አዲስ የወረዳ ስብሰባ ፕሮግራም
1 በአንዳንድ ቦታዎች በጥር ወር መግቢያ ላይ የሚጀመረው የወረዳ ስብሰባ ፕሮግራም “በመስጠት የሚገኘውን ታላቅ ደስታ ቅመሱ” የሚል ጭብጥ ይኖረዋል። (ሥራ 20:35) ደስታ “የደህንነትና የእርካታ ስሜት መሰማት” ተብሎ ሊገለጽ ይችላል። ብዙ ሰዎች ከሕይወት ሊያገኙ የሚችሉትን ማንኛውንም ዓይነት ደስታ ለማግኘት ያልተቆጠበ ጥረት ያደርጋሉ። ሆኖም እንዲህ ዓይነቱ ደስታ ጊዜያዊ ብቻ ይሆናል። ይህም እውነተኛ ደስታ አይደለም። ይሁን እንጂ ይሖዋ ራሳችንን እንዴት ለዘላለም መጥቀም እንደምንችል ያስተምረናል። (ኢሳ. 48:17፤ 1 ዮሐ. 2:17) አዲሱ የወረዳ ስብሰባ ፕሮግራም መንፈሳዊ ነገሮችን በመስጠት ከሁሉ የበለጠ ደስታ ሊገኝ የሚችለው እንዴት እንደሆነ ጎላ አድርጎ ይገልጻል።
2 ራሳችንን ለአገልግሎቱ ማዋል የምንችለው እንዴት እንደሆነ ተግባራዊ በሆነ መንገድ እንማራለን። ተጓዥ የበላይ ተመልካቾች ከሚያቀርቧቸው ንግግሮች መካከል “በዓመፃ ገንዘብ ወዳጆችን መግዛት፣” “መለኮታዊ ዝግጅት ለሆነው ‘የሰዎች ስጦታ’ አክብሮት ይኑራችሁ፣” እና “የእውነተኛውን ደስታ የተለያዩ ዘርፎች መቅመስ” የሚሉት ይገኙበታል። በስብሰባው ላይ ለመጠመቅ ፍላጎት ያላቸው ሁሉ የጥምቀት ጥያቄዎች አብረዋቸው የሚከልሱላቸውን ሽማግሌዎች እንዲያዘጋጅላቸው ለሰብሳቢ የበላይ ተመልካቹ ማሳወቅ ይኖርባቸዋል። ንጹሕ ዝምድና መሥርቶ ይሖዋን ማገልገል ለአዲስ ተጠማቂዎች ትልቅ ደስታ ያመጣላቸዋል።
3 የይሖዋን ሥልጣን በትክክል ማወቅና መቀበልም እውነተኛ ደስታና ዋስትና ያለው ሕይወት ያስገኛል። ሁሉም ሰዎች ይህን ሐቅ ማወቅ ይኖርባቸዋል። በወረዳው ስብሰባ ላይ የሚቀርበው የሕዝብ ንግግርም “ደስተኛ ከሆኑት የአምላክ ሕዝቦች ጋር ተባበሩ” የሚል ጭብጥ ያለው ነው። ለእውነት ፍላጎት ያሳዩ ሰዎች ሁሉ በዚህ ንግግር ላይ እንዲገኙ መጋበዛችሁን አትዘንጉ። በሰይጣን መዳፍ ሥር ካሉት ከዚህ ዓለም ሰብዓዊ ገዢዎች ምንም ዓይነት እውነተኛ ዋስትና ያለው ሕይወትም ሆነ ዘላቂ ደስታ ሊያገኙ አይችሉም። (መክ. 8:9) ይሁን እንጂ ደስተኛ ከሆኑት የይሖዋ ሕዝቦች ጋር መቀላቀላቸው እንዴት ያለ ደስታ ያስገኝላቸው ይሆን!— መዝ. 144:15
4 ምንም እንኳ እየተባባሱ የሚሄዱ አስከፊ ሁኔታዎች በዚህ የነገሮች ሥርዓት ውስጥ ቢኖሩም በመንፈሳዊ ለጋስ በመሆን ታላቅ ደስታ የተጎናጸፉ ሁሉ ወደፊትም ቢሆን ደስተኛው አምላክ ፈጽሞ አያሳፍራቸውም። (1 ጢሞ. 1:11) እንዲህ ያለው ሁኔታ ትክክል መሆኑን አዲሱ የወረዳ ስብሰባ ማረጋገጫ ይሰጠናል። ስብሰባው አያምልጣችሁ!