህ መጽሐፍ ውስጥ እንደተብራራው መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ይሖዋ አምላክ ብዙ ነገሮች ይነግረናል።” እውቀት በተባለው መጽሐፍ ገጽ 29 ላይ ያለውን ሥዕል አሳየውና ለሥዕሉ የተሰጠውን መግለጫ አንብብ። በምዕራፍ 3 ላይ በሚገኙት የመጀመሪያዎቹ ሦስት አንቀጾች ላይ ከተወያያችሁ ጥናት አስጀመርክ ማለት ነው!
3 “የዓለም ሃይማኖቶች የሚጠፉት ለምንድን ነው?” በሚለው ርዕስ ላይ ተወያይታችሁ ለነበረ ሰው እንደሚከተለው በማለት ተመላልሶ መጠየቅ ልታደርግለት ትፈልግ ይሆናል:-
◼ “ይህንን ርዕስ ካነበቡ በኋላ ሁሉንም ሃይማኖቶች አንድ አድርገን መመልከት እንደማንችል በማወቅዎ ተገርመው ይሆናል። እውነተኛ ሃይማኖት እንዳለ ሁሉ ሐሰተኛ ሃይማኖቶችም አሉ። ይህም አምላክ የሚቀበለው የእነማንን አምልኮ ነው? የሚል ምክንያታዊ ጥያቄ ያስነሳል። ኢየሱስ ለዚህ ጥያቄ መልስ የሰጠ ሲሆን መልሱ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ጎላ ተደርጎ ተገልጿል።” እውቀት የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 5 ካወጣህ በኋላ አንቀጽ 4ንና ዮሐንስ 4:23, 24ን አንብብ። ከዚያም “ያለ ምንም ክፍያ እቤትዎ መጽሐፍ ቅዱስ ማጥናት ይፈልጋሉ?” በማለት ጠይቀው። እሺ ካለ ምዕራፍ 1 አውጣና ጥናት ጀምር።
4 ለሚያዝያ— ሰኔ “ንቁ!” መጽሔት ፍላጎት አሳይቶ ለነበረ ሰው ተመላልሶ መጠየቅ ስታደርግ “እውቀት” በተባለው መጽሐፍ ጥናት ለማስጀመር በሚከተለው አቀራረብ ልትጠቀም ትችላለህ:-
◼ “ጦርነት የማይኖርበት ዓለም እንደሚመጣ ያደረግነውን ውይይት ያስታውሱት ይሆናል። እንዲህ ያለው ጊዜ ምን እንደሚመስል ለማሰብ እንኳ ያስቸግራል። እዚህ ላይ አንድ ሠዓሊ እንዲህ ባለ መልኩ አስቀምጦታል። [እውቀት በተባለው መጽሐፍ ገጽ 188-9 ላይ የሚገኘውን ሥዕል አሳየው።] በዚህ አካባቢ መኖር አያስደስትም? [ገጽ 4-5ን አውጥተህ ሥዕሉን አሳየውና ሣጥኑ ውስጥ ያለውን ሐሳብ አንብብ።] የዚህ መጽሐፍ ርዕስ በዮሐንስ 17:3 ላይ ከሚገኙት የኢየሱስ ቃላት ጋር የሚመሳሰል ነው። [ጥቅሱን አንብብ።] ፈቃድዎ ከሆነ በዚህ መጽሐፍና በመጽሐፍ ቅዱስ ተጠቅመው ይህንን ሕይወት አድን የሆነ እውቀት ማግኘት የሚችሉት እንዴት እንደሆነ ላሳይዎ እወዳለሁ።” የምታነጋግረው ሰው ፈቃደኛ ከሆነ በመጀመሪያው ምዕራፍ ተጠቅመህ ጥናት ጀምር።
5 መጀመሪያ ስታነጋግረው ሥራ በዝቶበት ከነበረ ሰው ጋር ከተገናኘህ እንዲህ ማለት ትችላለህ:-
◼ “በቅርቡ መጥቼ መጠበቂያ ግንብ እና ንቁ! የተባሉትን መጽሔቶች ትቼልዎ ነበር። እነዚህ ወቅታዊ መጽሔቶች ለመጽሐፍ ቅዱስና መጽሐፍ ቅዱስ ለሚሰጣቸው የሥነ ምግባር መመሪያዎች ያለንን አክብሮት ይገነባሉ። ሁሉም ሰው የአምላክን ቃል ቢረዳ በጣም ጠቃሚ ነው ብዬ ስለማስብ ይህንን ለማድረግ የሚረዳዎ አንድ ነገር ላሳይዎ ተመልሼ መጥቻለሁ።” እውቀት የተባለውን መጽሐፍ አውጣና ገጽ 3 ላይ የሚገኘውን የርዕስ ማውጫ አሳየው። ይበልጥ ለማወቅ የሚፈልገው ስለ የትኛው ርዕስ እንደሆነ ጠይቀውና ምዕራፉን አውጥተህ ጥናት ጀምር።
6 ወደ ዘላለም ሕይወት የሚወስደውን ‘የእምነት በር ለሌሎች ሰዎች መክፈት’ ከቻልን ደስታችን እጥፍ ድርብ ይሆናል።— ሥራ 14:27፤ ዮሐ. 17:3